የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት መስከረም ባተ፡፡ ሰኔ ግም ብሎ የሐምሌን ጨለማ አልፎ፣ ዕኝኝ ብላን (ከነሐሴ 28 ቀን እስከ 30 ባለማቋረጥ የሚዘንበው) ጎርፍ በጳጉሜን በኩል ክረምቱ ሲሻገር፣ መስከረምን የምታደምቀው ዐደይ አበባ ትከሰታለች፡፡ በመስከረም የምትፈነዳውና ለኢትዮጵያ ምድር ጌጧ ሽልማቷም የሆነችው ዐደይ አበባ እንደ አለቃ ደስታ ተክለወልድ ‹‹ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት›› ዐደይ ሲፈታ የበጨጨ፣ ብጫ የሆነ አበባ ነው፡፡ ግሱ ‹‹ዐደየ›› በጨጨ፣ ብጫ መሰለ፤ ነጣ፣ ነጭ ሆነ ሲሉም ይፈቱታል፡፡ በኦሮምኛ ነጭን ዐዲ፣ ፀሐይን ዐዱ የሚለው ከዚህ የወጣ ነው ሲሉም ያክሉበታል፡፡
ስለዐደይ አበባ ተክል ምንነት ሳይንሳዊ መግለጫ ያዘጋጁት ዶ/ር ከበደ ታደሰ ‹‹የኢትዮጵያ ወፍ ዘራሽ አበቦች (Wild Flowers for Ethiopia) በተሰኘው መጽሐፋቸው፣ ስለዐደይ አበባ ከምትበቅልበት ከተለያዩ ከፍታዎች አንፃር በሁለት መልክ እንዲህ ጽፈዋል፡፡
የተከፋፈሉ ሰፊ ላይዶ ቅጠሎችና ስምንት የተበተኑ መልካበቦች ያሉት ዓመታዊ ሃመልማል፣ ከመንገድ ዳር ዳርና ከቃሊም እንዲሁም በከፍተኛና ድንጋያማ ተዳፋት፣ ከ400 እስከ 2,700 ሜትር ከፍታ ላይ ይበቅላል፤ ከመስከረም እስከ ታኅሣሥም ያብባል፡፡ በሌላ በኩልም እስከ ኅዳር ድረስ የሚያብበው የሚገኘው ከ2,000 እስከ 3,600 ሜትር ከፍታ ላይ ነው፡፡ ይህንንም ዶ/ር ከበደ ሲገልጹት፣ ዐደይ አበባ ረጃጅም ግንድና ሰፋ ያለ ላይዶ ቅርጽ ያላቸው ቅጠሎች ያሉት ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ የሚበቅል ከረም ሃመልማል ነው ይሉታል፡፡ መሀላቸው ብርቱካንማ የሆነ ብጫ አበቦች በግንዱ ጫፍ ሰብሰብ ብለው ይታያል፡፡
ድሮ ድሮ ‹‹ዐደይ ዐደይ የመስከረም፤ ሱስንዮስ ንጉሠ ሮም›› ይባል ነበር፡፡ ‹‹ዐደይ ዐደይ የመስከረም፤ እንዳንቺ ያለ የለም››ም ተብሏል፡፡ ‹‹መስከረም መስከረም የወራቱ ጌታ፤ አበቦች ተመኙ ካንተ ጋር ጨዋታ›› እየተባለም ድሮ በመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ ቤት ተማሪዎች ሲዘምሩ እንደነበር መጽሐፋቸው ይናገራል፡፡