የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት የክብር ዘበኛ ሻምበል አበበ ቢቂላ (በቀኝ) ከነ ግርማ ሞገሱ ከክፍሉ ባልደረቦች ጋር
***
አንቺ የሌለሽበት!
አግኝቶ ማጣቱ ÷ አጥቶም መደኽየቱ
ሲፈራረቅብሽ ÷ በየዘመናቱ፣
ሐዘን ያጠላበት ÷ የመረርሽበቱ
አይኾኑው ስሜቱ ÷ ሳለሽ ምልክቱ፤
አተኵረው ያዩሽ ÷ ዛሬስ በሥርዓቱ
ሀገሬ በከንቱ ÷ አልፎ ያ ጊዜያቱ።
የጥበባት ቋቱ ÷ የዕውቀት መዛግብቱ
ሳለሽ ከበፊቱ
የእምነት የሥርዓቱ ÷ የባህል ማዕከላቱ
ኾነሽም ባናቱ
አልይዝ ያለው ቤቱ ÷ ከሥር መሠረቱ
ምናልባት ሀገሬ ÷ የለሽ በሰዓቱ
ሲያነሱ ሲጥሉ ÷ የውሉን ጥናቱ።
አምላክ ሥራው ግሩም ÷ ፈቃዱም ዕፁብ
ያሰቡት ያለሙት ÷ ባይደርስም ከልብ።
ያሻውን ቢገብር ÷ ያሻውን ቢወስን
አቤት ያስብል እንጂ ÷ አይወጣለት እንከን።
ያሻውን ቢሾም ÷ ያሻውን ቢሽር
ፍርዱም አይታጠፍ ÷ በሰማይ በምድር።
ያሻውን ቢያጸድቅ ÷ ያሻውን ቢኰንን
ያሻውን ሊያኖርም ÷ ከሞት ቢሠውር፣
የሰው ልጅ አያምን ÷ ካላየ በቀር
ክፉ ደጉ ኹሉ ÷ ተርፎት ላ‘ዳም ዘር።
የድኩማን ምርኩዝ ÷ የዕውራን በትር
ለምንንገዳገድ ÷ ሁሌም በጭፍን፤
ሀገሬ ኢትዮጵያ! ባለሽ ቃል ኪዳን
ዓይነ ጥላችንን ÷ አንቺው ግፈፊልን።
ኃይለ ልዑል ካሣ
ታኅሣሥ 10/2010 ዓ.ም.
***
በገና ዋዜማ ከ40ሺዎች በላይ በኦንላይን የተመለከቱት የጌም ፈጣሪ
አንድ ሰው በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ብሎ ምንም እንቅስቃሴ ሳያደርግ ለደቂቃዎች ቢመለከቱት የሥርጭት ብልሽት ሊሆን ይችላል ብለው ሌላ ጣቢያ ፍለጋ ያማትሩ ይሆናል፡፡ የታዋቂው ‹‹ኦቨርዎች›› ቪዲዮ ጌም ዲዛይነር ጄፍ ካፕላን ድርጊት ግን ሰዎች ቲቪያቸውን እንዲዘጉ ሳይሆን ለዘጠኝ ሰዓት ያህል ዓይናቸውን ከኦንላይን ቲቪያቸው መስኮት እንዳይነቅሉ አድርጓል ሲል ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡ ዕለቱ የፈረንጆቹ ገና ዋዜማ ነበር፡፡ የጌሙ ዲዛይነር ካፕላንም ከሶፋው ላይ እግሩን አጣምሮ ተቀምጦ፣ ቀጥታ እየተመለከተና ከኋላም ከቼምኒ ውስጥ ማገዶው እየተንቦለቦለ የሚያሳየው ፊልሙ በኦንላየን ቪዲዮ ለአሥር ሰዓት ያህል ተለቋል፡፡
በእነዚህ ሰዓታት 40ሺሕ ተመልካቾች የካፕላንን እንቅስቃሴ አልባ መልክ የተመለከቱ ሲሆን፣ በገና ዕለት ቢያንስ ለሦስት ሰዓታት ያህል ፊልሙን የተመለከቱት ብዛት ከ250 ሺሕ በላይ ደርሷል፡፡ ለአሥር ሰዓት በነበረው ቆይታ አንዴ ስልክ ሲመልስ፣ አንዴ ደግሞ ቸኮሌት በልቷል፡፡ አንዴ ማይክራፎን ወድቆበታል፡፡ ከዚህ ውጪ ያለምንም እንቅስቃሴና ድምፅ ነበር ቁጭ ብሎ አሥር ሰዓታትን ያሳለፈው፡፡ አስተያየት ሰጪዎችም የካፕላንን ድርጊት እንደወደዱለት፣ ለዘጠኝ ሰዓት ያህል ቁጭ ብለው የተመለከቱም እንደነበሩ ዘገባው ያሳያል፡፡
***
ለሰርጓ ስትደንስ የሽንት ውኃ የፈሰሳት እርጉዝ ሙሽራ
የሠርግ ታዳሚዎች ከሚቋደሱት ምግብ መለስ ብለው በሙሽሮች የተጀመረውን ዳንስ ማየት መጀመራቸው ነው፡፡ ሆኖም በሙሽሮቹ የተጀመረ ዳንስ በሙሽሮቹ አላለቀም፡፡ ነፍሰጡር የነበረችው የ19 ዓመቷ ሙሽራ ዳኒ ማውንትፎርድ ከ18 ዓመቱ ባለቤቷ ካርል ጋር ዳንስ ገና ከመጀመሯ ሽንት ውኃዋ ያፈሳል፡፡ ወዲያውኑም ወደ ሆስፒታል ሩጫ ሆነ፡፡ የመጀመሪያ ሴት ልጃቸው ጃስሚንም ተወለደች፡፡ ሚረር እንዳሰፈረው፣ ሙሽሮች በሌሉበት ሠርጉ በዲጄ ጭፈራ ታጅቧል፡፡ ዳኒም ‹‹አንድ ሰከንድ ከባሌ ጋር ደንሼ በቀጣዩ ትንሿ ጃስሚንን ወለድኩ፡፡ የሠርጋችን ዕለት የበለጠ እንዳይረሳ የሚያደርግ አጋጣሚ ነበር፤›› ብላለች፡፡
***
በአዲሱ ዓመት የተወለዱት የአፍሪካ ሕፃናት
የጎርጎርዮስ ቀመርን በሚከተሉት አገሮች አዲሱን ዓመት 2018 ጃንዋሪ 1 (ታኅሣሥ 23 ቀን 2010 ዓ.ም.) ተቀብለዋል፡፡ የሕፃናት ጉዳይን የሚመለከተው የመንግሥታቱ ድርጅት ክንፍ ዩኒሴፍ በዋዜማው ይፋ እንዳደረገው፣ በዓመቱ መባቻ ምሥራቃዊና ደቡባዊ የአፍሪካ አገሮችን በልደት የተቀላቀሉት 48,000 ሕፃናት ናቸው፡፡ በእነዚህ የአፍሪካ ግዛቶች የተወለዱ ሕፃናት ቁጥር 9,023 በኢትዮጵያ፣ 5,995 በታንዛኒያ፣ 4,953 በዑጋንዳ፣ 4237 በኬንያና 3417 በአንጎላ ከፍተኛ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