የኢዮትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንን እያስተዳደረ የሚገኘው የአቶ ጁነዲን ባሻ ካቢኔ የአገልግሎት ዘመኑን ለማጠናቀቅ አራተኛ ዓመቱ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ የፌዴሬሽኑ የቆይታ ጊዜ ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ መልኩ በመጨረሻው ዓመቱ ላይ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ላይ የዕገዳ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
የአዲስ አበባ አስተዳደርን በመወከል ለፌዴሬሽኑ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል በመሆን የተመረጡት አቶ ዮሴፍ ተስፋዬ አንዱ ናቸው፡፡ አቶ ዮሴፍን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ከወራት በፊት የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ውጪ መሆኑን አስመልክቶ የተላለፈውን ውሳኔ ተከትሎ ፌዴሬሽኑ ከኃላፊነታቸው እንዲታገዱ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ከሰሞኑ ደግሞ የጋምቤላው ተወካይና የፌዴሬሽኑ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት ኢንጂነር ቾል ቤል ሁለተኛው አመራር ሆነዋል፡፡ ፌዴሬሽኑም አመራሩን በዲሲፕሊን ከኃላፊነታቸው ያገደ መሆኑ ፌዴሬሽኑ ይፋ አድርጓል፡፡ የውሳኔው ዝርዝር ጉዳይን አስመልክቶ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ግልጽ አልተደረገም፡፡ ስለጉዳዩ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የፌዴሬሽኑ ተጠባበቂ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንድምኩን አላዩ የውሳኔውን እውነትነት አረጋግጠው ዝርዝር ማብራሪያ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ በኢንጂነር ቾል ቤል በኩል ያለውን ለማረጋገጥ ሪፖርተር ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
እንደ አቶ ወንድምኩን ገለጻ ከሆነ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በኢንጂነር ቾል ላይ የዕገዳ ውሳኔ ከማስተላለፍ ቀደም ብሎ ከሴቶቹ ብሔራዊ ቡድን ጋር በተያያዘ በዕገዳ የቆዩት የአቶ ተስፋዬ ዕገዳ እንዲነሳላቸው ተደርጓል፡፡ ይህንኑ የፌዴሬሽኑን ውሳኔ ተከትሎ አንዳንድ ወገኖች ሒደቱ ‹‹የጎመን ምንቸት ውጣ፣ የገንፎ ምንቸት ግባ›› ዓይነት መሆኑን በመግለጽ ላይ ይገኛሉ፡፡