Monday, December 4, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜና‹‹ሁሉም የፀጥታ ኃይሎች የሕግ የበላይነት እንዲያስከብሩ አዝዣለሁ›› ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ

‹‹ሁሉም የፀጥታ ኃይሎች የሕግ የበላይነት እንዲያስከብሩ አዝዣለሁ›› ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ

ቀን:

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማክሰኞ ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ለመንግሥት መገናኛ ብዙኃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የፀጥታ ኃይሎች የሕግ የበላይነትን እንዲያስከብሩ ትዕዛዝ መስጠታቸውን አስታወቁ፡፡

በአሁኑ ወቅት በተለይ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች በተነሱ ጥያቄዎች ያልተገቡ ሕገወጥ ድርጊቶች እየተፈጸሙ እንደሆነና እነዚህን ችግሮች ለመፍታት የተለያዩ የመፍትሔ ዕርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸው፣ የሕግ የበላይነትን እንዲያስከብሩ ለሁሉም የፀጥታ ኃይሎች ትዕዛዝ መስጠታቸውን አስታውቀዋል፡፡

በትግራይና በአማራ ክልሎች የወሰንና የማንነት ጥያቄና እስካሁንም ችግሩ ላለመፈታቱ የየክልሉ አመራሮች ተጠያቂ ይሆናሉ በማለት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸው፣ ‹‹ኢሕአዴግ ብቃቱ የሚለካው ችግሮች ሲያጋጥሙት ብቻ አይደለም፡፡ ችግሮች ሲያጋጥሙት በሚያካሂደው ሳይንሳዊ ትንታኔ ተመሥርቶ በሚወስደው ዕርምጃ ነው፤›› በማለት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡

‹‹በእኔ እምነት ኢሕአዴግ ብቃቱ አልተሟጠጠም፤›› ብለው፣ ‹‹እዚህም እዚያም በተነሱ ግጭቶች አገሪቱ ትፈርሳለች የሚለው ሥጋት መሠረተ ቢስ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በፅኑ መሠረት ላይ ትገኛለች፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡  

ኢሕአዴግ ብቻ ይህ ችግር እንዳልገጠመው፣ ይልቁኑም ሌሎች ልማታዊ መንግሥታት ይህ ችግር አጋጥሟቸው እንደነበር ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡

‹‹ቱርክ ፈጣን ልማት ያመጣ መንግሥት ነው፡፡ አሁን ግን ችግር ገጥሞታል፡፡ ብራዚልና ኮሪያም ባካሄዱት ልማት ከችግር ወጥተዋል፡፡ አሁን ደግሞ በተለይ ብራዚል ችግር አጋጥሟታል፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ኢሕአዴግ ከዓመታት በፊት ልማቱን ሲጀምር 40 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ከድህነት ወለል በታች ነበሩ፡፡ ነገር ግን አሁን ከድህነት ወለል በታች ያሉ ሕዝቦች ቁጥራቸው በግማሽ ቀንሶ ወደ 20 ሚሊዮን ወርዷል፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ከታዳጊ ኢኮኖሚ ወዳደገ ኢኮኖሚ እስኪደርስ ድረስ ችግር ሊያጋጥም ይችላል ብለዋል፡፡

ነገር ግን ኢሕአዴግ ለተፈጠሩ ችግሮች ግምገማ ካካሄደ በኋላ ለችግሩ መባባስ የራሱ አመራሮችም እጅ እንዳለበት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸው፣ ዕርምጃም እንደሚወሰድ አስታውቀዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ኢትዮጵያ የራሷ የተፈጥሮ ሀብት እንዳትጠቀም የውጭ ኃይሎች፣ በተለይ በውጭ ለሚኖሩ ጽንፈኛ ዳያስፖራ አባላት ከፍተኛ ገንዘብ መስጠታቸው በመረጃ መረጋገጡን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን አልገለጹም፡፡

እነዚህ ዳያስፖራዎችም አብዛኛው ለራሳቸው ካስቀሩ በኋላ ከፊሉን ወደዚህ በመላክ ብጥብጥ እየፈጠሩ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኃይለ ማርያም ከአዲስ አበባና ከኦሮሚያ ልዩ ዞን ማስተር ፕላን ጋር ተያይዞ የተነሳው ችግር ላይ ምንም ባይሉም፣ ከሕዝብ ጋር በተሠራው ሥራ ግን መረጋጋት መፈጠሩን አመልክተዋል፡፡    

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

በዓለም አቀፍ ደረጃ ሕይወታቸውን በኤድስ ምክንያት ላጡ ሰዎች 35ኛ ዓመት መታሰቢያ

ያለፍንበትን እያስታወስን በቁርጠኝነት ወደፊት እንጓዝ - በኧርቪን ጄ ማሲንጋ (አምባሳደር) በየዓመቱ...

እዚያ ድሮን… እዚህ ድሮን…

በዳንኤል ካሳሁን (ዶ/ር) ተዓምራዊው የማዕበል ቅልበሳ “በሕግ ማስከበር” ዘመቻው “በቃ የተበተነ...

ለፈርጀ ብዙ የማንነት ንቃተ ህሊናችን የሚጠቅሙ ጥቂት ፍሬ ነገሮች

በበቀለ ሹሜ ከጨቅላነት ጅምሮ ያለ የእያንዳንዳችን የሰብዕና አገነባብ ከቤተሰብ እስከ...