‹‹የፀጥታ ኃይሎቻችን ፀጥታ እንዲከበር ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ያደረጉበት፣ ምንም ዓይነት የጥይት ድምፅ ያልተሰማበት መንግሥትም ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደረገበት ሒደት ነው፡፡ ሕዝቡን ለመጠበቅ የፀጥታ ኃይሎች ላደረጉት ከፍተኛ ጥረት በመንግሥት ስም ምስጋና ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡››
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፣ መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም. በቢሾፍቱ ከተማ ሊከበር በነበረው የኢሬቻ በዓል ሥነ ሥርዓት ላይ በተነሳው ተቃውሞ፣ የበርካታ ሰዎች ሕይወት መጥፋቱን ተከትሎ ባስተላለፉት የሐዘን መግለጫ መልዕክታቸው ላይ የተናገሩት፡፡ የኢሬቻ ክብረ በዓል የኦሮሞ ብሔር አባላት ለፈጣሪያቸው ዋቃ ምስጋና የሚያቀርቡበት ነው፡፡ በተለይም በሀሮ አርሰዲ (አርሰዲ ሐይቅ) ሕዝቡ በአባ ገዳዎች እየተመራ ርጥብ ሳርና አደይ አበባ በሐይቁ ዳርቻ በማስቀመጥ ከክረምት ወደ ጥቢው ላሸጋገረው አምላክ ምስጋና የሚያቀርብበት ቢሆንም በዕለቱ በተፈጠረው ተቃውሞ በዓሉ ሳይከበር ከመቅረቱም በላይ ከ52 በላይ ሕይወትን ቀጥፏል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በሬዲዮና በቴሌቪዥን ባስተላለፉት መልዕክትም ይህ ድርጊት በጭራሽ ሊከናወን የማይገባው ነው ሲሉም አክለዋል፡፡