በሰሜን ኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ልጃገረዶች/ሴቶች በተለይ ከነሐሴ አጋማሽ ጀምሮ በወገባቸው ላይ በመቀነቶቻቸው ሸብ አድርገው፣ አስረውና አሸርጠው የሚጫወቱበት ቅጠል አሸንዳ ይባላል፡፡ በ1962 ዓ.ም. የታተመው የአለቃ ደስታ ተክለወልድ ‹‹ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት›› አሸንዳን ሲፈታው፣ ‹‹ርጥብ ገሣ [ሣር] የትግራይ ልጃገረዶች በበዓል ቀን ያሸርጡታል›› በማለት ይገልጸዋል፡፡ አሸንዳ በዋግ ኽምራ (ሰቆጣ) በኽምጣኛ ቋንቋ ሻደይ ሲባል፣ ፍችውም ለምለም አረንጓዴ ሣር መሆኑ ይታወሳል፡፡ ዶ/ር ከበደ ታደሰ ባዘጋጁት ‹‹Wild Flowers of Ethiopia – የኢትዮጵያ ወፍ ዘራሽ አበቦች›› መጽሐፍም፣ አሸንዳ (Torch Lily) ረዥም መስመር ቅጠልና ከጫፉ ቢጫ/ቀይ/ብርቱካንማ አበቦች ያለው በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኝ ዓመታዊ ሐመልማል (An endemic herb) ይለዋል፡፡ [ሐመልማል ለምለም ቡቃያ፣ ሣር ቅጠል እንደማለት ነው] አሸንዳ ከ2100 እስከ 4000 ሜትር ከፍታ ላይ በተዳፋትና በመንገድ ዳር ዳር ያድጋል፣ ከሚያዝያ እስከ ጥር ድረስ ያብባል፡፡
- Advertisement -
- Advertisement -