- Advertisement -

‹‹አሁን ባለው አቅም ኤጀንሲው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ሊቆጣጠር አይችልም››

ዶ/ር ተስፋዬ ሙህዬ፣ የከፍተኛ ትምህርት ጥራትና አግባብነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር

ዶ/ር ተስፋዬ ሙህዬ ፒኤችዲ ዲግሪያቸውን የሠሩት በጂኦግራፊ ሲሆን፣ በፐብሊክ አድሚኒስትሬሽን ደግሞ ማስተርስ አላቸው፡፡ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ላይ ሠርተዋል፡፡ የዓለም ባንክ ምሥራቅ አፍሪካ ሪሀብሊቴሸን ፕሮጀክት ማናጀርም ነበሩ፡፡ ከዚያም የአማራ ክልል የትምህርትና ሥልጠና አቅም ግንባታ ፕሮግራሞች መምሪያ ኃላፊ ሆነውም አገልግለዋል፡፡ በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት፣ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ደግሞ ምክትል ፕሬዚዳንት በመሆን ሠርተዋል፡፡ የከፍተኛ ትምህርት ስትራቴጂ ማዕከል የተወሰነ ጊዜ ከሠሩ በኋላ እንደገና ወሎ ዩኒቨርሲቲን ተቀላቅለዋል፡፡ ዶ/ር ተስፋዬ ሙህዬ በአሁኑ ወቅት የከፍተኛ ትምህርት ጥራትና አግባብነት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ናቸው፡፡ በአገሪቱ የከፍተኛ ትምህርትን ጥራት ለማሻሻል ተቋሙ እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ በሚመለከት ምሕረት አስቻለው ከዶ/ር ተስፋዬ ሙህዬ ጋር ቆይታ አድርጋለች፡፡

 

ሪፖርተር፡- የአገሪቱ የከፍተኛ ትምህርት ከባድ የጥራት ችግር እንዳለበት አጥኚዎች ይገልጻሉ፡፡ ኤጀንሲውም የተለያዩ ጥረቶችን ሲያደርግ ቢቆይም ችግሩን መፍታት ሳይቻለው የትምህርት ጥራት እየወደቀ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ኤጀንሲውን የመምራት ኃላፊነትን እንዴት ተቀበሉ?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ የከፍተኛ ትምህርት ጥራት እየወረደ እንደነበር ተማሪዎቼን በመመልከት እገነዘብ ነበር፡፡ ስለዚህም ወደዚህ ኃላፊነት እንድመጣ ሲነገረኝ ደንግጬ ነበር፡፡ የምንቀበለው፣ አስመርቀን የምናመጣው ተማሪ እንዴት ያለ ነው? የሚለው ሁሌም የመምህራን መወያያ ነው፡፡ ከማኅበረሰቡ የምንሰማቸው ነገሮችም አሉ፡፡ በከፍተኛ ትምህርት ተቋም ያለፉና ችግሩን የሚያውቀው ባለሙያ ተቋሙን ካልመራው ሁኔታው ሊቀየር እንደማይችል በማመን ኃላፊነቱ ከባድ እንደሆነ እያወቅኩኝ ተቀብያለሁ፡፡ ወደ ኃላፊነት ስገባም ያልጠበቅኳቸው ችግሮች አጋጥመውኛል፡፡ ቢሆንም በተስፋና በቁርጠኝነት ለመሥራት ወስኛለሁ፡፡

ሪፖርተር፡- ከወራት በፊት ኃላፊነት ሲቀበሉ ኤጀንሲው በመዋቅራዊ ለውጥ ሒደት ላይ ነበር፡፡ ሒደቱ አሁንም እንደቀጠለ ይመስለኛል፡፡ የመዋቅራዊ ለውጡ ዋነኛ ጉዳዮች ምን ምን ናቸው?

