Thursday, June 1, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትር

[ክቡር ሚኒስትሩ በአዲሱ ሹመት ውስጥ ባለመካተታቸው ተበሳጭተው ከባለቤታቸው ጋር እያወሩ ነው]

  • ምንድነው ብስጭትጭት ያደረገህ?
  • እንዴት አልበሳጭ?
  • ካልተሾምክ ምን ታደርገዋለህ ታዲያ?
  • የእኔ ውለታ ይኼ ነው?
  • የምን ውለታ?
  • ለድርጅቴ ብትይ ለመንግሥት ብትይ የሠራሁት ውለታ?
  • ድንቄም ውለታ፡፡
  • ምን ማለትሽ ነው?
  • አንተን ብሎ ባለውለታ?
  • አንቺም እንዲህ ትያለሽ?
  • አንዳንዴ እውነቱን እንነጋር እንጂ፡፡
  • የምን እውነት?
  • በሹመትህ ዘመን ምን ሠራህ?
  • እኔ?
  • እኔ ነኝ ታዲያ?
  • እንዴት ምን ሠራህ ትይኛለሽ?
  • ከአገልግሎትህ ይልቅ ያጋበስከው ጥቅም የትና የት ነው፡፡
  • በምን? በምን?
  • በውጭ ጉዞ ብትል ከአፍሪካ እስከ አውሮፓ፣ ከእስያ እስከ አሜሪካ ምኑ ቅጡ. . .
  • እሺ?
  • ከጉዞ አበል እስከ ክብር መጠበቂያ በዩሮ፣ በዶላር. . .
  • ሌላስ?
  • በመንግሥት ወጪ በውድ ሆቴሎች መንፈላሰስ፡፡
  • ከዚያስ?
  • ከፕራዶ እስከ ቪኤይት በየዓይነቱ፡፡
  • ህም. . .
  • የሚዥጎደጎድልህ ሥጦታና ገፀ በረከት በቀላሉ የሚነገር አይደለም፡፡
  • ሆሆ. . .
  • በዚያ ላይ ከተለያዩ ፕሮጀክቶች የሚገኘው በሚሊዮኖች የሚቆጠር ኮሚሽን፡፡
  • ወይ ጉድ?
  • በተለያዩ ዘመዶችህ ስም ሕንፃዎች፣ ሞሎች፣ ሆቴሎች፣ ሬስቶራንቶች፣ ጂሞች. . .
  • ኧረ አንቺ ሴትዮ ዝም በይ፡፡
  • እኔማ ዝም ብዬ ነው የኖርኩት፡፡
  • አሁን ይኼን ሁሉ የሚያስለፈልፍሽ ምንድነው?
  • አንተ ነሃ፡፡
  • እኔ ምን ሆንኩ?
  • ለምን አልተሾምኩም ብለህ ስትበሳጭ ነዋ?
  • ምን ልበል ታዲያ?
  • እንኳንም ሹልክ ብዬ ወጣሁ ነው ማለት ያለብህ፡፡
  • ለምን?
  • አላርፍ ካልክ የሚከተለውን አታውቅም ማለት ነው?
  • ምን እንዳይመጣ?
  • ተረቱን አታውቀውም?
  • ምን የሚባለውን?
  • ‹የአንበሳ ትራፊ አይጥ በልታ በልታ፣ አመጣች ነገሯን ጎትታ ጎትታ› የሚባለውን፡፡
  • ምን ለማለት ነው?
  • ካላረፍክ ዋ!
  • ምንድነው እሱ?
  • እጅህ ላይ ያጠልቁልሃል፡፡
  • የወርቅ ብራስሌት?
  • አይይ. . .
  • ምንድነው ታዲያ?
  • ካቴና!

[ክቡር ሚኒስትሩ እንደተሰባጩ ወደ ቢሯቸው እየሄዱ ከሾፌራቸው ጋር እያወሩ ነው]

