Monday, May 29, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትር

[ክቡር ሚኒስትሩ ከአማካሪያቸው ጋር እያወሩ ነው]

  • ጠፍተዋል ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እንዴት አልጠፋ?
  • የት ሄደው ነው?
  • በአገር ውስጥ የለህም እንዴ?
  • ኧረ አለሁ፡፡
  • ቲቪ አትከታተልም?
  • ሰሞኑን መብራት ስለሌለ አይቼ አላውቅም፡፡
  • አንተ እኮ አፍራሽ መሆንህን አውቃለሁ፡፡
  • ምን አደረግኩ?
  • መብራት ያለበት ቦታ አትሄድም?
  • አይ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን ሆንክ?
  • መብራት ጠፍቶብኛል ስል አፍራሽ እያሉኝ እንዴት ልንግባባ እንችላለን?
  • ታዲያ ታዳሽ እንድልህ ጠብቀህ ነው?
  • ምንድን ነው እሱ?
  • የስብሰባችን ፍሬ ነዋ፡፡
  • የምን ስብሰባ?
  • ሰሞኑን የጠፋሁት ስብሰባ ገብቼ ነው፡፡
  • ማለት?
  • ለመታደስ ወስነን ነው የወጣነው፡፡
  • መታደስ ሲሉ?
  • ይኸውልህ አገሪቱ በአጠቃላይ መታደስ አለባት፡፡
  • እ…
  • ግን ቢያንስ ከራሳችን መጀመር አለብን፡፡
  • መታደስ ማለት ምን ማለት ነው?
  • ሁሉን ነገር በአዲስ መተካት፡፡
  • እሺ፡፡
  • እና መታደስ በእኔ ይጀምራል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር በአዲስ ሰው ሊቀየሩ ነው እንዴ?
  • የለም የለም፡፡
  • መታደስ ከእኔ ይጀምራል ሲሉኝ ነዋ፡፡
  • እኮ ለምሳሌ የቢሮዬ ቀለም መቀየር አለበት፡፡
  • ምን?
  • ምንጣፌም መቀየር አለበት፡፡
  • ስድስት ወር አልሞላውም እኮ፡፡
  • ግን አዲስ አይደለም፡፡
  • እ…
  • የቢሮዬ ፈርኒቸርም ሙሉ ለሙሉ መቀየር አለበት፡፡
  • ኧረ ክቡር ሚኒስትር?
  • የእኔ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ የመሥሪያ ቤቱ መቀየር አለበት፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር የገባዎት አልመሰለኝም፡፡
  • ምኑ?
  • መታደስ ማለት፡፡
  • ደግሞ ፖለቲካውን ልታስተምረኝ ነው?
  • የተሳሳቱ ስለመሰለኝ ነው፡፡
  • አልጨረስኩም እኮ፡፡
  • እሺ፡፡
  • መኪናዬም የ2017 ሞዴል መሆን አለበት፡፡
  • ምን?
  • ስልኬም አይፎን 7 ፕላስ ይሁንልኝ፡፡
  • ካሉ ምን ይደረጋል?
  • ነገርኩህ በተሃድሶ ሁሉም ነገር መታደስ አለበት፡፡
  • እርስዎ እንዳሉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ስለዚህ ሁሉም ነገር በአዲስ ይለወጥ፡፡
  • ጨረታ ይውጣ?
  • አያስፈልግም፡፡
  • ለምን?
  • ሕዝብ ሰልችቶታል፡፡
  • ምኑ?
  • ቢሮክራሲው!

