Friday, June 9, 2023

የኢሕአዴግ አንጋፋ አመራሮች ምን እያሉ ነው?

- Advertisement -spot_img

በብዛት የተነበቡ

በኦሮሚያና በአማራ ብሔራዊ ክልሎች ዓመቱን ሙሉ ማለት ይቻላል የተለያዩ ተቃውሞዎችና የአመጽ እንቅስቃሴዎች ተከስተዋል፡፡ በሒደቱ የሰዎች ሕይወት ጠፍቷል፣ የአካል ጉዳት ተከስቷል፣ ንብረት ወድሟል፡፡ በዜጎች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ላይም ተፅዕኖ ተፈጥሯል፡፡

በአገሪቱ በሁለቱ ትልልቅ ክልሎች ይህን መሰል ክስተት መፈጠሩ ምን ያመለክታል? የሥርዓቱ ዕጣ ፈንታን ይወስናል? ምን ዓይነት ጊዜያዊና ዘላቂ ተፅዕኖ ይፈጥራል? በሚል ጉዳዩ ይመለከተናል ያሉ የአገር ውስጥና የውጭ ኃይሎች የውይይት አጀንዳ ከፈጠሩ ሰነባብተዋል፡፡

ዜጎች፣ ቡድኖችና የተለያዩ ተቋማት በጉዳዩ ላይ የራሳቸውን ትንታኔ በማቅረቡ ላይም ይገኛሉ፡፡ መንግሥትም ለጉዳዩ እየሰጠ ካለው ምላሽ በተጨማሪ የራሱን ማብራሪያ ሲሰጥ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ መንግሥት መሥርቶ አገሪቱን መምራት ከጀመረ 25 ዓመታት ያለፉት ኢሕአዴግም፣ በቅርቡ ጉዳዩን ገምግሜ የመፍትሔ አቅጣጫ አስቀምጫለሁ ማለቱ ይታወቃል፡፡

ከቀናት በፊት የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች የሕወሓት፣ የብአዴን፣ የኦሕዴድና የዴኢሕዴግ አንጋፋ አመራሮች የሆኑት አቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ አቶ በረከት ስምኦን፣ አቶ አባዱላ ገመዳና ዶ/ር ካሱ ኢላላ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሸን (ኢቢሲ) ጋር ባደረጉት ሰፋ ያለ ውይይት በእነዚሁ ጉዳዮች ላይ የበኩላቸውን ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

እነዚህ አንጋፋ የኢሕአዴግ አመራሮች የተቃውሞዎቹና የአመፅ እንቅስቃሴዎቹ የመንግሥት የልማትና የዕድገት ስኬቶች የወለዷቸው እንደሆኑ በመግለጽ፣ በቅርቡ በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምና በኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚና ማዕከላዊ ምክር ቤት የተሰጡ መግለጫዎች ላይ የተቀመጠውን ጭብጥ ደግመውታል፡፡

በርካታ አስተያየት ሰጪዎች ችግሮቹ በሥርዓቱ ላይ ያሉ ክፍተቶችን ያጋለጡና ማሻሻያ አስፈላጊ እንደሆነ ያሳዩ ናቸው በማለት ይገልጻሉ፡፡ ኢሕአዴግ በኪራይ ሰብሳቢነት፣ በዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብት ይዞታ እንዲሁም የጠባብነትና የትምህክተኝነት አመለካከቶች ላይ ክፍተቶች እንደተከሰቱ በመግለጽ ጉዳዩ የመልካም አስተዳደርና የአፈጻጸም ክፍተት እንጂ ከፖሊሲና ከሥርዓቱ መሠረታዊ መርሆች ጋር የተያያዘ አይደለም በማለት ራሱን ይከላከላል፡፡

የአንጋፋዎቹ ማብራሪያም በዚሁ መንፈስ የተሰጠ ነው፡፡ አቶ በረከት ኢትዮጵያ በኢሕአዴግ አመራር በመነሳት ላይ ያለችና የቆዩ ችግሮቹን እየፈታች ያለች አገር እንደሆነች ገልጸዋል፡፡ በአቶ በረከት ገለጻ እነዚህ የቆዩ ችግሮች ብዝኃነትን በአግባቡ ማስተናገድ፣ የሰብዓዊ መብትና የዴሞክራሲ ይዞታ፣ የኢኮኖሚ ዕድገትና የሰላም መረጋገጥ ናቸው፡፡ ‹‹ብዝኃነትን በአግባቡ ማስተናገድ ጀምረናል፡፡ ዴሞክራሲን ተግባራዊ ማድረግና ማስፋት ችለናል፡፡ አሁን የአገሪቱ ፀጋዎችን በደንብ ማልማትና ሀብት ማፍራት ጀምራለች፡፡ ግጭቶችን ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመከተል እየፈታን በመሆኑ ውጫያዊና ውስጣዊ ሰላም ተከብሯል፤›› ብለዋል፡፡