  • ክቡር ሚኒስትር?
  • አቤት፡፡
  • የእኔ ጉዳይ ምን ሊሆን ነው?
  • አንተ ደግሞ ምን ሆንክ?
  • እርስዎ ከሥልጣንዎ ተነሱ ማለት አይደል?
  • ማን ነገረህ እሱን?
  • አሁን ባረጋግጥም ቀደም ሲል ሠራተኛው ሁሉ ይኼንን አይደል እንዴ ሲያወራ የከረመው?
  • ቀድሞ ከየት ሰማው?
  • በዚህ ዘመን ወሬ ከየት መጣ አይባልም እኮ?
  • ፌስቡክ በተዘጋበት በዚህ ጊዜ የእኔ መነሳት ወሬ ከየት መጣ?
  • ፌስቡክ ቢዘጋም ወሬው ግን በእግሩ መጥቷል፡፡
  • አንተ ከየት ሰማህ?
  • ሠራተኞች ክበብ ውስጥ ሲወራ፡፡
  • ምን ተባለ?
  • ክቡር ሚኒስትሩ ተንሳፈፉ፡፡
  • የሚያንሳፍፍ ያንሳፋችሁ፡፡
  • እኔ ግራ የገባኝ የራሴ ጉዳይ ነው፡፡
  • አንተ ምን ትሆናለህ?
  • እርስዎ ከተባረሩ ማለቴ ከተነሱ አለቀልኝ፡፡
  • እንዴት?
  • የሚወራውማ ሌላ ነው፡፡
  • ምን ተባለ?
  • እርስዎ ከተጫሩ እኔም መውረዴ ነው፡፡
  • ከምንድነው የምትወርደው?
  • ከቪኤይት ነዋ፡፡
  • ከዚያስ?
  • ጠቅላላ አገልግሎት ሊወሽቁኝ ነው ተብሏል፡፡
  • ወይ ጣጣ?
  • ሞተሩ እንደ ወፍጮ የሚጮህ አሮጌ ፒካፕ ላይ መመደቤን ሰምቻለሁ፡፡
  • እኔ ሳላውቅ ይኼ ሁሉ ከምኔው ተወሰነ?
  • እርስዎ ጥቅም የሚያስገኙ ትልልቅ ፕሮጀክቶች ላይ ብቻ ሲሯሯጡ ሌላውን እኮ አያውቁትም ነበር፡፡
  • ማለት?
  • ማለትማ እንደሌሉ ነበር የሚቆጠረው፡፡
  • እንዴት?
  • ለዚህም እኮ ነው የሚንሳፈፉት፡፡
  • አንተ ምን እያልክ ነው?
  • እየተባለ ያለውን ነው የደገምኩልዎት፡፡

[ክቡር ሚኒስትሩ የበለጠ እየተናደዱ ቢሮአቸው ገብተው ጸሐፊያቸውን ጠሯት]

  • አንቺ ምን እየተከናወነ ነው ያለው፡፡
  • ኧረ ጉድ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምንድነው ጉዱ?
  • ልክ እንደ እግር ኳስ ቡድን ነው የሆነው፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • አዲስ ፎርሜሽን ተሠራ እየተባለ ነው፡፡
  • የምን ፎርሜሽን?
  • በፊት የነበረው 4-4-2 ፎርሜሽን ተለውጧል፡፡
  • እና ምን ሆነ ታዲያ?
  • አሁን 3-5-2 ሆኗል ተብሏል፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • በጥልቀት ማጥቃት የሚያስችል፡፡
  • ከጥልቅ ተሃድሶ ጋር ይገናኛል?
  • እንዲያ ነው አሉ፡፡
  • ይኼንን ከእኔ ጋር ምን ያገናኘዋል?
  • እርስዎ ቻው ከተባሉ አሠላለፉ እንዲህ ነው እየተባለ ነው፡፡
  • ማን ነው የነገረሽ?
  • አማካሪዎ፡፡
  • እሱም እየዶለተብኝ ነበር እንዴ?
  • አሠላለፍን መቀየር ብቻ ሳይሆን ማሊያ መቀየርም ተጀምሯል፡፡
  • እኔን ከዳኝ ማለት ነው?
  • መሰለኝ፡፡
  • በምን አወቅሽ?
  • የሆነ ጥቅስ ሲያነበንብ ነበር፡፡
  • ምን የሚሉት ጥቅስ?
  • ‹በሚሰጥም ጀልባ ማንም አይሳፈርም› የሚል፡፡
  • ምን አልሽ አንቺ?
  • እኔ አይደለሁም ያልኩት፡፡
  • ያንቺስ አቋም ምንድነው?
  • ከተጨባጭ ሁኔታው አንፃር የተቃኘ ነው፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • እኔ ደግሞ አንድ አባባል ደስ ይለኛል፡፡
  • ምንድነው እሱ ደግሞ?
  • ‹ሁለት ባላ ትከል አንዱ ሲሰበር ሌላው ላይ ተንጠልጠል› የሚል፡፡
  • እና?
  • እናማ አሳዘኑኝ፡፡
  • አሳዝኜሽስ?
  • አማካሪዎት እንዳለው መሆኑ ነው፡፡
  • ምንድነው የሚሆነው?
  • አዲሱን ፎርሜሽን በአዲሱ ማሊያ መቀላቀል፡፡
  • በቃ?
  • ምን ይደረግ እንግዲህ?
  • ወይ ሰው?
  • ቀበሮም እንዲህ ነው ያለችው፡፡
  • ምን አለች?
  • ‹ለሰው ሞት አነሰው›፡፡