[ክቡር ሚኒስትሩ ለምሳ ቤት ገብተው ከሚስታቸው ጋር እያወሩ ነው]

  • ዛሬ ቀጠሮ የለህም እንዴ?
  • የምን ቀጠሮ?
  • ለምሳ መጣህ ብዬ ነው፡፡
  • በቃ ተሰብስበን ጨረስን፡፡
  • ለዚያ ነው የመጣኸው?
  • መታደስ አለብን፡፡
  • ምን?
  • በቃ ዋናው መፍትሔ መታደስ ነው፡፡
  • ሰውዬ ይኼን እዚያው ስብሰባህ ላይ አውራ፡፡
  • አይ ቤተሰባችንም መታደስ አለበት፡፡
  • ስማ ልጆቼን ፖለቲካ ውስጥ እንዲገቡ አልፈልግም፡፡
  • ምን ነካሽ? ፖለቲካና ሕይወት እኮ የተሳሰሩ ናቸው፡፡
  • ነገርኩህ ሰውዬ፡፡
  • ለመሆኑ የቤቱን ቀለም አይተሽዋል?
  • አዎ ምን ሆነ?
  • እስቲ እይው፡፡
  • አየሁት እኮ ምንም አልሆነም፡፡
  • አዲስ ቀለም መቀባት አለበት፡፡
  • ከተቀባ እኮ ስድስት ወር አልሞላውም፡፡
  • ነገርኩሽ ይኼ ሶፋ፣ ዳይኒንግ ቴብሉ ምናምን ይቀየር፡፡
  • አብደሃል እንዴ?
  • ምን ሆንሽ?
  • ባለፈው ለሱቅ ፈርኒቸር ሳስጭን እኮ ነው የቤቱ ዕቃ የተገዛው፡፡
  • ቢሆንስ?
  • ሰባት ወሩ ነው ገና፡፡
  • መቀየር አለበት፡፡
  • እ…
  • ግቢውንስ አይተሽዋል?
  • አንደኛውኑ ቤቱ ፈርሶ ይሠራ ለምን አትልም?
  • እርሱም ጥሩ ሐሳብ ነው፡፡
  • ምን?
  • ቤቱ ለምን…
  • ምን?
  • ሙሉ ለሙሉ አይታደስም?
  • ምን ሆኖ?
  • የስብሰባችን ውሳኔ መታደስ አለብን የሚል ነው፡፡
  • መቼም አይገባህም አይደል?
  • ምኑ?
  • ሁሉም ነገር፡፡
  • ማለት?
  • ይታደስ የተባለው እኮ ሌላ ነገር ነው፡፡
  • ማለት?
  • ፖሊሲው፣ አሠራሩ፣ ቢሮክራሲው እኮ ነው ይታደስ የተባለው፡፡
  • ግን እኛም መታደስ አለብን፡፡
  • ከእናንተ የሚታደሰው ዕቃችሁ አይደለማ፡፡
  • ታዲያ ምናችን ነው የሚታደሰው?
  • አዕምሯችሁ!

[የክቡር ሚኒስትሩ ሾፌር ከፍቶታል]

  • ምን ሆነሃል?
  • ምን አደረግኩዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • እኮ ምን ሆንክ?
  • እኔ ለእርስዎ ታዛዥ አይደለሁም?
  • ምንድን ነው የምታወራው?
  • በጠዋት ቢጠሩኝ በሌሊት፣ ቅዳሜ ቢሉ እሑድ እምቢ ብዬ አውቃለሁ?
  • ሰውዬ ጤነኛ ነህ?
  • እኮ የድሃን ጉሮሮ ዘግተው እንቅልፍ ይወስድዎታል?
  • ምንድን ነው የምትቀባጥረው?
  • ከሥራ ሊያባርሩኝ መሆኑን ሰማሁ፡፡
  • ማን ነው የነገረህ?
  • የ2017 ሞዴል መኪና ሊገዙ አይደል?
  • አዎ ልገዛ ነው፡፡
  • የ2017 ሞዴል መኪና ከሆነ ያለሾፌር እንደሚሄድ የቲቪ ማስታወቂያ አይቻለሁ፡፡
  • ኪኪኪ…
  • ምን ያስቅዎታል?
  • ያለሾፌር የሚሄድ መኪና ቢሆን እኔ መቼ ይገባኛል?
  • ምኑ?
  • ቴክኖሎጂው!

