አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን መጨረሻ ድረስ ለቱሪስቶች ጭምር አገልግሎት መስጠት የሚችሉ፣ ዘመናዊና ደረጃቸውን የጠበቁ 3,000 ተንቀሳቃሽ መፀዳጃ ቤቶች ይሠራሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል 90 ያህሉ በሚቀጥለው ዓመት ተገንብተው ጥቅም ላይ እንደሚውሉ የከተማው አስተዳደር የውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን የፍሳሽ ማንሳት ንዑስ የሥራ ሒደት መሪ አስታወቁ፡፡
የሥራ ሒደት መሪው አቶ ሙሉዓለም ብርሃነ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በአሥሩም ክፍለ ከተሞች የሚሠሩት የሕዝብ መፀዳጃ ቤቶች የገላ መታጠቢያ፣ መዝናኛ ሥፍራዎችና ተጨማሪ የገቢ ማስገኚያዎች ይኖራቸዋል፡፡
ከዚህም ሌላ መገናኛ አካባቢ የገላ መታጠቢያና መፀዳጃ ቤቶችን ያካተተ ባለአንድ ፎቅ ማዕከል በመገንባት ላይ መሆኑን ገልጸው፣ በሚቀጥለው ዓመት ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር አስረድተዋል፡፡
የየካ ክፍለ ከተማ የመሬት ልማት ጽሕፈት ቤት በሰጠው ባዶ ቦታ ላይ በመገንባት ላይ ያለው ማዕከል እንደማሳያ ሲሆን፣ በቀጣይም በሌሎች ክፍለ ከተሞች ውስጥ ለማስፋፋት ታቅዷል፡፡
ቀደም ባሉት ዓመታት በብሎኬት የተሠሩ 66 የሕዝብ መፀዳጃ ቤቶች፣ በ2008 ዓ.ም. 27 አዳዲስ ተመሳሳይ መፀዳጃ ቤቶች እንደተገነቡና ይህም የመፀዳጃ ቤቶችን ቁጥር ወደ 93 ከፍ ማድረጉን፣ በአሥሩም ክፍለ ከተሞች 114 ተንቀሳቃሽ መፀዳጃ ቤቶች መገንባታቸውንም ተናግረዋል፡፡
መፀዳጃ ቤቶቹ በአነስተኛና ጥቃቅን ለተደራጁ ወጣቶች በኮንትራት የተሰጡ ሲሆን፣ ከአገልግሎቱ ከሚገኘው ገቢ ለሠራተኛ ደመወዝና ለአላቂ የንጽሕና መጠበቂያ መግዢያ ወጪ ሆኖ ከሚተርፈው ገንዘብ፣ አሥር ከመቶ ያህሉ ለባለሥልጣኑ ገቢ እንደሚደረግ አስታውቀዋል፡፡
ኅብረተሰቡ በመፀዳጃ ቤቶች የመጠቀም ባህሉ ገና እንዳልዳበረ፣ በዚህም የተነሳ በየቦታው እንደሚፀዳዳ፣ ይህን ለመከላከል ባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ ከደንብ ማስከበር ጽሕፈት ቤት ጋር በመቀናጀት እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የመፀዳጃ ቤቶች ዙሪያ አረንጓዴ የተደረገ ሲሆን፣ በሥፍራው ለሚቀመጡ ሰዎች ተመጣጣኝ በሆነ ክፍያ ቡና ይቀርባል፡፡ ጋዜጣና መጽሔትም ለማቅረብ ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡
በሁሉም ክፍለ ከተሞች ከተቋቋሙት የሕዝብ መፀዳጃ ቤቶች መካከል በጉለሌ ክፍለ ከተማ አስኮ መስመር ጄኔራል ዊንጌት ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ ባለው አደባባይ አቅራቢያ የሚገኘውና ስምንት ወጣቶች በአነስተኛና ጥቃቅን ተደራጅተው የሚሠሩበት መፀዳጃ ቤት ተጠቃሽ ነው፡፡
የማኅበሩ ፕሬዚዳንት እንዳብራራው፣ አገልግሎቱን የሚሰጡት በሁለት ፈረቃዎች ተደራጅተው ነው፡፡ መፀዳጃ ቤቱ ከንጋቱ 12 እስክ ምሽቱ ሁለት ሰዓት ክፍት መሆኑንና በየዕለቱም እስከ 100 የሚደርሱ ሰዎች እንደሚጠቀሙ፣ ከተጠቃሚዎቹም መካከል የሴቶች ብዛት በቀን ከአምስት እንደማይበልጥ አስረድቷል፡፡
ከተጠቃሚዎች ከሚገኘው ገቢ ውስጥ በሥራው ላይ ለተሰማራው ለእያንዳንዱ ወጣት በወር እስከ 420 ብር ክፍያ እንደሚፈጸምም አመልክቷል፡፡