[ክቡር ሚኒስትሩ ተናደው በትካዜ ውስጥ እንዳሉ አንድ የሚያውቁት ባለሀብት ደወለላቸው]

  • ክቡር ሚኒስትር ምንድነው የምሰማው?
  • ምን ሰማህ?
  • ተንሳፋፉ መባልን፡፡
  • ይኼ ቃል ከየት ነው የተሠራጨው?
  • ምኑ?
  • መንሳፈፍ የሚባለው?
  • መባረር ከሚባለው ይሻላል ተብሎ ነው፡፡
  • አንተም እንዲህ አልክ?
  • ምን ልበል ታዲያ?
  • ትንሽ ኃፍረት የለህም?
  • ለምን የሚሆን?
  • ይሉኝታ፡፡
  • ይሉኝታ ድሮ ቀረ፡፡
  • በምን ተተካ?
  • በአማራጭ ፍለጋ፡፡
  • ምን ዓይነት አማራጭ?
  • ከወቅቱ ጋር መራመድ፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • አሮጌውን ሸኝቶ አዲሱን ማላመድ፡፡
  • በዚህ ነው የተካንከው፡፡
  • ይኼንንማ እርስዎ ከእኔ በላይ ያውቁታል፡፡
  • እንዴት እባክህ?
  • ያኔ ጨረታዎቹን እንደ ካርታ እየፐወዙ ሲጫወቱብን ነዋ፡፡
  • አሁን እየተካካድን ነው ማለት ነው?
  • አዎን፡፡
  • ስለዚህ?
  • ያው እንግዲህ እኔም በጨረታው አልገደድም፡፡
  • ምን ለመሆን?
  • ከእርስዎ ጋር የነበረኝን ግንኙነት ለማቋረጥ፡፡
  • ይዝጋህ!
  • እርስዎም እንዳይዘጋብዎት፡፡
  • የት ነው የሚዘጋብኝ?
  • ቅሊንጦ!

[ክቡር ሚኒስትሩ እንዲሁ ሲጨሱ እንደዋሉ የማታ ማታ ቤታቸው ደርሰው ከልጃቸው ጋር ማውራት ጀመሩ]

  • ዳዲ ምን ሆነሃል?
  • ምን ሆንኩ?
  • ፊትህ?
  • ፊቴ ምን ሆነ?
  • ጥለኸዋል፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • አኩርፈሃል፡፡
  • የሆነ ነገር አበሳጭቶኝ ነው፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • ከሥልጣኔ ተነሳሁ፡፡
  • ሶ ዋት?
  • አያናድድም?
  • ኧረ ዳዲ አትቀልድ፡፡
  • ለምን?
  • ብዙ ነገር ቀለለልህ፡፡
  • ለምሳሌ?
  • ስኳር፡፡
  • ምን?
  • ደም ግፊት፡፡
  • እ. . . ?
  • ኮሌስትሮል፡፡
  • ምንድነው የምትይው?
  • ከበሽታ ዓይነቶች ትገላገላለህ፡፡
  • በቃ እንዲህ ብቻ ነው የምታስቢው?
  • ዋናው ጤና ነው ዳድ፡፡
  • አንቺ ምን አለብሽ?
  • ኧረ ዳድ አታካብድ፡፡
  • ለምንድነው የማላካብደው?
  • ከጤናህ በላይ ሌላም ችግር አለ፡፡
  • የምን ችግር?
  • የአንተ ነገር መጣራት ቢጀመር እኮ ብዙ ችግር ይፈጠራል፡፡
  • ምን ስለሆነ?
  • ዳድ ታውቀዋለህ፡፡
  • ምኑን ነው የማውቀው?
  • እስከ ዛሬ የሠራኸውን፡፡
  • ምን ሠራሁ?
  • ከሠራኸው ይልቅ ያልሠራኸውን ብቆጥር ይቀለኛል፡፡
  • በምን አወቅሽ?
  • ሁሉንም ነገር አውቃለሁ፡፡
  • ለምሳሌ?
  • ሥልጣንህን ለምን ተግባር እንደተጠቀምክበት፡፡
  • እና ከሥልጣን መነሳቴ ትክክል ነበር?
  • ኧረ በእሱ በተገላገልክ?
  • ምን እንዳይመጣ?
  • የሚመጣውን ለመተንበይ ነብይ መሆን አያስፈልግም፡፡
  • እንቺ ልጅ ምን እያልሽ ነው?
  • እኔማ የምልህ ሪያሊቲውን አትሽሽ ነው፡፡
  • እና?
  • እናማ ውጤቱን በፀጋ መቀበል ነው ያለብህ፡፡
  • የምኑን ውጤት?
  • የመባረሩን፡፡
  • ምን አልሽ አንቺ?
  • ማለቴ የመንሳፈፉን፡፡
  • ምን?
  • ገብቶሃል፡፡
  • ባይገባኝስ?
  • አፉን ከፍቶ ይጠብቅሃል፡፡
  • ምንድነው የሚጠብቀኝ?
  • ታውቀዋለህ፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • ሸቤ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

