በዓለም አቀፍ እግር ኳስ ውስጥ ‹‹ምስጋና›› የሚባል ነገር የለም የሚሉ ታዋቂና ለእግር ኳሱ ቅርበት ያላቸው ሰዎች ሲናገሩ ይደመጣሉ፡፡ በታላላቅ የእግር ኳስ ውድድር መድረኮች ላይ የተለያዩ ውድድሮችን በማሸነፍ ትልቅ ገድል የፈጸሙ አሠልጣኞች የሁለት ጨዋታ ስህተት የሠሩትን ግንብ የማፍረስ ያህል በደጋፊዎች ሲብጠለጠሉና ከኃላፊነታቸው እንዲወርዱ ሲደረግ መመልከት አዲስ አይደለም፡፡
የክለብን ደረጃ ለማሻሻል ወደ ተለያዩ ክለቦች የሚዘዋወሩት አሠልጣኞች ተጫዋቾችን ወደ አሸናፊነት የማምጣት ትልቅ ኃላፊነት ይጣልባቸዋል፡፡ በአንፃሩ ክለቦች የሚያስቀምጡት ዕቅድና አሠልጣኙ የሚያመጣው የጨዋታ ፍልስፍና ውጤት አሳማኝ መሆን ይኖርበታል፡፡ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ምንም እንኳ መቆራረጥ የበዛበትና የደጋፊዎች ረብሻ ገጽታውን የበለጠ እያደበዘዘ ቢመጣም ክለቦች አሠልጣኞችን በመሾምና በመሻር ተጠምደዋል፡፡
ስምንተኛ ሳምንቱን የያዘው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር ገና በጅምር የአራት አሠልጣኞችን ስንብት አሳይቷል፡፡ በፕሪሚየር ሊጉ ግልጽ ያልሆኑ የአሠልጣኝ ቅጥር የሚያከናውኑ ክለቦች ለስንበቱም ምላሽ ሲሰጡ አይስተዋልም፡፡
በሊጉ ላይ ከ17 በላይ አሠልጣኞች ሲኖሩ እነዚህም ባለሙያዎች ከአንዱ ክለብ ወደ አንዱ ክለብ ሲዘዋወሩ በመመልከት ውጪ ዕቅዳቸውንና ግባቸው ሲተገብር አይታይም፡፡
ክረምት ላይ አርባ ምንጭን የተረከቡት አሠልጣኝ ፀጋዬ ኪዳነማርያምን ጨምሮ የቀድሞ የሐዋሳ፣ የአዳማና የሲዳማ ቡናው አሠልጣኝ ዘለዓለም ሽፈራው ከድሬዳዋ፣ ዘጠኝ ዓመታትን በወላይታ ድቻ ያሳለፈው መሳይ ተፈሪና በኤሌክትሪክ ረጅም ቆይታ ያደረገው ብርሃኑ ባዩ ስንብት ተገልጸዋል፡፡ የፕሪሚየር ሊግ ክለብ አሠልጣኞቹ ከሰባት ጨዋታዎች ከአንድ በላይ ማሸነፍ ባለመቻላቸው በክለቦቹ አመራሮች ከኃላፊነታቸው እንዲነሱ ተደርገዋል፡፡
በአሠልጣኞች ቅጥር ላይ ቅሬታ የሚያነሱት የስፖርት ቤተሰቦች ክለቦች ግባቸውን ያለማወቅ ችግር ሲገጥማቸው ይስተዋላል የሚሉ አሉ፡፡
አሠልጣኞች ወደ አንድ ክለብ ፊርማቸውን ሲያኖሩ የተጫዋቾች አቅም በመገንዘብ የተለያዩ ታክቲኮችን በመከተል ክለቡን ወደ ተሻለ ደረጃ ማምጣት እንዳለባቸው ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ቅጥር መሠረት ክለቦች ቀድመው የሚያስቀምጡት መስፈርት ባለመኖሩ አሠልጣኞች ክለቦችን ወጥ የሆነ አቋም እንዳይኖራቸው ሲያደርጓቸው ይስተዋላል የሚል አስተያየት ይሰጣል፡፡
ባለፉት የሩብ ምዕት ዓመታት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ቆይታ ውስጥ የአንድ የክለብ የበላይነት መኖሩ ማሳያ እንደሆነ ባለሙያዎች ያስቀምጣሉ፡፡
ከዚህም ባሻገር ልምድ አላቸው የሚባሉት አሠልጣኞች ከተለያዩ አካላት ጋር በጥቅም መተሳሰራቸውም ወደ ፈለጉት ክለብ በመዘዋወር ኪሳቸውን ከመሙላት በቀር ግዴለሽ መሆናቸውም ይነገራል፡፡
