– የአቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስ ባለቤት የተፈቀደላቸው ዋስትና ታገደ
በእነ አቶ መላኩ ፈንታ የክስ መዝገብ በተከሰሱበት የሙስና ወንጀል እንዲከላከሉ የፍርድ ውሳኔ የተሰጠባቸው የአዲስ ልብ ሕክምና ማዕከል ባለቤት ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን የጤና ሁኔታ አጣርቶ ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያቀርብ፣ የማረሚያ ቤት አስተዳደር በፍርድ ቤት የመጨረሻ ትዕዛዝ ተሰጠው፡፡
ቀደም ብሎ የስኳርና የደም ግፊት ሕመምተኛ መሆናቸው የተገለጸው ዶ/ር ፍቅሩ፣ የግራ ሳንባቸው ሙሉ በሙሉ ሥራ በማቆሙ በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ተኝተው በመታከም ላይ መሆናቸው ተገልጿል፡፡
በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በተደረገላቸው ምርመራ ከፍተኛ ሕክምና እንደሚያስፈልጋቸው በመረጋገጡ የሆስፒታሉ የሕክምና ቦርድ ወደ ውጭ ሄደው እንዲታከሙ ቢወስንም፣ ማረሚያ ቤትና ፍርድ ቤት መግባባት ስላልቻሉ የመጨረሻ ውሳኔ ተሰጥቶ ውጤቱን ማወቅ እንዳልተቻለ ቤተሰቦቻቸውና ጠበቃቸው ተናግረዋል፡፡
ክሳቸውን እያየው ለሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 15ኛ ወንጀል ችሎት በተደጋጋሚ አቤቱታ ያቀረቡት የዶ/ር ፍቅሩ ጠበቃ፣ ሕይወትን ከማትረፍ አንፃር እንዲታይላቸው ጠይቀው ነበር፡፡
የጠበቃውን ማመልከቻ ያዳመጠው ፍርድ ቤቱ፣ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ዶ/ር ፍቅሩን ጥቅምት 2 ቀን 2009 ዓ.ም. በራሱ ወይም በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል አምቡላንስ ፍርድ ቤት እንዲያቀርብ ያዘዘ ቢሆንም፣ በዕለቱ ሳይቀርቡ ቀርተዋል፡፡ ማረሚያ ቤቱ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ እንደማያከብር የዶ/ር ፍቅሩ ጠበቃ ገልጸው፣ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ የሚያከብር ቢሆን ኖሮ ዶ/ር ፍቅሩ የተኙበትን ሆስፒታል አነጋግሮ ማቅረብ ይችል እንደነበር አስረድተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ኮሚሽን አቋቁሞ እንዲያጣራ ወይም ችሎቱ ታማሚው ወደተኙበት ሆስፒታል ሄዶ እንዲያረጋግጥ ወይም ማረሚያ ቤቱ ከሐኪሞች ጋር ተነጋግሮ በዕለቱ ከሰዓት በኋላ እንዲያቀርብ እንዲታዘዝላቸው ጠይቀዋል፡፡
የማረሚያ ቤቱ ተወካይ በሰጡት ምላሽ እንደተናገሩት፣ አንድ እስረኛ በሪፈራል ሆስፒታል እንዲታከም ከተወሰነ ታክሞ እንዲመለስ ከማድረግ ውጪ በተፈለገ ጊዜ ይምጣ ወይም አይምጣ የሚል ስምምነት የለም፡፡ ዶ/ር ፍቅሩ ጠበቆቻቸው እንደሚሉት ሳይሆን ጤንነታቸው መሻሻል የሚታይበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገኖች ክርክር ካዳመጠ በኋላ፣ የዶ/ር ፍቅሩን ጤንነት ሁኔታ የማረሚያ ቤቱ የጤና ባለሙያዎች ጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሄደው በማረጋገጥ፣ ታካሚው ፍርድ ቤት መቅረብ የማይችሉ ከሆነ ከሚመለከተው ሐኪም በማኅተም የተረጋገጠ ማስረጃ ይዘው ለመጨረሻ ጊዜ ጥቅምት 11 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በተመሳሳይ የክስ መዝገብ በ75,000 ብር ዋስትና ከእስር እንዲፈቱ ተፈቅዶላቸው የነበሩት የአቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስ ባለቤት ኮሎኔል ሃይማኖት ተስፋዬ፣ ይግባኝ ስለተባለባቸው የዋስትና መብታቸው ታግዷል፡፡ የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ፍርድ ቤቱ የሰጠውን የዋስትና መብት ፈቃድ በመቃወም፣ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ይግባኝ ማለቱን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ እስከ ጥቅምት 7 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ የተፈቀደውን ዋስትና ማስከልከሉን የሚገልጽ የዕግድ ትዕዛዝ ካላቀረበ ዋስትናው ፀንቶ ከእስር እንደሚፈቱ ችሎቱ አስረድቷል፡፡