– ግቡን ያሳኩት ሰባት አገሮች ብቻ ናቸው
ድህነትን ከአፍሪካ ለማጥፋት የተያዙት የምእት ዓመቱ የልማት ግቦች አለመሳካታቸውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) አስታወቀ፡፡ እ.ኤ.አ. እስከ 2015 ድረስ አህጉሪቷን ከድህነትና ከረሃብ ለማላቀቅ፣ የኤችአይቪ ኤድስን ሥርጭት ለመግታትና ሁሉም ሕፃናት የመጀመርያ ደረጃ ትምህርት እንዲያገኙ ለማስቻል ዕቅዱ እ.ኤ.አ. በ2000 የተያዘ ሲሆን፣ አብዛኛዎቹ አገሮችም በተለያዩ ምክንያቶች ዕቅዱን ሳያሳኩ መቅረታቸው ድርጅቱ ጥቅምት 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
በዕቅዱ ከተቀመጡት ግቦች ድህነት ቅነሳ አንዱ ሲሆን፣ ድህነትን መቀነስን በተመለከተ ዕቅዱን ማሳካት የቻሉት ከ54 አገሮች ሰባት ብቻ እንደሆኑም በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡ 12 አገሮች የድህነት ቅነሳን ግብ ለማሳካት ጫፍ እንደደረሱ፣ 11 ደግሞ ቀድሞ ከነበሩበት ደረጃ ወደኋላ መቅረታቸው በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ ቦትስዋና፣ ካሜሩን፣ አይቮሪኮስት፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኦፍ ኮንጎ፣ ጂቡቲ፣ ኢትዮጵያና ኡጋንዳም የተሻለ አፈጻጸም ማሳየታቸው የተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን በሪፖርቱ አካቷል፡፡
እየታየ ያለው ለውጥ ከሚጠበቀው በታች መሆኑ አፍሪካን ከሁሉም የዓለም ክፍሎች በተለየ የድሆች መናኸሪያ አድርጓታል፡፡ በአፍሪካም 110 ሚሊዮን ሰዎች በከፍተኛ ድህነት ውስጥ ይገኛሉ፡፡
በሪፖርቱ መሠረት፣ በአብዛኛዎቹ የአፍሪካ አገሮች ለተመዘገበው አሉታዊ ውጤት መንስኤ ተብለው ከተቀመጡት፣ በውስን የልማት ሴክተሮች ላይ ብቻ ማተኮርና አህጉሪቱ ያላትን ከፍተኛ የወጣት ኃይል የሚያሳትፉ ኢንዱስትሪዎች አለመኖር ይገኙበታል፡፡
የምእት ዓመቱ ዕቅድ ከተጠናቀቀበት 2015 በኋላ 17 የልማት ቅዶችን ያካተተ ግብ ይፋ ሆኗል፡፡ ይሁን እንጂ በአህጉሪቱ ጠንካራ የሆነ ተቋማዊ መዋቅር አለመኖር፣ በሚሠሩ ሥራዎች ዙሪያ በቂ ክትትል አለማድረግና የተጠናከረ የመረጃ ሥርዓት አለመኖር በሁለተኛው ዙር የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እንቅፋት እንደሚሆን በሪፖርቱ ተብራርቷል፡፡