በሶማሊያ ሥልጠና በመውሰድና ወደ ኢትዮጵያ በመግባት፣ የአልሽባብን ተልዕኮ ለማስፈጸም ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል የተባሉ ሁለት ተጠርጣሪዎች የሽብር ተግባር ወንጀል ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ እንዳስረዳው ተከሳሾቹ መሐመድ አሊይ ኢብራሂምና መሐሙድ አደም አብዱላሂ የተባሉ ተጠርጣሪዎች ናቸው፡፡ የአልሽባብን ተልዕኮ ለማስፈጸም ከአመራሮች ጋር በተለያዩ ተንቀሳቃሽ ስልኮች በመገናኘት የተለያዩ ትዕዛዞችን መቀበላቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ ጥሩ አቋም ያላቸውን ሰዎች መልምለው ወደ ሶማሊያ እንዲልኩ ለመንቀሳቀሻ ገንዘብ እንደተላከላቸው በክሱ ተገልጿል፡፡
የአልሽባብ ታጣቂ የነበረውና በሽብር ወንጀል ተከሶ ማረሚያ ቤት ሆኖ ክሱን በመከታተል ላይ ከሚገኘው አብዱላሂ አሊይ ገንዘብ ሲላክላቸው ተከሳሾቹ መቀበላቸውንም ዓቃቤ ሕግ በክሱ ጠቅሷል፡፡
በአገር ውስጥ ያለው ሁኔታ የአልሽባብን ዓላማ ለማስፈጸም ጥሩ መሆኑን በመግለጽ፣ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ብቻ መጠየቃቸውንም ክሱ ያስረዳል፡፡ የአልሽባብ አመራሮች ሰዎችን በመመልመል ለሥልጠና ወደ ሶማሊያ እንዲልኩ ሲጠይቋቸው፣ ተከሳሾች ደግሞ አዲስ ሰው መልምሎ ከማሠልጠን ይልቅ ሥልጠና የወሰዱ ሰዎችን ወደ ኢትዮጵያ ማስገባት ቀላል እንደሆነ በመግለጽ ስምምነት ላይ እንደደረሱም በክሱ ተገልጿል፡፡
የአልሽባብ ዓላማን ለማስፈጸም ተደራጅተው መንቀሳቀስ የሚችሉ 75 ሰዎችን ማግኘት እንደሚችሉ፣ የጦር መሣሪያ ስለሌላቸው የጦር መሣሪያ መግዣ ገንዘብ እንዲልክላቸው መጠየቃቸውንም ክሱ ያስረዳል፡፡ ተከሳሾቹ በሶማሊያ ሥልጠናቸውን ጨርሰው ወደ ኢትዮጵያ በመግባት፣ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1ሀ)ን እና የሽብርተኝነት ሕግ አዋጅ ቁጥር 652/2001ን አንቀጽ 4ን ተላልፈው በመገኘታቸው ክስ እንደመሠረተባቸው ዓቃቤ ሕግ ገልጿል፡፡