በአገሪቱ እየተከሰቱ ያሉ የተቃውሞና የአመፅ እንቅስቃሴዎች ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱና የፌዴራል ሥርዓቱ በአግባቡ እየዋለ አይደለም በማለት ተቃውሞ ያቀረቡበት አጋጣሚን አስተናግደዋል፡፡ አቶ ዓባይ ግን ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱም ሆነ የፌዴራል ሥርዓቱ በአግባቡ እየተተረጎመ መሆኑን በመግለጽ ተከራክረዋል፡፡ አሁን በኢሕአዴግ የተመዘገበው ስኬት ከቀደመው ሥርዓት ችግሮች አንፃር ቢቃኝ ልዩነቱን በግልጽ ማየት እንደሚቻልም አስገንዝበዋል፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ያስወገደው የፖለቲካ ሥርዓት ልዩነትን በኃይል የሚጨፈልቅ፣ የፖለቲካ ልዩነትን እንደ ወንጀልና ኃጢያት የሚወስድ ነበር፡፡ አሁን የሥልጣን ክፍፍልና የመንግሥት ተቋማት ሚዛናዊ የሆነ የቁጥጥር ሥርዓት ተዘርግቷል፡፡ ራሳቸውን የቻሉ ገለልተኛ የፌዴራልና የክልል ምክር ቤቶችና ፍርድ ቤቶች ተቋቁመዋል፡፡ በሕግ የሚመራ አስፈጻሚ አካላትም አሉ፤›› ብለዋል፡፡

ኢሕአዴግ የሐሳብ ልዩነትን እንደማይቀበልና ተቃዋሚዎቹን በኃይል ለማጥፋት ይጥራል በሚል በተደጋጋሚ እንደሚተች ይታወቃል፡፡ አቶ ዓባይ  ግን ክፍተት ካለ የሥርዓቱ መለያ ሳይሆን በበቂ ሁኔታ ያለመተግበር ችግር እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ ‹‹ሥርዓቱ ሕገ መንግሥቱን በአጥጋቢ ደረጃ ቢተገብርም ያልዳበሩና የሚፈቱ ጉዳዮች አሉ፤›› ብለዋል፡፡

አቶ አባዱላም ከአቶ ዓባይ ጋር ይስማማሉ፡፡ የአገሪቱ የ25 ዓመታት ጉዞ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱ የሚሠራ መሆኑን በተግባር እንዳረጋገጠም አመልክተዋል፡፡ ‹‹የፌዴራል ሥርዓቶችን የሚሠራ፣ ምንም እንከን የሌለውና ተጠናክሮ የሚቀጥል ነው፤›› ብለዋል፡፡

አሁን አገሪቱ የዕድገት ተምሳሌት እንደሆነች ያመለከቱት አቶ አባዱላ ልማቱ የፈጠረውን ኃይል ፍላጎት ማሟላት ከባድ ፈተና መፍጠሩ ግን አምነዋል፡፡ ችግሩም በማስፈጸም አቅም ውስንነትና በገንዘብ እጦት የሚገለጽ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡

ዶ/ር ካሱ በበኩላቸው የአገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ዴሞክራሲያዊ ሰላም ማምጣቱን ገልጸዋል፡፡ ‹‹ድሮ ድርቅ ሲኖር ሕዝብ ይረግፍ ነበር፤›› ያሉት ዶ/ር ካሱ፣ አሁን ይህን የመቋቋም አቅም መዳበሩ አገሪቱ በትክክለኛ አቅጣጫ ላይ እንደምትገኝ አመላካች እንደሆነ አስገንዝበዋል፡፡ ‹‹ወደ መካከለኛ ገቢ ለመግባት አስተማማኝ ሁኔታ ላይ ነው ያለነው፤›› ብለዋል፡፡

የሕዝቡ ከድህነት የመውጣት ፍላጎት በብዙ ሺሕ የሚቆጠር ልማታዊ ባለሀብት እያፈራ እንደሆነም ገልጸዋል፡፡ ኅብረተሰቡም ሞጋችና መብቱን ጠያቂ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡

