የኢትዮጵያ መንግሥትን የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት አያያዝ ሁኔታን በተመለከተ የተለያዩ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ቡድኖችና አገሮች፣ በተለያዩ ወቅቶች የተለያዩ ይዘት ያላቸውን ሪፖርቶች ይፋ ያደርጋሉ፡፡
በተለይ ከምርጫ 97 ወዲህ ባሉት ዓመታት የየተቋማቱ ሪፖርቶችና መንግሥት ለሪፖርቶቹ የሚሰጠው ምላሽ በተለያዩ ወቅቶች የመገናኛ ብዙኃንን ትኩረት ስቦ መቆየቱ ይታወሳል፡፡
ከእነዚህ በተደጋጋሚ ከወጡ ሪፖርቶች መካከል ግን ኤችአር 2003 የተባለውና በአሜሪካ የኮንግሬስ አባል በነበሩት ዶናልድ ፔይንና ክሪስ ስሚዝ ተረቆ ለአሜሪካ ሕግ አውጭ ምክር ቤት ቀርቦ የነበረው ረቂቅ፣ ረዥም ሒደቶችን ያለፈና በኢትዮጵያ መንግሥትም ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት ሕግ ሆኖ እንዳይፀድቅ ከፍተኛ ሥራ የሠራበት እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡
እ.ኤ.አ. በ2007 ቀርቦ የነበረው ይህ ረቂቅ ሕግ ‹‹Ethiopia Democracy and Accountability Act of 2007›› የሚባል ሲሆን፣ በአገሪቱ የሰብዓዊ መብት እንዲስፋፋና እንዲጠናከር፣ እንዲሁም ዴሞክራሲያዊ ተቋማት እንዲጠናከሩ ግፊት ለማድረግ የቀረበ ረቂቅ ነበር፡፡
እነዚህንም ነገሮች ለማሳካት ይቻለው ዘንድ ረቂቁ የአሜሪካ ኮንግረስ ከደኅንነት ጋር የተያያዙ ድጋፎችን እንዲቆጣጠርና በወቅቱ ተፈጥሮ ከነበረው አለመረጋጋት ጋር እጃቸው ያለበት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የሚጠይቅ ረቂቅ ነበር፡፡
የእዚህን ረቂቅ ሕግ ለመቃወምና ከታለመለት ግብ እንዳይደርስም የኢትዮጵያ መንግሥት መቀመጫውን አሜሪካ ያደረገውን ዲኤልኤ ፓይፐር የተሰኘ ዓለም አቀፍ የሕግ ተቋም በመቅጠር፣ ረቂቁ ከግቡ እንዳይደርስና የተዘጋጁት ማዕቀቦች ተፈጻሚ እንደሆኑ ማድረግ ችሎ ነበር፡፡
በተመሳሳይ በቅርቡ ለአሜሪካ ሕግ አውጪ ምክር ቤት በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት አያያዝና ዴሞክራሲ ዙሪያ የሚያጠነጥን አዲስ ረቂቅ ቀርቧል፡፡
ይህን ረቂቅ ሐሳብ የቀረበው በአፍሪካ ጉዳዮች ንዑስ ቋሚ ኮሚቴ ሊቀመንበርና ኤችአር 2003ን ካቀረቡትና እንዲፀድቅ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ ከነበሩት መካከል ክሪስ ስሚዝ አማካይነት ነው፡፡
ይህ ኤችአር 2016 የተባለው ረቂቅ በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት እንዲከበር የሚጠይቅና በእስር ላይ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ተማሪዎችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች በአስቸኳይ ከእስር እንዲለቀቁ የሚጠይቅ ነው፡፡
ይህ ረቂቅ ሕግ ዋነኛ ዓላማው ለሰብዓዊ መብት መከበር የሚሠራና ሁሉን አቀፍ የሆነ መንግሥት ምሥረታን መደገፍና ማበረታታት እንደሆነ ይገልጻል፡፡ በአገሪቱ ተቃውሞ የሚያደርጉ ዜጎች ላይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የሚወስዱትን የኃይል ዕርምጃ በፅኑ ይኮንናል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች በፀጥታ ኃይሎች ስለተገደሉት ሰዎች ተዓማኒነት ያለው ምርመራ እንዲካሄድና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) በኢትዮጵያ ስላለው የሰብዓዊ መብት አያያዝ ሁኔታ ምርመራ አድርጐ ሪፖርት እንዲያቀርብ የሚጠይቅ ነው፡፡
የረቂቁ አጠቃላይ ይዘት
