በአሁኑ ወቅት ግን በተለያዩ ሥራዎች የከተማዋ የጐርፍ አደጋ ሥጋት ተቀርፏል፡፡
* * *
ኢዮሐ!
ኢዮሐ!
አበባ ፈነዳ
ፀሐይ ወጣ ጮራ
ዝናም
ዘንቦ
አባራ፡፡
ዛፍ አብቦ
አፈራ፡፡
ክረምት መጣ ሄደ
ዘመን ተወለደ፡፡
አዲስ ዓለም ሆነ፡፡
ሌሊት ሊነጋጋ…
ጋራው ድንጋይ ከሰል፣
የተተረከከ ፍም እሳት
ደመናው
ፀሐይ ያነደደው
ዓለም ሞቆ
ደምቆ፡፡
ብርሃን ሲያሸበርቅ
ጤዛው ሲያብረቀርቅ
ሕይወት ሲያንሰራራ
ፍጥረት ሲንጠራራ፡፡
ዘመን ተለወጠ
መስከረም አበራ፡፡
‹‹ኢዮሐ አበባዬ!!››
- ገብረክርስቶስ ደስታ ‹‹መንገድ ስጡኝ ሰፊ›› (2001)
* * *
ወጣቷ የልጅነት ፎቶዎቿን በፌስቡክ ገጻቸው የለጠፉ ወላጆቿን ከሰሰች
የ18 ዓመቷ ወጣት የልጅነቷን ፎቶዎች በፌስቡክ ገጻቸው የለጠፉ ወላጆቿን ከሰሰች፡፡ ወላጆቿ ፌስቡክ ላይ በለጠፉት የልጅነት ፎቶዎቿ የተነሳም እ.ኤ.አ. ከ2009 ወዲህ ሕይወቷ እንደተመሳቀለ መግለጿንም ሚረር ዩኬ ዘግቧል፡፡
በኦስትሪያ የምትኖረው ወጣት ወላጆቿን ከመክሰሷ በፊት በፌስቡክ ገጻቸው የለጠፏቸውን የልጅነቷን ፎቶዎች እንዲያነሱ በተደጋጋሚ ጠይቃለች፡፡ ሆኖም ቤተሰቦቿ ፈቃደኛ አልነበሩም፡፡
ግላዊ የሆኑና በልጅነት ጊዜዋ ያለፈችባቸውን ዳይፐር ሲቀየርላት፣ ፖፖ ላይ ተቀምጣና መሰል ፎቶዎች በፌስቡክ መለቀቁ እንዳበሳጫት የምትናገረው ወጣት፣ በወላጆቿ እምቢተኝነት ምክንያት ፍርድ ቤት አቁማቸዋለች፡፡
ከሕፃንነት ጀምሮ ያሉ ዕድገቶቿን በተለይም ግላዊ የምትላቸውን ፎቶዎች ቤተሰቦቿ በመለጠፋቸው፣ 700 ያህል የፌስቡክ ጓደኞቿ ሼር አድርገዋቸዋል፡፡ ይህም እሷን አበሳጭቷታል፡፡
የወጣቷ ጠበቃ ሚቼል ራሚ እንደሚሉት፣ ወላጆቿ ከ500 ያላነሱ ፎቶዎችን ከእሷ ዕውቅና ውጪ በፌስቡካቸው ለጥፈዋል፡፡ ይህም ወጣቷ በፍርድ ቤት እንድታሸንፍ ዕድል ይፈጥርላታል፡፡ ሆኖም አባቷ ‹‹ፎቶዎቹን ራሴ ካነሳኋቸው የመለጠፍ መብት አለኝ፤›› ብሎ እንደሚያምን ገልጿል፡፡
* * *
ሰውና እባብ
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው በጉዞ ላይ እያለ ከአንድ ወንዝ ዳርቻ ላይ ከአንድ እባብ ጋር ተገናኘ፡፡ እባቡም ሰውየው ወንዙን እንዲያሻግረው ጠየቀው፡፡
ሰውየውም “እንዴት አድርጌ?” ብሎ ሲጠይቀው እባቡም “አንገትህ ላይ አድርገኝ፤” አለው፡፡
ሰውየው እባቡን ቢፈራውም አንገቱ ላይ አድርጎ አሻገረው፡፡
ወንዙን ከተሻገሩም በኋላ ሰውየው እባቡን “በል አሁን ከአንገቴ ላይ ውረድልኝ፤” ሲለው እባቡ ግን አልወርድም፣ እንዲያውም ወደ ዳኛ እንሂድ አለው፤”
ሰውየውም በዚህ ተስማምቶ ወደ ዳኛ ሲሄድ ዳኛው ጅብ ነበርና ጅቡ ጉዳያቸውን ካዳመጠ በኋላ እባቡን ስለፈራው “እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ ፍርድ መስጠት አልችልምና ወደ ጦጣዋ ሂዱ፤” አላቸው፡፡ ከዚያም ወደ ጦጣዋ ዘንድ ሄደው ጉዳያቸውን ሲያቀርቡ ጦጣዋ “እሺ፣ መጀመሪያ ግን ዛፍ ላይ ልውጣ፤” ስትላቸው እነርሱም “እሺ” አሏት፡፡
ከዚያም ጦጣዋ “በሉ አሁን ሁለታችሁም መጀመሪያ መሬት ላይ መሆን አለባችሁ፤” አለቻቸው፡፡
እናም እባቡ መሬት ወረደ፡፡
በዚህ ጊዜ ጦጣዋ ሰውየውን “ታዲያ አሁን ምን ትጠብቃለህ? በእጅህ ቢላዋ ይዘሃል፡፡ እባቡም መሬት ላይ ነው፤” አለችው፡፡ ሰውየውም የጦጣዋ ንግግር ስለገባው እባቡን ገደለው፡፡
- ‹‹የትግራይ ተረት›› ከኢትዮጵያ ተረቶች ገጽ የተወሰደ