[ክቡር ሚኒስትሩ በቅርቡ ካሠሩት ሕንፃ ማኔጀር ጋር እያወሩ ነው]

  • እንዴት ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • አንተ ስንቴ ነው የምነግርህ?
  • ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
  • እዚህ ክቡር ሚኒስትር አትበለኝ አላልኩህም?
  • ማን ልበልዎት ታዲያ?
  • ክቡር ኢንቨስተር፡፡
  • እሺ ክቡር ኢንቨስተር፡፡
  • ስማ ሕንፃው መታደስ አለበት፡፡
  • አዲስ እኮ ነው፡፡
  • በቃ ተሃድሶ ማድረግ እንዳለብን ስለተስማማን፣ በአስቸኳይ ሕንፃው ይታደስ፡፡
  • እሺ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር አትበለኝ አልኩህ እኮ?
  • መታደስ ምናምን ሲሉ ረስቼው ነው፡፡
  • ስለዚህ ተከራዮቹ የቢሯቸውን ቀለም እንዲቀይሩ ንገራቸው፡፡
  • ችግር የለውም፡፡
  • የሚፈልጉትን ቀለም መምረጥ ይችላሉ፤ የማቀርበው ግን እኔ ነኝ፡፡
  • ከየት?
  • ከራሴ ፋብሪካ ነዋ፡፡
  • እሺ እንዳሉ፡፡
  • ፓርቲሽኖቻቸውን ከፈለጉ በአልሙኒየም፣ ከፈለጉ በፒቪሲ፡፡
  • አስተላልፋልሁ ጌታዬ፡፡
  • አቅራቢው ግን እኔ ነኝ፡፡
  • ከየት?
  • ኢምፖርት አደርጋለሁ አይደል እንዴ?
  • እሺ፡፡
  • ፈርኒቸሮቻቸውንም መምረጥ ይችላሉ፣ አቅራቢው ግን…
  • እርስዋ ነዎት!

[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ሚኒስትር ደወሉላቸው]

  • ኧረ ተው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን አደረግኩ ደግሞ?
  • ይኸው ከተማው ውስጥ የፈርኒቸር ቢሉ የአልሙኒየም ግዥ እያጧጧፉት ነው አሉ፡፡
  • ምን ችግር አለው?
  • በቃ በአደባባይ አደረጉት?
  • በሰጣችሁኝ አቅጣጫ እኮ ነው እየተንቀሳቀስኩ ያለሁት፡፡
  • የምን አቅጣጫ?
  • የተሃድሶ አቅጣጫ፡፡
  • አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
  • በቃ ቤቴም፣ ቢሮዬም፣ ሕንፃዬም እየታደሱ ናቸው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ለእርስዎ መታደስ አይደለም መፍትሔው?
  • እና ምንድን ነው?
  • መወገድ!

[የክቡር ሚኒስትሩ አማካሪ ቢሯቸው ገባ]

  • ክቡር ሚኒስትር ሰሙ እንዴ?
  • ስለምኑ?
  • ስለሹም ሽሩ?
  • እኔ ሳልሰማ አንተ እንዴት ሰማህ?
  • አይ እንዳይሰሙ ተፈልጐ ይሆናላ፡፡
  • ማለት?
  • ቴክኖክራቶች ሥልጣን ላይ ሊወጡ ነው አሉ፡፡
  • ይውጡ ምን ችግር አለው?
  • ከዛም ባለፈ ሌላ የሰማሁት ነገር አለ፡፡
  • ምን ሰማህ?
  • ከዳያስፖራም አገር ለመምራት የሚመጡ አሉ ተብሏል፡፡
  • ምን ችግር አለው ታዲያ?
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • እኛም እንሆናለና፡፡
  • ምን?
  • ዳያስፖራ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

ከወለድ ነፃ ባንክ የተሰበሰበውን በመቶ ቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ለምን ሥራ ላይ ማዋል አልተቻለም?

  ባንኮች ከወለድ ነፃ የሚሰበስቡት ተቀማጭ ገንዘብ መጠን ዕድገት እያሳየ...

መንግሥት ባለፈው ዓመት ለማዳበሪያ የደጎመው 15 ቢሊዮን ብር ለአርሶ አደሮች አለመድረሱ ጥያቄ አስነሳ

መንግሥት ለ2014/15 በጀት ዓመት እርሻ በአፈር ማዳበሪያ ላይ ያለውን...