- Advertisement -

ዶ/ር ተስፋዬ፡- እኔ ከመምጣቴ በፊት የመዋቅርና ተጓዳኝ የደረጃ ማሻሻያ ተደርጎ ነበር፡፡ አደረጃጀቱ በጣም ጠባብ ነው፡፡ መደቦች ዝቅተኛ በመሆናቸው እንኳን ሌላ ባለሙያ መሳብ እዚህ ያለውንም ለማቆየት የሚያስችል አይደለም፡፡ እዚህ ላይ እየሠራን ነው፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር መሻሻል ያለበት ነገር ቶሎ ተሻሽሎ ወደ ተግባር እንዲገባ ነገሮች እንዲፋጠኑና የትምህርት ጥራት ላይ ሊታይ የሚችል ተጨባጭ ለውጥ እንዲመጣ እየጠየቀን ነው፡፡

ሪፖርተር፡- እንዲደረግ የሚጠበቀው ትልቁ ለውጥ ምንድን ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- አቅማችንን ማሻሻል፡፡ ምክንያቱም በዚህ የቀጨጨ አደረጃጀት በቁጥር፣ በሚሸፍኑት የሥልጠና ዘርፍ አድማስ ሰፊ የሆኑ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ጥራት ማስጠበቅ የሚቻል አይሆንም፡፡ አሁን ባለንበት ደረጃ የከፍተኛ ትምህርት ጥራትን ማሻሻል ቀርቶ ተቋማቱን መከታተል የምንችልበት ሁኔታ ላይ አይደለንም፡፡ ስለዚህም የትምህርት ሚኒስቴር ውትወታ አቅም መፍጠሩ ነው፡፡ እኛም እዚህ ላይ እየሠራን ነው፡፡ አሁን ባለው አቅም ግን ኤጀንሲው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ሊከታተልና ሊቆጣጠር አይችልም፡፡

ሪፖርተር፡- የኤጀንሲውን አቅም ለመጨመር ምን ዓይነት ነገሮች መደረግ አለባቸው?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- የመጀመርያው የሰው ኃይል መሟላት ነው፡፡ ይህ የሰው ኃይል መምጣት ያለበት የከፍተኛ ትምህርት ሁኔታን፣ የማስተማር ሒደቱን ችግሩን ከሚያውቅ ከዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ ነው፡፡ እንደ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ፣ አስተማሪና አመራር ሆኖ ማሰብ የሚችል ባለሙያ ያስፈልጋል፡፡ በዚህ ደረጃ ያለን ሰው ለመሳብ ደግሞ ኤጀንሲው የሚሰጠው ደረጃ ቢያንስ ከዩኒቨርሲቲ መሻል ይኖርበታል፡፡ ሥራውም ጫና ያለው በመሆኑ ደረጃው ሳቢ መሆን አለበት፡፡ ሌላው አቅምን ለማሻሻል የሚያስፈልገው የኤጀንሲው ሥልጣን እንዲጨምር ማድረግ ነው፡፡ ለዚህም ኤጀንሲው የተቋቋመበት አዋጅን ለማሻሻል እየተሠራ ነው፡፡ አዋጁ በመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች፣ በግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አስተያየት እንዲሰጥበት ተደርጓል፡፡

ሪፖርተር፡- ኤጀንሲው የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን በመቆጣጠር ረገድ ምንድረስ ሥልጣን አለው?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- አንደኛው አዋጁን ማሻሻል ያስፈለገበት ጉዳይ ይህ ነው፡፡ የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ፕሮግራሞችን የመክፈት የማሠልጠን ሥልጣን  ተሰጥቷቸዋል፡፡ በአደረጃጀት፣ በሰው ኃይልና በመሳሰሉት ተቋማዊ ኦዲት እናደርጋለን፡፡ በዚህ ኦዲት መሠረት በትምህርት ሚኒስቴር በኩል ዕርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ እንችላለን፡፡ በራሳችን ለብቻችን ግን ዕርምጃ መውሰድ አንችልም፡፡ አዋጁ ቢሻሻል ግን ይህን ማድረግ፣ ፕሮግራሞች ሲከፈቱም የአግባብነታቸውን ጉዳይ በመመዘን ረገድ ሥልጣን ይኖረናል ብዬ እገምታለሁ፡፡ ያኔ ፕሮግራሞች እንዲከፈቱ የመፍቀድ የመዝጋት አቅም ይኖራል ማለት ነው፡፡