በኦሮሚያ ክልል በስድስት ከተሞች የተዋቀረውን ሸገር ከተማን የማደራጀት ሥራ ተጀመረ

በአዲስ አበባ ዙሪያ በሚገኙ ስድስት ከተሞች የተዋቀረው ሸገር ከተማን...

ኢንቨስተሮች አደጋ ሲገጥማቸው ድጋፍ ማድረግ የሚያስችለው መመርያ ተሻረ

በተፈጥሮና በሰው ሠራሽ አደጋዎች በኢንቨስተሮች ንብረት ላይ አደጋ ቢከሰት፣...

የኦሮሞን ሕዝብ ታሪክ አልባ በማድረግ ታሪክ አይሠራም

በኢተፋ ቀጀላ​​  ከዛሬ ሃምሳ ዓመት ወዲህ ከተፈጠሩት የኦሮሞ ድርጅቶች መካከል ከኢጭአት በስተቀር፣...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በአዲስ አበባ በድምቀት ተከበረ

የአዛርባጃን ኤምባሲ  የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በትላንትናው ዕለት አከበረ። ሰኞ...

የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነት መርህ በኢትዮጵያ

እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሃይማኖት ተቋማት አዎንታዊ ሚና የጎላ...

ሐበሻ ቢራ ባለፈው በጀት ዓመት 310 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ

የአንድ አክሲዮን ሽያጭ ዋጋ 2,900 ብር እንዲሆን ተወስኗል የሐበሻ ቢራ...

የባንኮች ብድር አሰጣጥ ፍትሐዊና ብዙኃኑን ያማከለ እንዲሆን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አሳሰበ

ባንኮች የብድር አገልግሎታቸውን በተቻለ መጠን ፍትሐዊ፣ የብዙኃኑን ተጠቃሚነት ያማከለና...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ አምሽተው ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ‹‹ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ሕዝባችንን እናሻግራለን›› የሚለውን የቴሌቪዥን ዜና ተመልክተው ለብቻቸው ሲስቁ አገኟቸው]

ስልክ እያወራሽ ነበር እንዴ? ኧረ በጭራሽ... ምነው? ታዲያ ምንድነው ብቻሽን የሚያስቅሽ? አይ... በቴሌቪዥኑ የሚቀርበው ነገር ነዋ። ምንድነው? ድሮ ድሮ ዜና ለመስማት ነበር ቴሌቪዥን የምንከፍተው፡፡ አሁንስ? አሁንማ ቀልዱን ተያይዘውታል... አንተ ግን በደህናህ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ስልካቸው ጠራ። ደዋዩ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ኃላፊ እንደሆኑ ሲነገራቸው የስልኩን መነጋገሪያ ተቀበሉ]

ሃሎ፡፡ እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። አንተስ? አስተዳደሩስ? ሕጋዊ ሰውነታችን ተነጥቆ እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ክቡር ሚኒስትር? ለዚህ ጉዳይ እንደደወልክ ገምቻለሁ። ደብዳቤም እኮ ልከናል ክቡር ሚኒስትር፡፡ አዎ። ሁለት ደብዳቤዎች ደርሰውኛል።...

[ክቡር ሚኒስትሩ አየር መንገዱ ወጪ ቆጣቢ የሥራ እንቅስቃሴ በማድረግ የውጭ ምንዛሪ ግኝቱን በሚያሳድግበት ሁኔታ ላይ ከተቋሙ ኃላፊ ጋር እየተወያዩ ነው]

ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ትልቁ ወጪያችን ለነዳጅ ግዥ የሚውለው ነው። ክቡርነትዎ እንደሚገነዘቡት የዩክሬን ጦርነት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በእጅጉ አሻቅቧል። ቢሆንም አገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ችግር ውስጥ...