የአገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ነሐሴ 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በነበረው አስቸኳይ ስብሰባ በአገሪቱ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ እንደተወያየ የገለጸው የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ)፣ ከስብሰባው በኋላ የተላለፈው ውሳኔ የጋራ ምክር ቤቱን አዋጅና ደንብ የጣሰ ነው በማለት ተቃወመ፡፡
‹‹የጋራ ምክር ቤቱ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት አስቸኳይ ስብሰባ ጠርቶ ነበር፡፡ በስብሰባው ላይ ‘ያልተፈቀዱ ሠልፎች’ የሚወገዙ ናቸው በማለት ምክር ቤቱ የያዘውን አቋም ኢዴፓ ተቃውሞ በዚያ መልኩ መታየት እንደሌለበትና የልዩነት አቋም አለን ብለን ረጅም ሰዓት የፈጀ ውይይት አድርገን ነበር፤›› በማለት የኢዴፓ የጥናትና ምርምር ኃላፊ አቶ ዋስይሁን ተስፋዬ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡
‹‹ረጅም ሰዓት የፈጀ ውይይት ብናደርግም ግን የጋራ ምክር ቤቱን ደንብ በመጣስ በስምምነት መወሰን የሚገባው ጉዳይ በአብላጫ ድምፅ ተወስኖ በመገናኛ ብዙኃን ተላልፏል፡፡ ነገር ግን የእኛ የልዩነት ሐሳብ በመገናኛ ብዙኃን አልተስተናገደም፡፡ ይህ ደግሞ እኛን አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚከት ነው፤›› ሲሉ አቶ ዋስይሁን አብራርተዋል፡፡
‹‹በመሆኑም የጋራ ምክር ቤቱ ሕግን የሚጥስ ተግባሩን በሦስት ወራት ውስጥ የማያስተካክል ከሆነ ኢዴፓ ከጋራ ምክር ቤት ሊለቅ እንደሚችል ከወዲሁ ያሳውቃል፤›› በማለት ፓርቲው ለሪፖርተር በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ኢዴፓ የአገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ ነሐሴ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. መግለጫ ማውጣቱን አስታውሶ፣ በመንግሥት ቁጥጥር የሚገኙ የመገናኛ ብዙኃን የመግለጫውን ይዘት አዛብተው አቅርበዋል በማለት ቅሬታውን አሰምቷል፡፡
‹‹በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የተከናወኑ ሠልፎችን አስመልክቶ በሰጠነው ጋዜጣዊ መግለጫ እንቅስቃሴዎቹ በማንም ይደረጉ በማንም የሠልፉን ዋነኛ ምክንያት ማወቅ ያስፈልጋል የሚል አቋም ይዘናል፤›› በማለት አቶ ዋስይሁን ገልጸዋል፡፡
እንቅስቃሴው መሪ የሌለውና ከመርህ ውጪ የተደረጉ ሠልፎች ናቸው ተብሎ በመንግሥት በኩል እንደተገለጸ የሚናገሩት አቶ ዋስይሁን፣ ‹‹ይህ ሊሆን የቻለበት ምክንያት ግን በሰላማዊ መንገድ ተመዝግበው የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ድምፃቸውን ሊያሰሙ የሚችሉበት ዕድል በማጣታቸው፣ ሕዝቡ የዴሞክራሲ ጥያቄዎቹን በራሱ መንገድ ገፍቶ በመውጣቱ ነው፤›› በማለት ኢዴፓ በመግለጫው ማስታወቁን አቶ ዋስይሁን አስረድተዋል፡፡
‹‹ከዚህ አንፃር ፓርቲዎች ተዳክመዋል ማለት ሕዝቡ የመብት ጥያቄውን አያቀርብም ማለት አይደለም በማለት ገልጸን የነበረ ቢሆንም፣ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር የሚገኙት የመገናኛ ብዙኃን ግን ዘገባውን ያቀረቡት በተዛባ መንገድ ‘ኢዴፓ የሕዝቡን እንቅስቃሴ አወገዘ’ በሚል ነው፤›› በማለት አቶ ዋስይሁን አስረድተዋል፡፡
በመሆኑም በመንግሥት ቁጥጥር ሥር የሚገኙ የመገናኛ ብዙኃን የኅብረተሰቡን መረጃ የማግኘት መብት እንዲያከብሩና አሠራራቸውንም ፈትሸው እንዲያስተካክሉ ኢዴፓ ይጠይቃል ሲሉ አክለዋል፡፡