የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ጫኔ ከበደ (ዶ/ር) መሆናቸውን አስታወቀ፡፡ በቅርቡ ተደርጓል የተባለውን የፕሬዚዳንት ለውጥ አላውቅም ብሏል፡፡ ቦርዱ ይህን ያስታወቀው በሳምንቱ መጀመርያ ላይ ለፓርቲው አመራሮች በጻፈው ደብዳቤ መሆኑን፣ የቦርዱ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ተስፋዓለም ዓባይ ለሪፖርተር አስታውቀዋል፡፡
በኢዴፓ አመራሮች መካከል ከገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ ጋር እየተደረገ በሚገኘው ድርድር ላይ፣ አለመግባባቶች ተፈጥረው እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡
በዚህም መሠረት አቶ አዳነ ታደሰ የፓርቲው ፕሬዚዳንት እኔ ነኝ በማለት ለድርድሩ ዋና አደራዳሪና ለተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን ደብዳቤ ቢጽፉም፣ ምርጫ ቦርድ ግን አቶ አዳነን በኢዴፓ ፕሬዚዳንትነት እንደማያውቃቸው አስታውቋል፡፡
የኢዴፓን ፕሬዚዳንት የሚመርጠው የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት 25 አባላት ያሉት ሲሆን፣ አቶ አዳነ ፕሬዚዳንት ነኝ ብለው ሲነሱ የብሔራዊ ምክር ቤቱ ምልዓተ ጉባዔ ያልተሟላ በመሆኑ ቦርዱ ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጎታል ሲሉ አቶ ተስፋዓለም አስረድተዋል፡፡
‹‹በአቶ አዳነ የሚመራው ቡድን 14 የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት የፈረሙበትን ደብዳቤ በማያያዝ ፕሬዚዳንት ሆነው መመረጣቸውን ቢገልጽም፣ ቦርዱ ባደረገው ማጣራት ሁለት ሰዎች ከዚህ ውጪ እንደሆኑ ተደርሶበታል፡፡ በዚህም መሠረት አንደኛው የኦዲትና ኢንስፔክሽን ኮሚቴ አባል ሲሆን፣ አንደኛው ደግሞ ፓርቲው ከዚህ ቀደም ለቦርዱ ባስገባው የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት ስም ዝርዝር ውስጥ የማይገኝ በመሆኑ ጥያቄያቸው ተቀባይነት አላገኝም፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ምልዓተ ጉባዔ ባልተሟላበት ሁኔታ የተመረጠ ፕሬዚዳንት በቦርዱ በኩል ተቀባይነት የለውም፡፡ ስለሆነም ምርጫ ቦርድ የኢዴፓ ፕሬዚዳንት መሆናቸውን የሚያውቀው ጫኔ ከበደን (ዶ/ር) እንጂ አቶ አዳነ ታደሰን አይደለም፤›› በማለት አቶ ተስፋዓለም ገልጸዋል፡፡