ሪፖርተር፡- የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን በመቆጣጠር ረገድ የኤጀንሲው እንቅስቃሴ ምን ይመስላል?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- እዚህ ላይ ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ ተማሪዎች መቆየት ያለባቸውን ዓመታት ሳይቆዩ የማስመረቅና ባልተፈቀደ ካምፓስ ትምህርት የመስጠት ችግሮች አሉ፡፡ በዚህ መልኩ ተምረው ተመርቀው ሥራ የያዙ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ ነው፡፡ ሲኦሲ ሳይወስዱ አስተምሮ የማስመረቅ ነገር በተቋማቱ በኩል ይታያል፡፡ በዚህ መልኩ ተምረው ለተመረቁ ዕውቅና አልሰጥም ያሉ ክልሎችም አሉ፡፡ ይህንን ተከትሎ ዕውቅና አለኝ ብሎ በአደባባይ ባስተዋወቀ የትምህርት ተቋም እንዴት እንዲህ እንጭበረበራለን? የሚል አቤቱታ ለእንባ ጠባቂ ሁሉ ቀርቧል፡፡ እነዚህን ችግሮች መፍታት ያስችለናል ያልነውን ስትራቴጂ ለትምህርት ሚኒስቴር አቅርበን ነሐሴ መጨረሻ ላይ ፀድቆ ተሰጥቶናል፡፡ ስትራቴጂውን ተግባራዊ ማድረግ የሚያስችል የማስፈጸሚያ ስትራቴጂ ከሌለ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ አሁን የማስፈጸሚያ ስትራቴጂውን መፅደቅ እየተጠባበቅን ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በዚህ አዲስ ዓመት ተቋማቱን በመቆጣጣር ረገድ የምትከተሉት አሠራር ምን ይመስላል?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- ተቋማቱ ከተፈቀደላቸው ውጭ መንቀሳቀስ የሚችሉበትን ዕድል መዝጋት ነው፡፡ ለምሳሌ በዚህ ዓመት ሥልጠና መስጠት የሚችሉ ተቋማትን፣ የሥልጠና ዘርፎችና ካምፓሶችን ዝርዝር አውጥተናል፡፡ ይህን ዝርዝር በተለያዩ ቋንቋዎች ለራሳቸው ለተቋማቱ ለወረዳ መስተዳድሮች በሙሉ እናሠራጫለን፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጊዜ የወረዳ መስተዳድሮች ተቋማቱ አካባቢያቸው ላይ ሲንቀሳቀሱ ፈቃድ ይኑራቸው አይኑራቸው መጠየቅ እንዳለባቸው አያውቁም፡፡ ይህ በዚህ ወር ተግባራዊ መሆን ይጀምራል፡፡ ሌላው ከዚህ ቀደም የነበረ ቢሆንም፣ ከመንግሥትም ተቋማት ጋር በቅርበት መሥራት የዚህ ዓመት ትኩረት ነው፡፡ በቅርቡ የግልም የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ፕሬዚዳንቶችና የጥራት ማረጋገጫ ኤክስፐርቶችን ጠርተን ተነጋግረን ነበር፡፡ 

