‹‹ባለሥልጣኑ ያለ ሕጋዊ ውሳኔ በጅምላ የላከልንን የቅጥር ፎርም ማስተናገድ አንችልም›› ዋና ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ጌታቸው አምባዬ
የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ባወጣው የጀማሪ ዓቃቢያነ ሕግ የሥራ ቅጥር ተወዳድረውና የቅጥር ፎርም በመሙላት በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ 54 ጀማሪ ዓቃቢያነ ሕግ፣ በቅርቡ የተቋቋመው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግና የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን እንግልትና በደል ፈጽመውብናል በማለት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የአቤቱታ ደብዳቤ ጻፉ፡፡
ባለሥልጣኑ የካቲት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ለጀማሪ ዓቃቢያነ ሕግ የሥራ ቦታ ማስታወቂያ አውጥቷል፡፡ መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ለተመዝጋቢዎች ፈተና ሰጥቷል፡፡ 54 ተወዳዳሪዎች ማለፋቸውንም ባለሥልጣኑ ሚያዝያ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. አሳውቋል፡፡ የሥራ ቅጥርና የጡረታ ፎርም ከሞሉ በኋላና በተለያዩ ቅርንጫፍ መሥሪያ ቤቶች መመደባቸው ከተነገራቸው በኋላ፣ እስኪሚጠሩ ድረስ እንዲጠብቁ እንደተነገራቸው ቅሬታ አቅራቢዎቹ በአቤቱታቸው አስረድተዋል፡፡
ነገር ግን የጀማሪ ዓቃቢያኑ ቅጥር አዲስ በተቋቋመው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በተላለፈ ትዕዛዝ ለጊዜው ይቁም ተብሏል የሚል መልስ እንደተሰጣቸውም አስረድተዋል፡፡ ባለሥልጣኑ የመሾም ሥልጣን እንደሌለውና ጉዳዩ አዲስ ወደተቋቋመው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ እንደተላለፈ መረጃ እንደተሰጣቸውም አስረድተዋል፡፡
ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በሰጣቸው ምላሽ ባለሥልጣኑ እንዲቀጥር የተሰጠው ኃላፊነት አሥር ሰዎች ብቻ ሆኖ ሳለ 54 ሰዎችን ፎርሞ አስሞልቶ መላኩ አግባብ አለመሆኑን በመግለጽ የተምታታ ምላሽ እየሰጣቸው እንደሚገኝ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በጻፉት ደብዳቤ አስረድተዋል፡፡
ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በሌላ ጊዜ ባለሥልጣኑ የፈጸመበትን የቅጥር ሁኔታ ሕጋዊነት እንዲያብራራለት ጠይቆ ማብራሪያና ሌሎች ሕጋዊ ሰነዶች ተያይዘው ቢላኩለትም፣ ሊያስተናግዳቸው ፈቃደኛ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡
ባለሥልጣኑ በወቅቱ የሰው ኃይል እንደሚያስፈልገው በመግለጽ ቅጥሩ እንዲደረግና ውል እንዲፈጽሙ ያደረገው የዓቃቤ ሕግ ቢሮ ኃላፊ አሁንም አዲስ በተቋቋመው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ውስጥ ሥራውን እየመራ ባለበት ሁኔታ፣ ዋና ጠቅላይ ዋና ዓቃቤ ሕግ አቶ ጌታቸው አምባዬ ‹‹ቅጥር የተፈጸመበት ሁኔታ ተገቢ አይደለም፡፡ ይኼንን ተግባር የፈጸመው አካል (የሥራ ኃላፊ) ማንነት ተጣርቶ እንዲገለጽልን፤›› ማለታቸው ተገቢ እንዳልሆነም አስረድተዋል፡፡
ቅሬታ አቅራቢዎቹ በመንግሥት የመካድ ስሜት እንዲያድርባቸው እንዳደረጋቸውም አክለዋል፡፡ አንዳንዶቹ በ2007 ዓ.ም. የተመረቁና ሥራ የሌላቸው ሲሆኑ፣ አንዳንዶቹ ደግሞ የሥራ ቅጥር ፎርም ስለሞሉ የነበራቸውን ሥራ የለቀቁ መሆናቸውንና የቤተሰብ ሸክም መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሁለቱ የመንግሥት ተቋማት ላደረሱባቸው አላስፈላጊ እንግልት አስፈላጊውን ካሳ ከፍለው የተቀጠሩበት የሥራ መደብ እስካሁን ክፍት በመሆኑ፣ ወደ ሥራ የሚመደቡበትን ሁኔታ እንዲመቻችላቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሚመለከተው አካል ትዕዛዝ እንዲሰጡላቸው ጠይቀዋል፡፡
ሥልጣናቸውን ያላግባብ በመጠቀም ከተጠቀሩ በኋላ እንዳይመደቡ ያደረጉና ከእነሱ መካከል አሥር ዓቃቢያነ ሕግ እንዲቀጠሩ ያደረጉ ኃላፊዎች እንዲጠየቁና ዕርምጃ እንዲወሰድባቸውም ጠይቀዋል፡፡
በቅርቡ በአዋጁ የተቋቋመውና ሥራ የጀመረው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ዋና ዓቃቤ ሕግ አቶ ጌታቸው አምባዬ ለ27 ጀማሪ ዓቃቢያነ ሕግ በጻፉት ደብዳቤ፣ ‹‹ባለሥልጣኑ ያለ ሕጋዊ ውሳኔ በጅምላ የላከልንን የቅጥር ፎርም ማስተናገድ አንችልም፤›› ካሉ በኋላ፣ እንዲቀጥር የታዘዘው አሥር ሰዎች ብቻ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የቅጥር ማስታወቂያ ከማውጣት ጀምሮ ቅጥር እስከመፈጸም የተሄደበት አግባብ ተገቢ አለመሆኑን ጠቁመው፣ ይኼንን የፈጸመ የሥራ ኃላፊ ማንነት ተጣርቶ እንዲገለጽላቸው ባለሥልጣኑን በደብዳቤ መጠየቃቸውን አሳውቀው፣ አቤቱታ አቅራቢዎቹን እንዳልተቀበሏቸው ገልጸውላቸዋል፡፡