ከሠላሳ ዓመታት በፊት በጥር 1979 ዓ.ም.፣ ሦስቱን የኢትዮጵያ ሙዚቃ ቤተሰብ አባላት ያገናኘች ቅጽበት፡፡ በግራ ፍራንሲስ ፋልሴቶ፣ ‹‹የትዝታው ንጉሥ›› ማህሙድ አሕመድና የቀድሞው ታንጎ ሙዚቃ ቤት ባለቤት አሊ ታንጎ ይታያሉ፡፡
*******
ኧረ በፈጠረሽ!
ንግግር አብቅቼ አፌን ተለጉሜ፤
ንግግር አብቅተሽ አልናገር ብለሽ፤
ስለተኮራረፍን፣
ፀሐይ ተሰበረች አላበራም ብላ፡፡
ጨረቃም ጠፋችው ደንግጣ ኮብልላ፤
ዳግም ዳቦ ላትጥል ተፈጥማ ምላ፡፡
እኔና አንቺ ብቻ አለነው ከዚሁ፤
አኩርፈሽ፤ አኩርፌ፤
ኩርፍርፍ ብለን፤
ፍጥረት እስኪደንቀው የእኛ እንደዚህ መሆን፡፡
ኧረ በፈጠረሽ!
አን. . . ዴ ሳቅ በይና፤
ፀሐይ ብልጭ ትበል፤
ሕይወት ትስረፅና!
(1965 ዓ.ም.)
ዮናስ አድማሱ ‹‹ጉራማይሌ›› (2006)
******
ዛሬ ነገ ማለትና ጤና
በቫንኩቨር ሳን ጋዜጣ ላይ የተጠቀሰ አንድ ጥናት ‹‹ዛሬ ነገ እያሉ ሥራን ማዘግየት ሊያሳምም ይችላል›› ይላል፡፡ በቅርቡ በቶሮንቶ፣ ካናዳ በተደረገ የአሜሪካ ሥነ አእምሮ ማኅበር ጉባኤ ላይ 200 የሚያክሉ የካናዳ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ላይ የተደረገ የጥናት ውጤት ‹‹መሥራት ያለባቸውን ሥራ ዛሬ ነገ እያሉ የሚያዘገዩ ሰዎች በዚህ ድርጊታቸው ምክንያት በራሳቸው ላይ ከፍተኛ የሆነ ጭነት ስለሚያስከትሉ ከሌሎቹ የበለጠ ከጭንቀት ጋር ተዛምዶ ባላቸው በሽታዎች እንደሚጠቁ አረጋግጧል፡፡ … የፈተናው ቀን እየቀረበ ሲመጣ በዛሬ ነገ ባዮቹ ላይ የሚደርሰው ውጥረት እያየለ ይሄዳል፡፡ በግድ የለሽነት ያሳለፉት ጊዜ በራስ ምታት፣ በወገብ በሽታ፣ በጉንፋን፣ በእንቅልፍ እጦትና በተለያዩ አለርጂዎች ይተካል፡፡ ከሌሎቹ የበለጠ በመተንፈሻ አካላት ችግሮች፣ በተለያዩ ኢንፌክሽኖችና ራስ ምታቶች ተጠቅተዋል፡፡››
- ንቁ መጽሔት (ሚያዝያ 2002)
*******
ይከፍላላ!
ሦስት ጓደኛሞች ምግብ ሊበሉ ሆቴል ይገቡና ሁለቱ እጃቸውን ሲታጠቡ፣ ጋብሮቩ ውድ የሆኑትን የምግብ ዓይነቶች ከዝርዝሩ ላይ በፍጥነት ይሰርዝ ጀመር፡፡
የሆቴሉ ባለቤት፣ በድርጊቱ ተገርመው አፍጠው ሲመለከቱትም ‹‹ሒሳቡን የምከፍለው እኔ ነኛ!›› አላቸው፡፡
*******
ጠቃሚ ትምህርት
ቀድሞ የነበረበትን ዕዳ ያልከፈለው የአያ ሚንዮ ጐረቤት ሁለተኛ ብድር ሊጠይቅ ይሄዳል፡፡ ሽማግሌው ሚንዮም በትህትና ተቀብለውት ችግሩን ካዳመጡ በኋላ፣ እፊት ለፊቱ ያለውን ጠረጴዛ እያመለከቱ ከመሳቢያው ውስጥ የሚፈልገውን ያህል ገንዘብ እንዲወስድ ይፈቅዱለታል፡፡
ባለ ዕዳው መሳቢያውን ይጐረጉርና ‹‹አያ ሚንዮ! ለምን ይቀልዱብኛል? መሳቢያው ውስጥ ሰባራ ሳንቲም እንኳ የለም’ኮ!›› ይላቸዋል፡፡
ይኼኔ አዛውንቱ ሚንዮ፣ ‹‹አዬ ልጄ፣ የመጀመሪያውን ዕዳህን ሳትከፍል እንዴት ሰባራ ሳንቲም እኔ ዘንድ ሊኖር ይችላል ብለህ ነው?›› ሲሉ መለሱለት፡፡
- አረፈዓይኔ ሐጎስ፣ ‹‹ቀልዶች ከጋብሮቮ ምድር›› (1979)
*******
‹‹ለሰው ሞት አነሰው››
እባብ በክረምት ውኃ ሞልቶበት ዳር ዳሩን ሲንቀዋለል አንድ ሰው መጣ፤ እባቡም ሰውዬ እባክህ አሻገረኝ ብሎ ለመነው፡፡ ያም ሰው እጅ የለህ እግር የለህ ምንህን ይዤ ነው የማሻግርህ አለው፡፡ እባቡም ፈቃድህስ ከሆነ ራስህ ላይ ጠምጥመኝ ቢለው ጠምጥሞ አሻገረው፡፡ ካሻገረውም በኋላ በል ውረድልኛ ቢለው እምቢ አልወርድም አለ፡፡ ወደ ዳኞች (አራዊትም) ሁሉ ሂዶ ቢከሰው ዳኞቹ (አራዊቶቹ) በገዛ እጅህ እባብ ራስሀ ላይ ጠምጥመህ እያሉ ፈረዱበት፡፡
በመጨረሻውም በቀበሮ ዳኝነት ከስሰው ቀበሮዋም እባብን ምድር ወርደህ በግራ ቆመህ ሥርዓት ለብሰህ ተነጋገር አለችው፤ እሱም ተተረተረና ዱብ አለ፡፡ ከዚህም በኋላ ቀበሮዋን ሰውዬው እህ አላት እሷም ሰው በትር ይዞ ቆሞ እባብ እምድር ተጋድሞ ብትለው ራስ ራሱን ብሎ ቀጥቅጦ ገደለው፡፡ ችሎትም ሲመለስ ብድሯን ለመክፈል ማታ በግ አመጣልሻለሁና ቤትሽን አሳዪኝ አላት እሷም አስከትላው ሂዳ ቤቷን አይቶ ተመለሰ፡፡ ማታም ውሻውን አስከትሎ ሂዶ ከበር አፏ ቁሞ እንኰይ ቀበሩት ብቅ በዪ አላት በግ ይዞልኝ መጥቶ ይሆናል አለችና ብቅ ብትል ያዠ ኩቲ ብሎ ውሻውን ለቀቀባት፤ እሷም ሰው ሰው ሰው ለሰው ሞት አነሰው እያለች ወደ ቤቷ ተመለሰች፡፡
- ደስታ ተክለወልድ ‹‹ገበታዋርያ›› (1926)
**********
ወርቃማው ንስር ነዋሪዎችን አሸበረ
እጅግ በጣም ትልቅ የሆነውና ክንፉ እንኳን ስድስት ጫማ የሚረዝመው ወርቃማ ንስር በአንድ የእንግሊዝ መንደር በማምለጡ ነዋሪዎች እንዲጠነቀቁ ፖሊስ አስታወቀ፡፡ እግሮቹ ላይና ሌሎች አካላዊ ምልክቶችን በመጥቀስ ፖሊስ ነዋሪዎች ይህን ንስር ካዩ ራሳቸውን በመሸፈን እንዲከላከሉና ጥቆማቸውንም ለፖሊስ እንዲሰጡ ተጠይቋል፡፡
*******
ሕፃኑ ላይ የፈሳው ፍርድ ቤት ቀረበ
አንድ ሕፃን ልጅ ፊት ላይ የፈሳው ግሬ ማኬንዚ የተባለ የ22 ዓመት ወጣት ፍርድ ቤት መቅረቡን ሜትሮ ዘገበ፡፡ ሕፃኑ እንደገለጸው ወጣቱ መቀመጫውን ከፊቱ ላይ በመደቀን ፈስቶበታል፡፡ ለምን እንዲህ ታደርጋለህ? ሲለውም መጥፎ መልስ መልሶለታል፡፡ ወጣቱ ድርጊቱን የፈጸመው እሱ ላይ ብቻ ሳይሆን ሌላ ሕፃን ላይም ነው፡፡ ወጣቱ ማኬንዚ ሕፃንን በትራስ የማፈን ክስም እንደሚቀርብበት ተጠቁሟል፡፡ ወጣቱ የቀረቡበትን ውንጀላዎች የካደ ሲሆን፣ ጉዳዩ አሁንም በፍርድ ሒደት ላይ ነው፡፡