ሪፖርተር፡- የትምህርት ጥራት ወርዶ ወርዶ ወደቀ የሚባልበት ደረጃ የደረሰበት አገር ላይ የከፍተኛ  ትምህርት ጥራትና አግባብነት ኤጀንሲ የሚባል ተቋምን መምራት ምን ያህል አስቸጋሪ ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- እንደ ዩኒቨርሲቲ መምህር እኔም የጥራት ችግር ምን ድረስ እንደሆነ ተመልክቻለሁ፡፡ የአገሪቱ የትምህርት ጥራት ችግር ከቋንቋ ጋር የተያያዘ እንደሆነ የተለያዩ ተመራማሪዎች አመልክተዋል፡፡ የትምህርት ጥራትን ችግር መንግሥትም አምኖበት የተለያዩ ጥረቶችን እያደረገ ነው፡፡ ከከፍተኛ ትምህርት ጥራት ጋር ተያይዞ የሚነሳው ሌላ ነገር የሥነ ምግባር ነው፤ በአስተማሪም በተማሪም በኩል፡፡

ሪፖርተር፡- ከአቻ ግመታ ጋር በተያያዘ ምን እየሠራችሁ ነው?

ዶ/ር ተስፋዬ፡- ይህ ነገር የውጭ አገር ዲግሪዎችን በኢትዮጵያ መስፈርት የት ላይ ናቸው? የሚለውን የመገመት ሥራ ነው፡፡ ተግባሩ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ አንድ ተማሪ በትክክልም ከአንድ የውጭ አገር ዩኒቨርሲቲ ዲግሪውን አግኝቷል ወይ? የሚለውን ሁሉ ይጨምራል፡፡ ስለዚህ የአቻ ግመታ ሥራ ሰፊ ነው፤ ጥያቄውን መመለስም ረዥም ጊዜ ይወስዳል፡፡ የተሳሳቱ ማስረጃዎችን ይዘው የሚመጡ አሉ፡፡

 

- Advertisement -

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን

ከ ተመሳሳይ አምዶች

ፈተና የበዛበት አመጋገብ እንዴት ይፈታ?

አቶ አብነት ተክሌ የሥነ ምግብ ባለሙያ ሲሆን የመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪውን ምግብና ምግብ ነክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ትኩረቱን አድርጎ ነው ያጠናው፡፡ በመጀመሪያ ዲግሪው በሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ...

ከባህር ዳር የፈለቀው ተራድዖ

ዝግባ የሕፃናትና የአረጋውያን መርጃ የበጎ አድራጎት ድርጅት ከተቋቋመ 16 ዓመታት ሆኖታል፡፡ ዋና ማዕከሉን ባህር ዳር ከተማ ላይ በማድረግ በእንጅባራ፣ በጎንደርና በአዲስ አበባ ከተማ ላይ...

ታዳሽ ኃይልን ለኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች

ዩቶፕያ ቴክኖሎጂ በአውቶሞቲቭ፣ በታዳሽ ኃይል ቴክኖሎጂ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በግብርና ምርት ፕሮሰሲንግና ኤክስፖርት በማድረግ፣ እንዲሁም በአይሲቲ ዘርፍ ላይ በመሰማራት በተለያዩ ዓለም አቀፍ የንግድ ከተሞች ላይ የኢትዮጵያን...

አፍሪካን ከ‹‹ኤ›› እስከ ‹‹ዜድ››

የአፍሪካ አኅጉርን የተለያዩ መረጃዎችን በማጥናትና በመሰብሰብ በርካታ ዓመታትን አሳልፈዋል፡፡ ከመንግሥት አወቃቀር ጀምሮ እያንዳንዱ የአፍሪካ አገር ያለውን እሴት የሚዳስስ ኤቱዜድ አፍሪካ (አፍሪካ ከሀ እስከ ፐ)...