የሁለተኛው አብዮታዊ ሠራዊት ዋና አዛዥ ሜጀር ጄኔራል ሁሴን አህመድ (1930-2015)

ኢትዮጵያ የሁለተኛውን የፋሺስት ጣሊያን ወረራ (1928-1933) በድል ከተወጣች በኋላ...

የመስጅድ ፈረሳን በመቃወም እንዲቆም ለመጠየቅ በተደረገ ሰላማዊ ሠልፍ ላይ የሰው ሕይወት አለፈ

በ56 የፖሊስ አካላትና አጋዥ ኃይሎች ላይ ጉዳት ደርሷል ‹‹በሕዝበ ሙስሊም...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመስቀል አደባባይ የመግቢያ ክፍያ ለምን?

ወጣቶች፣ ሕፃናትና አረጋውያን ሳይቀሩ መንፈሳቸውን የሚያድሱበት እንዲሁም ሐሳባቸውን በነፃነት...

በሕገ መንግሥቱ የተዋቀረው ‹‹የብሔር ፖለቲካ›› እና ‹‹ሥርዓቱ›› ያስከተለው መዘዝና መፍትሔው

(ክፍል አራት) በዓቢዩ ብርሌ (ጌራ) ባለፈው ጽሑፌ (በክፍል ሦስት) አሁን ያለው...

የኢትዮጵያ ኅብረተሰብና የመንግሥት መሪ ምሥል

በበቀለ ሹሜ በ2015 ዓ.ም. መጋቢት ወር ውስጥ ይመስለኛል በ‹ሸገር ካፌ›...

ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ ያደረገው አዋጅ የፍትሐዊነት ጥያቄ አስነሳ

በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ስምንት ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ በማድረግ ተቋማዊና...

ለመጪው ዓመት የሚያስፈልገው 4.3 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ነዳጅ 4.4 ቢሊዮን ዶላር ወጪ ይጠይቃል

ለመጪው 2016 ዓ.ም. ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት ለታቀደው 4.3...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ስልካቸው ጠራ። ደዋዩ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ኃላፊ እንደሆኑ ሲነገራቸው የስልኩን መነጋገሪያ ተቀበሉ]

ሃሎ፡፡ እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። አንተስ? አስተዳደሩስ? ሕጋዊ ሰውነታችን ተነጥቆ እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ክቡር ሚኒስትር? ለዚህ ጉዳይ እንደደወልክ ገምቻለሁ። ደብዳቤም እኮ ልከናል ክቡር ሚኒስትር፡፡ አዎ። ሁለት ደብዳቤዎች ደርሰውኛል።...

[ክቡር ሚኒስትሩ አየር መንገዱ ወጪ ቆጣቢ የሥራ እንቅስቃሴ በማድረግ የውጭ ምንዛሪ ግኝቱን በሚያሳድግበት ሁኔታ ላይ ከተቋሙ ኃላፊ ጋር እየተወያዩ ነው]

ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ትልቁ ወጪያችን ለነዳጅ ግዥ የሚውለው ነው። ክቡርነትዎ እንደሚገነዘቡት የዩክሬን ጦርነት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በእጅጉ አሻቅቧል። ቢሆንም አገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ችግር ውስጥ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የነዳጅ ግብይት በዲጂታል ክፍያ መንገድ ብቻ እንዲፈጸም የተላለፈውን ውሳኔ አተገባበር ላይ ስለተነሱ ቅሬታዎች ከባልደረባቸው ጋር እየተወያዩ ነው]

ክቡር ሚኒስትር አተገባበሩ ጥሩ ቢሆንም፣ ከፍተኛ ወቀሳ እየደረሰብን ነው። ዲጂታል የግብይት ሥርዓቱን ለማስፋፋት በመጣራችን መመስገን ሲገባን እንዴት እንወቀሳለን? የሚገርመው በዲጂታል ክፍያ ላይ የተሰማሩ ኩባንያዎች ናቸው በዋነኛነት...