አቶ በረከት ኢትዮጵያ የጀመረችው ዕድገት ዘላቂነት እንዳለው ማሳያው በልማቱ እየመጣ ያለው ከአገር ውስጥ ሀብት መሆኑ ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ዛሬ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ሀብት ከራሳችን አገራዊ ምንጮች እያገኘን ነው፡፡ ከግብርናችን፣ ከአገልግሎት ዘርፍ፣ ከኢንዱስትሪው ሀብት እየፈጠርን ነው፡፡ የማንኛውም አገር ኢንዱስትሪ ልማት፣ የግብርና መስፋፋት፣ የአገልግሎት ዘርፍ መጠናከር የሚወሰነው የአገር ዕድገቱን ሊያፋጥንለት የሚችል ካፒታል ከራሱ ምንጮች ማግኘት ከቻለ ብቻ ነው፡፡ እኛ በሚሊዮን የሚቆጠር ጉልበት ያለው አርሶ አደር አለን፡፡ የሰሜን ምሥራቅ እስያ አገሮች ተሞክሮ የሚያሳየው በመሬት የተከፈለ፣ በጥሩ ፖሊሲዎች የሚደገፍ፣ መንግሥት የቴክኖሎጂና የብድር አቅርቦት የሚያሟላለት አነስተኛ አርሶ አደር በጣም ሰፊ አገራዊ ሀብት የመፍጠር አቅም ይኖረዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ የ1980ዎቹን ቻይና ትመስላለች፡፡ ቻይና ትልቁን ዕድገት ለማምጣት በተዘጋጀችበት ጊዜ የነበረችበት ደረጃ ላይ እንደደረስን አኃዛዊ መረጃዎች ያሳያሉ፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

በመንግሥት ጥረት ፍላጎቱን በደንብ የሚያውቅና የሚራመድ ኅብረተሰብ መፍጠሩን ያመለከቱት አቶ በረከት፣ መንግሥት አቅሙን አዲስ ከፈጠረው ኃይል ፍላጎት ጋር ለማጣጣም አቅሙን ሊያሳድግ ይገባል ብለዋል፡፡ ‹‹ከጊዜ ወደ ጊዜ የተማረ ኅብረተሰብ እየፈጠርን ነው የመጣነው፡፡ ይኼን የተማረና በዴሞክራሲውም የዳበረ አመለካከት ያለው ኅብረተሰብ ማስተዳደር ከመንግሥት በኩል የማያቋርጥ ብቃትና መሻሻል ይጠይቃል፡፡ ሕዝቡ አዳዲስ ፍላጎቶች ይዞ ይመጣል፡፡ ወጣቶችም አዳዲስ ፍላጎት ይዘው ይንቀሳቀሳሉ፤›› ሲሉም አብራርተዋል፡፡

ዕድገቱ የወለዳቸው ካሏቸው ፈተናዎች በተጨማሪ በመንግሥት በኩል አላግባብ የመጠቀም ዝንባሌም ሌላ ፈተና መሆኑን አቶ በረከት አምነዋል፡፡ ለሕዝብ የቆመ መንግሥት ግንባታ ላይ ግድፈት ቀጠለ ማለት ወደ ኋላ የመመለስ አደጋ የሚደቅን እንደሆነም አክለዋል፡፡

አቶ ዓባይ የተቃውሞና የአመፅ እንቅስቃሴው አንዱ መነሻ ምክንያት የገበሬዎች መፈናቀልም ቢሆን የልማቱ ውጤት እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ ‹‹በበርካታ አካባቢዎች ተገቢ ካሳ ተከፍሏል፡፡ መልሶ ማቋቋም ተከናውኗል፡፡ በሌሎች አንዳንድ አካባቢዎች ግን በአመራርና በአስተዳደር ክፍተት ይህ ሳይከናወን ቀርቷል፤›› ብለዋል፡፡

በፓርቲም ሆነ በመንግሥት ደረጃ የአመራር ድክመትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች መነሳታቸውን ያስታወሱ አቶ ዓባይ፣ የፍትሕ አካላት ራሳቸው የብቃት፣ የተጠያቂነትና የውጤታማነት ችግር ያለባቸው መሆኑ ነገሮችን እንዳባባሰ አመልክተዋል፡፡ ከእነዚህ ጋር የተያያዙ ጥያቄዎች ተገቢ በመሆናቸው ምላሽ እንደሚያስፈልጋቸው ገልጸዋል፡፡ ‹‹ነገር ግን ተገቢ ያልሆኑ ጥያቄዎችም አሉ፤›› ብለዋል፡፡

በተቃዋሚዎቹ የሕወሓት የበላይነት አንዱ ጥያቄ ነበር፡፡ የሕወሓት መሥራች የሆኑት አቶ ዓባይ ግን ይህን ጉዳይ አጣጥለውታል፡፡ ‹‹አንዱ ብሔር የበላይ፣ ሌላው የበታች አይደለም፡፡ ፖሊሲውም ሆነ ትግበራው ፍትሐዊና ተመጣጣኝ ልማት ነው፡፡ የጎደለ ነገር ካለ ሁሉም ጋር ነው የጎደለው፤›› ብለዋል፡፡ ዶ/ር ካሱም የትግራይ የበላይነት እውነትነት የሌለው ነው ብለዋል፡፡ መከላከያውም በአንድ ብሔር የበላይነት ነው መባሉ ስህተትና ፍትሐዊ በሆነ መልኩ የሁሉም ብሔረሰቦች ተዋጽኦ የተንፀባረቀበት ነው ብለዋል፡፡

አንጋፋዎቹ አመራሮች ሙስና በግለሰብ ደረጃ ቢታይም የሥርዓቱ መገለጫ አይደለም ሲሉ ተከራክረዋል፡፡ አቶ አባዱላ ‹‹አሁን የተፈጠረው ነገር የመንግሥትን ድክመት የሚያሳይ አይደለም፡፡ መንግሥታዊ ሙስና አይደለም ያለው፡፡ ፖሊሲዎችንና ተቋሞችን ለሙስና የሚመቹ አይደሉም፡፡ ለሙስና የማይመቹ አደረጃቶችና አሠራሮች አሉን፡፡ አሁን የተከሰተው ነገር እዚህ አገር ሙሰኛ ሆኖ መቀጠል እንደማይቻል ማሳያ ነው፤›› ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል የተነሳው ተቃውሞ መነሻ ምክንያት የወልቃይት የማንነት ጥያቄ መሆኑ ይታወሳል፡፡ በጉዳዩ ላይ አቶ ዓባይ ሲናገሩ፣ ‹‹ኢሕአዴግ ከመጣ በኋላ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ሌሎች ክልሎችም ሲካለሉ በድሮው አከላለል ትግራይ ውስጥ የነበረ ወደ አማራ ክልል የሄደ፣ ወደ አፋር ክልል የሄደ፣ ወደ ትግራይ ክልል ደግሞ የመጣ፣ ወደ ኦሮሚያ የሄደ ቦታ አለ፡፡ ሽግሽጎች ተደርገዋል፡፡ መስፈርቱን መሠረት በማድረግ በሕዝብ አሰፋፈርና በቋንቋ ነው የተወሰነው፡፡ ወልቃይት በትግራይ ክልል የተከለለው በዚያ መሠረት ነው፤›› ብለዋል፡፡ አሁን ጥያቄ ካለ ለትግራይ ክልል መቅረብና መታየት እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

በኦሮሚያ በተመሳሳይ ተቃውሞ የጀመረው የአዲስ አበባና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላንን በመቃወም ነበር፡፡ ተቃውሞው እየበረታ መጥቶ መንግሥት ማስተር ፕላኑ እንደቀረ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡ የኢሕአዴግ አንጋፋ አመራሮች ግን ማስተር ፕላኑ ቀረ ከማለት ይልቅ ‹እንዲዘገይ የተደረገው› የሚል ገለጻ ተጠቅመዋል፡፡ አቶ ዓባይ ‹‹ማስተር ፕላኑ አዲስ አበባንና በአዲስ አበባ ዙሪያ ያለውን የልዩ ዞን ሕዝብ የሚጠቅም ነው፡፡ ገበያው፣ ትራንስፖርቱ፣ መሠረተ ልማቱ ተጠቃሚ የሚያደርገው ክፍተት ነው፡፡ የአመራር ችግር ነው፡፡ ስለዚህ ሕዝቡ እስኪረዳው ድረስ ይቆይ የተባለው ለዚህ ነው፡፡ እንጂ ስህተት ስለሆነ አይደለም፤›› ብለዋል፡፡

ክፍተት የፈጠረው በመንግሥትና በገዥው ፓርቲ ብቻ ሳይሆን በሕዝቡና በዴሞክራሲ ተቋማት ጭምር እንደሆነ አቶ ዓባይ ተከራክረዋል፡፡ ‹‹ጥያቄዎችን ሰላማዊና ሕጋዊ በሆነ መልኩ የመጠየቅና የማስተናገድ ልምድ ተቋማዊና ባህል ልናደርገው እንችል ነበር፡፡ ከአሁን በኋላም ልናደርገው ይገባል፡፡ የዴሞክራሲ ተቋማት በአግባቡ ቢሠሩ ኖሮ መንግሥት ጥያቄዎችን በአግባቡና በወቅቱ እንዲፈታ ጫና ያደርጉ ነበር፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

አቶ ዓባይ ተቃውሞዎቹንና የአመፅ እንቅስቃሴዎቹን ‹የህዳሴ ጉዞ ማዕቀፍ ውስጥ የተፈጠሩ ጊዜያዊ ችግሮች ናቸው፤›› ብለዋል፡፡ ሌሎቹ አመራሮችም ችግሮቹ የአገር ህልውና ይፈታተናሉ በሚል የቀሪውን ትንታኔ በመቃወም በቀላሉ የሚፈቱ ናቸው ሲሉ ደምድመዋል፡፡

 

 

spot_img
- Advertisement -

ትኩስ ጽሑፎች

ተዛማጅ ጽሑፎች

- Advertisement -
- Advertisement -