መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም. ኢሬቻ በዓል ለማክበር ተገኝተው ሕይወታቸውን ያጡ ዜጎችን በሚመለከት ኃላፊነቱን መንግሥት መውሰድ አለበት በማለት ሲከራከሩ የነበሩት አንድ ጦማሪና ሁለት ጓደኞቹ፣ ወንጀል በመፈጸም ተጠርጥረው ከታሰሩ በኋላ ዓርብ መስከረም 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በዋስ እንዲለቀቁ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
ዞን ዘጠኝ በመባል ከሚጠሩት ጦማሪያን አንዱ የሆነው ናትናኤል ፈለቀ፣ ከጓደኞቹ ጋር ሆኖ መስከረም 25 ቀን 2009 ዓ.ም. በላሊበላ ሬስቶራንት ሻይ እየጠጡ፣ በቢሾፍቱ ኢሬቻ በዓል ለማክበር ሄደው መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም. ስለሞቱ ወገኖች ይወያዩ እንደነበር ጠበቃው አቶ አመሐ መኮንን ተናግረዋል፡፡
ከ50 በላይ ዜጎች ሕይወታቸው ስላለፈበት ጉዳይ ይወያዩ የነበሩት ናትናኤልና ጓደኞቹ፣ በኢሬቻ በተከሰተው አደጋ ኃላፊነቱን መውሰድ ያለበት መንግሥት መሆኑን በመጠቆም ድምፃቸውን ከፍ አድርገው መነጋገራቸው፣ ሕዝቡን ለአመፅ ለማነሳሳት ወይም እንዲነሳ ለማድረግ መሆኑን በጠረጠሩ የፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር ውለው እንደታሰሩም ተገልጿል፡፡
መስከረም 26 ቀን 2005 ዓ.ም. በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቂርቆስ ምድብ ችሎት የቀረቡት እነ ናትናኤል ፖሊስ ጠርጥሮ እንዲታሰሩ ያደረጋቸው ያለበቂ ምክንያት መሆኑን፣ በቂ ምክንያት አለ ቢባል እንኳን ዋስትና እንደማያስከለክል በመግለጽ በጠበቃቸው አማካይነት ባቀረቡት ክርክር፣ ፍርድ ቤቱ እያንዳንዳቸው በ5,000 ብር ዋስትና እንዲለቀቁና ከአገር እንዳይወጡ ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት እንዲጻፍ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡
የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ የተቃወመው ፖሊስ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ስምንተኛ ወንጀል ችሎት ይግባኝ በማለቱ በዕለቱ ሳይፈቱ ቀርተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ መስከረም 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ከቀትር በኋላ የፖሊስን ይግባኝ መርምሮ፣ ፖሊስ በይግባኙ የሥር ፍርድ ቤትን ብይን ሊያስቀለብስ የሚችል ነገር እንዳላቀረበ በማስታወቅ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅ የተሰጠውን ትዕዛዝ አፅንቶታል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ በሽብር ወንጀል ክስ ተመሥርቶበት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በነፃ ቢያሰናብተውም፣ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ይግባኝ በመጠየቁና ይግባኙም ተቀባይነት በማግኘቱ ጉዳዩ በጠቅላይ ፍርድ ቤት እየታየ ይገኛል፡፡