‹‹የብድርና ቁጠባ ኅብረት ሥራ ማኅበራትን ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ ማጠናከር ያስፈልጋል›› አቶ ፍፁም አብርሃ፣ የአሚጎስ ብድርና ቁጠባ ኅብረት ሥራ ማኅበር መሥራችና ሥራ አስኪያጅ

አሚጎስ የብድርና ቁጠባ ኅብረት ሥራ ማኅበር ከተመሠረተ አሥራ ሁለት ዓመታት ሆኖታል፡፡ በእነዚህ ዓመታት 8,500 አባላትን ማፍራት ችሏል፡፡ አሚጎስ ስለተመሠረተበት ዓላማ፣ እያከናወናቸው ስለሚገኙ ተግባራት፣ የብድርና...

ከደብረ ብርሃን የሚጣራው ሀበሻ የአረጋውያንና የምስኪኖች መርጃ

ሀበሻ የአረጋውያንና የምስኪኖች መርጃ ልማት ድርጅት መቀመጫውን ደብረብርሃን በማድረግ ጧሪ የሌላቸውን ችግረኞች እየረዳ ይገኛል፡፡ በነፍሰሄር አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም እና በአቶ ዮርዳኖስ ፍቃዱ ተክለማርያም በ2008...

አዳዲስ ጽሁፎች

የጤናው ዘርፍ ባለፉት ስድሥት ወራት

የወባ በሽታ ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገሮች ዋነኛ የጤናና የማኅበራዊ ቀውስ መንስዔ ነው፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት እ.ኤ.አ. በ2024 ያወጣው መረጃም 263 ሚሊዮን ሰዎች የወባ...

የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት በባለሙያ ዓይን

(በጎ ጎኖችና እርምት የሚፈልጉ ጉዳዮች) በዮሐንስ መኮንን በጥር ወር 2016 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ዋና ዋና ኮሪደሮችን በማዘመን ከተማዋን ለነዋሪዎቿና ለጎብኚዎቿ ምቹ ያደርጋታል የተባለ ፕሮጀክት በ43 ቢሊዮን...

በልዩነት ውስጥ ሆነንም እስኪ እንነጋገር

በገነት ዓለሙ ዴሞክራሲ መብቶችና ነፃነቶች የሚሠሩበት የሕዝብ አስተዳደር ነው፡፡ ሰብዓዊ መብቶችንና ነፃነቶችን መኗኗሪ ያደረገ ሥርዓት ነው፡፡ እነዚህ መሠረታዊ መብቶችና ነፃነቶች በተፈጥሮ የተገኙ፣ ሰው በመሆናችን ብቻ...

ለጤናማ የትራፊክ ፍሰትና ለመንገድ ደኅንነት ቅጣት መጣል ብቻውን መፍትሔ አይሆንም!

በአዲስ አበባ ከተማ ለተሽከርካሪዎች ምቹ የሆኑ መንገዶችን እየተመለከትን ነው፡፡ ከአዳዲሶቹ መንገዶች ባሻገር አንዳንድ ነባር መንገዶች የማስፋፊያ ሥራ ታክሎባቸው አገልግሎት ላይ ውለዋል፡፡ ከኮሪደር ልማቱ ጋር...

የግጭት አዙሪት ውስጥ ሆኖ የአፍሪካ ማዕከል መሆን ያዳግታል!

የአፍሪካ ኅብረት 38ኛው የመሪዎች ጉባዔ በአዲስ አበባ ሲካሄድ ብዙ ትዝ የሚሉ ጉዳዮች አሉ፡፡ እጅግ በጣም አሰልቺ፣ ውጣ ውረድ የበዛበትና ታላቅ ተጋድሎ ተደርጎበት ከከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ...

አገሬ ምንተባልሽ – ልብ ያለው ልብ ይበል

በቶማስ በቀለ ይቺ አገራችን ብዙ ተብሎላታልም፣ ብዙ ተወርቶባታልም፣ አገሪቱ በቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ አገር (ላይቤሪያን ጨምሮ) ከመሆኗ አኳያ የሚነገርላት ብዙ ጥሩና የሚገርሙ ነገሮች ያሉትን ያህል፣ ከረሃብ...
[the_ad id="124766"]

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን