‹‹ሙሉ ክፍያ የፈጸሙ የተመዝጋቢዎች ሁኔታ እየተጣራ ነው›› የቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ
መንግሥት ባቀረባቸው የቤት ግንባታ ፕሮግራሞች ተጠቃሚ መሆን የሚችሉት ምንም ዓይነት መኖሪያ ቤት የሌላቸው ብቻ መሆናቸውን የገለጸ ቢሆንም፣ ከተለያዩ ሪል ስቴቶች ቤት የገዙ በውጭና በአገር ውስጥ የሚኖሩ ግለሰቦች በ40/60 ኮንዶሚኒየም መመዝገባቸው ተጠቆመ፡፡
መንግሥት ፕሮግራሞቹን ሲያቀርብ ባወጣው ሕግ ለዜጐች ግልጽ እንዳደረገው፣ በማንኛውም ፕሮግራም ማለትም 40/60፣ 20/80 ወይም 10/90 መመዝገብ የሚችሉት፣ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ምንም ዓይነት መኖሪያ ቤት የሌላቸው፣ ለሦስተኛ ወገን ያላስተላለፉና በውርስም ቢሆን ቤት ያላገኙ መሆን እንዳለባቸው መገለጹን የኢንተርፕራይዙ የኮሙዩኒኬሽን የሥራ ሒደት መሪ አቶ ዮሐንስ ዓባይነህ አስታውሰዋል፡፡ ይኼንን ተላልፈው የተገኙ እስከ 15 ዓመታት የእስራት ቅጣት እንደሚያጋጥማቸው ኢንተርፕራይዙ ለሪፖርተር ገልጿል፡፡
መቶ በመቶ ክፍያ ፈጽመው ግንባታቸው የተጠናቀቁ የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ለሪፖርተር የገለጹት አቶ ላይኔ ሰለሞንና ወ/ሮ አዳነች መገርሳ፣ ዕጣው ሊወጣ መሆኑ ከተገለጸ ከአንድ ዓመት በላይ መቆየቱ ግራ እያጋባቸው እያሉ፣ ከሪል ስቴቶች ቤት የገዙ በርካታ ሰዎች ከመቶ ፐርሰንት በላይ ክፍያ ፈጽመው ዕጣ እየተጠባበቁ መሆኑን ሲሰሙ የበለጠ ግራ እንደተጋቡ አስረድተዋል፡፡
በተለያዩ መንገዶች ድርጊቱ እውነት ስለመሆኑ አጣርተው ትክክለኛነቱን እንዳረጋገጡ የሚናገሩት ሁለቱም ተመዝጋቢዎች፣ የሚመለከተው አካል ጉዳዩን አጣርቶ ባወጣው ሕግ መሠረት ዕርምጃ በመውሰድ እንዲያስተካክል አሳስበዋል፡፡
ተመዝጋቢዎቹ ያቀረቡትን ጥያቄ ኢንተርፕራይዙ ምላሽ እንዲሰጥበት ሪፖርተር ላቀረበው ጥያቄ፣ የቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ ልዩ የማጣራት ሥራ እያከናወነ መሆኑን አቶ ዮሐንስ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ግንባታቸው የተጠናቀቀው የሰንጋ ተራና የክራውን የ40/60 ሳይቶች ዕጣ ከመውጣቱ በፊት፣ የተመዝጋቢዎች ማንነትና በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማለትም በስማቸው የተመዘገበ ቤትም ሆነ ይዞታ መኖር አለመኖሩ፣ በየወረዳው እየተጣራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ዜጐች በግላቸው የገነቡትም ሆነ ከሪል ስቴት የገዙት ቤት ቢኖራቸው ካርታ የሚያገኙት ይዞታው ካለበት ክፍለ ከተማ በመሆኑ፣ ሊደበቁ ስለማይችሉ በቀላሉ ማረጋገጥ እንደሚቻልም አቶ ዮሐንስ አስረድተዋል፡፡