በተጨማሪም የክለብ አመራሮች አሠልጣኙ በቀድሞ ክለቡ የሠራውን ነገር በጥልቀት አለመመልከት ፍላጎታቸውንና ክፍተታቸውን ለይተው ያለማወቅ ችግር የተሻለ የእግር ኳስ ለውጥ እንዳይታይ ማነቆ ሆኖታል ይባላል፡፡
አሠልጣኞቹ ከአንድ ክለብ ወደ ሌላኛው ሲዘዋወሩ ክለቦች ያላቸው ተመሳሳይነት ‹‹በውኃ ውስጥ ያለ ድንጋይ መዋኘት እንደማይችለው›› ዓይነት ነው በማለት ባለሙያዎች አስተያየታቸውን ይሰነዝራሉ፡፡
በፕሪሚየር ሊጉ በተለያዩ ክለቦች እየተዘዋወሩ ከአሥር ዓመት በላይ እንዳሳለፉ የሚነገርላቸው አሠልጣኞቹ ‹‹ልምድ ያላቸው›› ብሎ ለመጥራት ያሳዩት ውጤት ወይም ለውጥ መገምገም አለብን በማለት አሠልጣኝና የብስራት ኤፍኤም የእግር ኳስ ተንታኝ ሚሊሻ ጉግስ አስተያየቱን ለሪፖርተር ሰጥቷል፡፡
እንደ ሚሊሻ አስተያየት ከሆነ አሠልጣኞች በሊጉ ላይ ከመቆየት ባሻገር የአንድ የክለብ የበላይነትን ለማስቆም ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ሲያደርጉ አይስተዋልም በማለት ይናገራል፡፡ የተጫዋቾች ዝውውር መጨመር አሠልጣኞቹን ከክለብ ወደ ክለብ እንዲዘዋወሩ ዕድል ይሰጣል ይላል፡፡
‹‹አሠልጣኞች ወደ አንድ ክለብ ሲዘዋወሩ ብዙ ተጫዋቾች ስላልፈረሙ ውጤት የሚያመጡ ስለሚመስላቸው አፈራርሰው መጠጋገን ይፈልጋሉ፤›› በማለት አስተያየቱን ያክላል፡፡
በተጨማሪም የክለብ አስተዳደሮች ውሳኔ ከውጭ አገሮች የሚዘዋወሩት ተጫዋቾች ከነባሮቹ ጋር ለመዋሃድ አዳጋች ስለሚሆን ክለቡን አደጋ ውስጥ እንደሚከት ይገልጻል፡፡
ተጨዋቾችን በተለይ በአንድ ክለብ ውስጥ ረዘም ባለ ጊዜ ውስጥ በማቆየትና ውህደቱን በመፍጠር ክለቡን ተፎካካሪ ከማድረግ ባሻገር ማፈራረስ ስለሚጎላ ክለቦች ተፎካካሪ ሆነው እንዳይቀጥሉ ያደርጋቸዋል ይላሉ ባለሙያዎቹ፡፡
ከጊዜ ወደ ጊዜ ከተለያዩ የአፍሪካ አገሮች የሚመጡት ተጫዋቾች የክለብ አስተዳዳሪዎችን እያማለሉ መምጣቱና በአሠልጣኞች ፍላጎትም ሆነ ከአሠልጣኞች ፍላጎት ውጪ በውጤቱ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ እየመጣ መሆኑ ይነገራል፡፡
የክለብ አስተዳደሮች ጣልቃ ገብነት ትክክለኛ መንገድ እየተከተሉ እንዳልሆነ ባለሙያዎች በተደጋጋሚ ሲናገሩ ይደመጣል፡፡
በተለያዩ ክለቦች ከተጫዋቾቻቸው ጋር ተማምነው ክለባቸውን የሚመሩ አሠልጣኞች ቢኖሩም በአስተዳደራዊ ውሳኔ ብቻ አሠልጣኞችን መቀያየር ባህል እየሆነ መምጣቱ ይነገራል፡፡ በስምንት ሳምንታት ውስጥ ከአሠልጣኝነታቸው የተነሱት አሠልጣኞቹ ደግሞ ወደ ሌላ ክለቦች አምርተው ተመሳሳይ ሁኔታ እንደሚከተሉና ‹‹የውኃ ቅዳ ውኃ መልስ›› ሒደትን መከተላቸው የማይቀር ነው የሚሉም አልታጡም፡፡ የክለብ አስተዳዳሪዎች በየዓመቱ የሚያወጡት በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ከግምት ውስጥ በመክተት ውጤት ለማምጣትና እግር ኳሱን ለማሳደግ ከወዲሁ የራሳቸውን ድርሻ መወጣት እንደሚገባቸው የብዙዎች እምነት ነው፡፡