አዲሱ ረቂቅ እ.ኤ.አ. በመጋቢት 2016 በአዲስ አበባ በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ፊት ለፊት ተቃውሞ ያሰሙ 20 የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መታሰራቸውን፣ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ሌሎች 21 የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላት በፀረ ሽብርተኝነት ሕጉ መከሰሳቸውና መታሰራቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የሰብዓዊ መብት አያያዝ ሁኔታን ችግር የሚያሳይ ነው ይላል፡፡
በተጨማሪም በዚህ ያላግባብ ጥቅም ላይ እየዋለ እንደሚገኝ በገለጸው የአገሪቱ የፀረ ሽብርተኝነት ሕግ አማካይነት የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩት አቶ ዮናታን ተስፋዬ የፌስቡክ ገጻቸው ላይ የጻፉዋቸው ጽሑፎች እንደ ማስረጃ ተመዝግበው መታሰራቸው፣ የፓርቲው ልሳን የነገረ ኢትዮጵያ ድረ ገጽ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበሩት አቶ ጌታቸው ሽፈራው፣ የኦሮሚያ ቴሌቪዥን የዜና አዘጋጅ የነበሩት አቶ ፍቃዱ ሚርካና እንዲሁም አቶ ዘላለም ወርቅ አገኘሁ የተባሉ ብሎገር መታሰራቸው ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰት ማሳያ እንደሆነ ያትታል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ይህ አዲሱ ረቂቅ የቀድሞው አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የሕዝብ ግንኙነት የነበሩት አቶ ሀብታሙ አያሌው የሚያስፈልጋቸውን ሕክምና በጊዜው እንዳያገኙ መከልከላቸው፣ የመንግሥትን በሃይማኖት ጣልቃ መግባትን የተቃወሙ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትን ማሰሩና ከሰባት እስከ ሃያ አምስት ዓመታት ድረስ በሚደርስ የእስር ቅጣት መቅጣቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰት መበራከቱን እንደሚያሳይ አስረጅ ሆነው ቀርበዋል፡፡
ሰብዓዊ መብትን መደገፍና ሁሉን አቀፍ የሆነ መንግሥትን ማበረታታት ተገቢ እንደሆነ የሚገልጸው ረቂቁ፣ በኢትዮጵያ በ2007 ዓ.ም. ከተደረገው ጠቅላላ ምርጫ በኋላ ግን የአገሪቱ የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት አያያዝ ሁኔታ በከፍተኛ ሁኔታ መመናመኑን ያትታል፡፡
ለዚህም የሰብዓዊ መብት አያያዝ ሁኔታና የዴሞክራሲ መመናመን በረቂቁ የሚቀርበው አንዱ ምክንያት ደግሞ፣ አገሪቱን እየመራ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎችን መቶ በመቶ መቆጣጠሩን ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ከምርጫው በኋላ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽና የመደራጀት መብት መገደቡ፣ በርካታ ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸው እስራቶች መፈጸማቸው፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ላይ እስራቶች፣ ወከባና ማስፈራራት መድረሱ ሌሎች ማስረጃዎች እንደሆኑ ረቂቁ ይዘረዝራል፡፡
በአማራ ክልልና በኦሮሚያ ክልል አለመረጋጋት ከተከሰተ በኋላ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የሟቾች ቁጥር 120 ነው ማለቱን የሚገልጸው ረቂቁ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ቡድኖች የሟቾችን ቁጥር 400 እንደሚያደርሱት ጠቁሞ ቁጥሩ ግን ከዚህ በላይ ሊሆን እንደሚችል አስታውቋል፡፡
በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች የሚነሱ አለመረጋጋቶችንና ግጭቶችን ለመቆጣጠርና ለማረጋጋት መንግሥት በሚወስደው ዕርምጃ፣ በመሠረታዊነት የአገሪቱን ሕገ መንግሥት የሚጥስ መሆኑንም ረቂቁ ያትታል፡፡
ረቂቁ በቅርቡ በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰው ቃጠሎ ተመርምሮ ለሕዝብ እንዲገለጽ የሚጠይቅ ሲሆን፣ በተጨማሪም በአገሪቱ የሚገኙ እስር ቤቶች በጣም የተጣበቡና የተጨናነቁ ከመሆናቸው ባሻገር የፅዳት ሁኔታቸውም ችግር እንዳለበት ይገልጻል፡፡
በተጨማሪም በአገሪቱ እስር ቤቶች የንፁህ የመጠጥ ውኃ እጥረት መኖሩን፣ እንዲሁም እስረኞች የሕክምና አገልግሎት እንዳያገኙ ማድረግና ተገቢውን የሕግ ምክር አገልግሎት እንዳያገኙና እንዳይጐበኙ ማድረግ፣ ሌሎች ከእስር ቤቶች ጋር በተያያዘ በረቂቁ የተዘረዘሩ ችግሮች ናቸው፡፡
እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩትን የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ ጥሰቶችን አስመልክቶ ጉዳዮቹን የዘረዘረው ረቂቅ፣ የንፁኃን ዜጐችን ሞትና የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተጠቀሙትን ከመጠን ያለፈ ዕርምጃ አውግዟል፡፡
በተጨማሪም ጋዜጠኞች፣ ተማሪዎች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችና የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠውን የመሰብሰብና ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትን በመጠቀማቸው የደረሰባቸውን እስራትና እንግልት እንዲሁ አውግዟል፡፡
የአገሪቱን ፀረ ሽብርተኝነት ሕግ መንግሥት በተለጠጠ ማዕቀፍ በመጠቀም የተለየና የተቃውሞ ድምጾችን ለማፈን ከማዋል እንዲቆጠብና ሌሎች የዜጐችን የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን የሚያፍኑ ሕጐችና አዋጆች እንዲሻሩ ይጠይቃል፡፡
በመጨረሻም በአገሪቱ እየተካሄዱ ያሉ ተቃውሞዎች በሰላማዊ መንገድ፣ እንዲሁም ከግጭቶች ፀድተው እንዲካሄዱ ለሕዝቡ መልዕክት ያስተላለፈ ሲሆን፣ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችም ከመጠን ያለፈ ኃይል መጠቀምን እንዲያቆሙ ጠይቋል፡፡
የመንግሥት ምላሽ
ኤችአር 2003 በረቂቅ ደረጃ እያለ ሕግ ሆኖ እንዳይፀድቅ ከፍተኛ ጥረት ያደረገውና ዓለም አቀፍ የሕግ ተቋምን በወትዋችነት ቀጥሮ የነበረው የኢትዮጵያ መንግሥት፣ አሁን ግን እንደዚያ ዓይነት ዕርምጃ እንደማይወስድ ገልጿል፡፡
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ‹‹ለአዲሱ ረቂቅ ምንም ዓይነት ወትዋች ቡድን አይቀጠርም፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥትን የሚደግፉ በርካታ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ስላሉ መንግሥት ተጨማሪ ወትዋች አያስፈልገውም፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት ሕጐች ጊዜ ጠብቀው እንደሚወጡ የገለጹት አቶ ጌታቸው ይህንንም ሕግ፣ ‹‹ይህ እንደ ኢንፍሉዌንዛ ጊዜ እየጠበቀ የሚወጣና ዴሞክራሲ ከአሜሪካ ብቻ ነው የሚመጣው የሚል አመለካከትን የሚያንፀባርቅ ነው፤›› በማለት አዲሱን ረቂቅ ተችተውታል፡፡
ኤችአር 2003 በርካታ ደረጃዎችን አልፎ የበርካታ ፖለቲከኞችና የኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ወገኖቹ መወያያ ሆኖ ነበር፡፡ አሁን የቀረበው ረቂቅ ኤችአር 2016 ምን ያህል እንደሚጓዝና የሚፈጥረው ተፅዕኖ በጊዜ ሒደት የሚታይ ይሆናል የሚሉም አሉ፡፡
የፖለቲካ ፓርቲዎች አተያይ
የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ጥናትና ምርምር ኃላፊ የሆኑት አቶ ዋስይሁን ተስፋዬ ረቂቁን መመልከታቸውን ገልጸው፣ በዋናነት ለረጅም ጊዜ የአገሪቱ የፖለቲካ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሲጠይቁት የነበረ ጥያቄ በረቂቁ መካተቱን ገልጸዋል፡፡ ‹‹የተነሱት ጥያቄዎች እኛ ስናነሳቸውና ስንጠይንቀቸው የነበሩ ናቸው፡፡ በዋናነት አሁንም ቢሆን ተቃዋሚዎች ናቸው ለኢትዮጵያ ሕዝብ የዴሞክራሲም ሆነ የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ኃላፊነት መውሰድ ያለባቸው፡፡ እነዚህን ረቂቅ ሕጐች የምንመለከታቸው ድጋፍ ይሆናሉ በሚል እንጂ፣ በዋናነት ከዚያ በኩል የሚነሳ ጥያቄ የኢትዮጵያን መንግሥት ጫና ውስጥ ከትቶ የእኛንም ጥያቄዎች ያስመልሳል የሚል ግምት የለንም፡፡ የመፅደቅ ዕድሉም ተስፋ የሚጣልበት አይደለም፤›› ብለዋል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ይህን ረቂቅ መሠረት አድርጐ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ የተለያዩ ጫናዎች ይፈጥራል የሚል እምነት እንደሌላቸውም አቶ ዋስይሁን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ብዙ ነገሮች ኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄዱ የአሜሪካ መንግሥት ምንም ሲያደርግ አላየንም፡፡ ምርጫ 2007 በተካሄደ ማግሥት ፕሬዚዳንቱ ስለኢትዮጵያ ምርጫ የሰጡትን አስተያየት ማንሳቱ በቂ ነው፤›› በማለት አሜሪካ የኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጫና የማድረግ ፍላጎት እንደሌላት አስረድተዋል፡፡
በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ረቂቁ ብቻውን ለኢትዮጵያ ፖለቲካ መልስ ይሰጣል ብለው እንደማያምኑ አመልክተዋል፡፡ ‹‹አሜሪካኖች ብዙ ጊዜ እንዲህ ዓይነት ነገር ሲያጋጥም የሕዝቡን ትኩረት ለመያዝና ከሕዝብ ጎን የቆሙ ለማስመሰል የሚያደርጉት ነው፤›› በማለት ረቂቁን ተችተዋል፡፡
በምርጫ 97 የወጣውን ኤችአር 2003 ያስታወሱት ኢንጂነር ይልቃል፣ ‹‹ነገሩ ውኃ በልቶት ነው የቀረው፤›› ብለዋል፡፡ ይኼኛውም ከዚያ የተለየ ዕጣ ፈንታ ይኖረዋል ብለው እንደማይገምቱ ገልጸዋል፡፡ ‹‹የዚህ ዓይነቱን በተግባር ያልተደገፈ የፖለቲካ አፍዓዊ አስተያየት አልቀበለውም፡፡ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሎች ናቸው እንጂ ውጤት የሚያመጡት፣ እንዲህ ያለ ነገር ዳር ደርሶ ውጤታማ ሲሆን አላይም፤›› በማለት በረቂቁ ላይ ያላቸውን ጥርጣሬ ገልጸዋል፡፡
‹‹እንደ አንድ ፖለቲከኛ ጓደኞቼ ከእስር ቢፈቱና አፋኝ አዋጆች ቢሰረዙ እውነት ከሆነ ደስ ይለኛል፡፡ እኛም ደጋግመን የምንጠይቃቸው ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር በረቂቁ የተነሱት ጥያቄዎች ትክክል ናቸው፡፡ ነገር ግን እንደ ፖለቲካ አሜሪካኖች ቁርጠኝነት እንደሚያንሳቸውና ጉዳዩን ከምር እንዳልያዙት የሚታይ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ከረቂቁ መፅደቅ አንፃር ሊፀድቅ እንደሚችል የገመቱ ቢሆንም፣ ‹‹ነገር ግን ወደ ተግባር ለመለወጥ ምን ያህል እርግጠኞች ናቸው?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ ‹‹ኤችአር 2003 ለምን ሳይፀድቅ ቀረ? የኢትዮጵያ መንግሥት ተሻሽሎ ነው? ከዚያ ወዲህ ነው እነዚህ አፋኝ ሕጎች የወጡት፡፡ ነገሮች እዚህ ደረጃ ላይ ሳይደርሱ ያን ሕግ ለማፅደቅ ብዙ ምክንያቶች ነበራቸው፡፡ ከዚህ አንፃር ከሕዝብ ግንኙነት ሥራ አልፎ አሜሪካኖች ለፖለቲካ ቆርጠው ይህን መንግሥት ለመቆንጠጥና ነገሮች እንዲለወጡ ሄደዋል በሚለው ጉዳይ ጥርጣሬ አለኝ፤›› በማለት ደምድመዋል፡፡