በያመቱ ጥቅምት ወር ሁለተኛ ሰኞ ላይ የሚውለው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀን ጥቅምት 7 ቀን 2009 ዓ.ም. በተለያዩ አካባቢዎች ተከብሯል፡፡ ለዘጠነኛ ጊዜ የተከበረው ‹‹ሰንደቅ ዓላማችን የሉዓላዊነት መገለጫ፤ በብዙኃነት ላይ የተመሠረተው አንድነታችን ዓርማ ነው፤›› በሚል መሪ ቃል ነው፡፡ ፎቶዎቹ (በግራ) አምና ክብረ በዓሉ ሲከበር የአዲስ አበባ ታዳጊዎች ስካውት አባላት በሰልፍ ትርዒት ይታያሉ፡፡ (በቀኝ) ዘንድሮ በመዲናይቱ ለበዓሉ መግለጫ ከተሰቀሉት ሰንደቅ ዓላማዎች አንዱ ይታያል፡፡
*******
አባዜ
ሲወርድ ሲዋረድ፣
ከጥንት የወረስነው፣
የወል ባህሪያችን፣
መታወቂያ ያረግነው፣
አልላቀቅ ያለን፣
ዘልቆ ከደማችን፣
እጅግ ለየት ይላል፣
ምግብ አሠራራችን፡፡
እንጨቱን ጨማምረን፣
እሳቱን አብዝተን፣
እልፍ ሰዓት ያህል፣
ታግሰን ቀቅለን፣
ከምግቡ ሚገኘው፣
እንዳይሆን ለገላ፣
ልማድ አድርጎብን
አቃጥለን፣ ገለን ነው፣
ምግብ የምንበላ፡፡
********************
2005 አክሱም
ፍሥሐ ተክሉ ‹‹የግዛት ዓለም›› (2008)
********
‹‹ብሽቅ!››
ኤደንብራ ውስጥ የሚገኙ የዊቨርሊ ደረጃዎች ነፋስ ይበዛባቸዋል፡፡ ከዓመት ዓመት ያለማቋረጥ ኃይለኛ ነፋስ እንደነፈሰ ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አንዷ ሴት ወይዘሮ ባቡር ልትሳፈር ተቻኩላ ደረጃዎቹን እየሮጠች ወጥታ ስትጨርስ ነፋሱ ገለባት፡፡ ተናዳ ያያት ሰው መኖሩን ለማወቅ ዞር ብላ ስትመለከት አንዱ ከታች ያጮልቃል፡፡
‹‹ወደ ሥራህ ብትሄድ አይሻልህም?!››አለችው በተግሳጽ፡፡
‹‹እሺ፣ እሄዳለሁ፤ ግን ትላንትም የለበሽው ይህንኑ የውስጥ ሱሪ ነበር አይደል?›› አላት፡፡
********
አንበሳን ማን ይቀድማል?
ስኮትላንዳዊውና እንግሊዛዊው ዱር ውስጥ እየተንሸራሸሩ ሳሉ አንበሳ ከፊት ለፊታቸው ሲመጣ አዩ፡፡ ይኼኔ ስኮትላንዳዊው ያደረገውን ትልቅ የቦት ጫማ በፍጥነት አውልቆ ቀለል ያለ ሸራ ጫማ ማጥለቅ ጀመረ፡፡
‹‹ይኼ ምን ይጠቅምሃል፣ ወዳጄ?›› አለ እንግሊዛዊው በመገረም፤ ‹‹መቼስ አንበሳን ሮጠህ ማምለጥ አትችልም?››
‹‹ልክ ነህ፣ እሱንማ አልቀድመውም፡፡ አንተን ግን እቀድምሃለሁ፤››
- አረፈዓይኔ ሐጐስ ‹‹የስኮትላንዳውያን ቀልዶች›› (2005)
*********
«እርኩምን ሊበሉ ጅግራ ነው አሉ»
ራስን መደለል በእንስሳትም መካከል በጥቂቶች ላይ የተደረገ ሆኖ፤ በምሳሌ ዓይነት እንደ ተረት የሚነገር ቃል እናገኛለን፡፡ ተረቱም እንደሚከተለው ነው፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት የተራበች ጦጣ ባንድ የወይን ሥፍራ አጠገብ ስታልፍ ቁመቷ ከማይደርስበትና ዘልላም ልታወርደው ከማይቻላት አስቸጋሪ ከሆነ ካንድ ከፍተኛ ሥፍራ ላይ በስሎ መልኩ ብቻ እንኳን የሚያስጎመጅ አንድ የወይን ዘለላ ተንዠርጐ ተመለከተች፡፡ ለማውረድም ሞክራ ሳይሆንላት ስለ ቀረ ፥ ልቧ እያወቀ ራሷን በማታለል ፥ ‹‹ወይኑ እኮ እንደሆን በእውነቱ ገና አልበሰለም፤ ለጊዜው የደረሰ መሰለ እንጂ ጥሬ ነው፡፡ ስለዚህ ላንድ ጥሬ ለሆነ ላልበሰለ ወይን ይህን ያኸል ምን ያደክመኛል? የሱን ዓይነት ከሌላስ ሥፍራ አጥቼ ነውን?›› በማለት ራሷን ደልላ ይኸንኑ ቃል በመደጋገም ራሷን እየነቀነቀች ነገሩን አኳስሳ ትታው ሄደች ይባላል፡፡
እንደዚሁም አንዲት ሰጐን አንድ አዳኝ ጠመንጃውን ደግኖ ሊተኩስባት ሲያነፃፅርባት እያየች፤ ሮጣ ሕይወቷን ለማዳን ከመሞከር ይልቅ፤ እዚያው ሁና ተደፍታ ዓይኖቹዋ እንዳያዩ ወደታች አቀርቅራ፤ ‹‹የት አለና ነው አዳኝ? ቢኖር ለምን አላያውም? ይኸው ምንም ነገር አላይም›› እያለች በሐሳቧ ራሷን ደልላ ከዚያው አንገቷን ደፍታ ተቀመጠች ይባላል፡፡ ነገር ግን እውነቱ ጦጣዋም ሆነች ይህችኛዋ አውሬ፤ ሁለቱም ራሳቸውን እንዲህ አድርገው ቢደልሉትም፤ ወይኑን የበሰለ መሆኑ፤ አዳኙም ከዚያ ተገኝቶ ጠመንጃውን የደገነ መሆኑ የማይቀርና የነርሱ ክህደት ነገሩን ለውጦ ሐሰት ሊያደርገው አለመቻሉ የተረጋገጠ ነው፡፡
እንግዲህ በዚህ ታሪክ ውስጥ ጦጣይቱና ሰጎኗ ራሳቸውን በመደለል ያደረጉትን ሙከራ እንመለከታለን፡፡ ሰውም ልክ እንደነዚሁ እንስሳት ይኸንኑ ዓይነት ተግባር በራሱ ላይ ሲፈጽም ይገኛል፡፡ ለዚያውም ደግሞ እነዚህ እንስሳት ይህንን ነገር ፈጽመውት ነው ማለት ሳይሆን፤ ከሰዎች ዘንድ የሚደረግ መሆኑን በምሳሌ መንገድ ለመግለጽና ለማስተማር ያኸል የሚነገር ነው፡፡ የቀድሞ አባቶቻችን፤ ሰው ያልኾነውን ነው በማለት ራሱን የሚደልል ከንቱ መኾኑን ተመልክተው «እርኩምን ሊበሉ፤ ጅግራ ነው አሉ» ብለው ይተርኩት የነበረ ቃልም ይገኛል፡፡
ስለዚህ ሰው ራሱን በራሱ እንደ ሕፃን ልጅ በመደለል በሐሳቡ የተመኘውን ነገር ሁሉ ሲፈጽም መታየቱ የቆየ እንጂ፤ አዲስ አይደለም፡፡
- የማነ ገብረማርያም (ዶ/ር) ‹‹የፍልስፍና ትምህርት ፩ኛ›› (1955)
*******
በሚሳይል ቅርፅ የተሠራው የሕፃናት አልጋ
እ.ኤ.አ. በ2014 በምሥራቅ ዩክሬን ተመትቶ በወደቀው የማሌዥያው አውሮፕላን ኤም ኤች17 አውሮፕላን በመታው ሚሳይል ቅርፅ ሩሲያ ውስጥ የተሠራው የሕፃናት አልጋ አነጋገሪ ሆነ፡፡ ሩሲያ ሴንት ፒተርስበርግ ውስጥ የሚገኘው ኩባንያ የዚህ ዓይነቱን አውሮፕላን በመሥራቱ የአገሪቱ ዜጎች እየተበሳጩ በድረ ገጾች አስተያየታቸውን እየሰጡ እንደሆነ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ አልጋው በ176 የአሜሪካ ዶላር የሚሸጥ ሲሆን፣ ቀይ ኮከብና የሩሲያ ሰንደቅ ዓላማ አለበት፡፡ በሌላ በኩል የሚሳይሉን ስም ከማንገብ ይልቅ መከላከልን የሚያመላክት ሌላ ቃል ይዟል፡፡ አልጋውን ያመረተው ኩባንያ ኃላፊ አልጋውን በሚሳይል ቅርፅ የሠሩት ሰዎች ነገሮችን አያይዘው እንዲጨነቁ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