የአገሪቱን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ የሚቆጣጠረው የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን፣ ዘመናዊ የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃና የአቪዬሽን ሙዚየም ለመገንባት በዝግጅት ላይ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ባለሥልጣኑ ዕቅዱን ይፋ ያደረገው የድርጅቱን የ2008 ዓ.ም. ዕቅድ አፈጻጸም ከሠራተኞቹ ጋር በገመገመበትና ዓመታዊ የሠራተኞች በዓል ባከበረበት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ነው፡፡ በዕለቱ የ2008 ዓ.ም. ዕቅድ አፈጻጸምና የ2009 ዓ.ም. ዕቅድ ሪፖርት ያቀረቡት የአየር ትራንስፖርት ዳይሬክተር አቶ እንደሻው ይገዙ እንደተናገሩት፣ ድርጅቱ አዲሱን ባለስድስት ፎቅ ሕንፃ የሚነባው በመሥሪያ ቤቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ ነው፡፡ የሕንፃው ንድፍ መሠራቱን የገለጹት አቶ እንደሻው፣ ግንባታው በመጪው ዓመት እንደሚጀመርና በአምስት ዓመታት ውስጥ እንዲጠናቀቅ መታቀዱን ለሠራተኞች ተናግረዋል፡፡
አዲስ የሚገነባው የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ ቢሮዎች፣ የአቪዬሽን ሥልጠና ማዕከል፣ የአገሪቱን የአቪዬሽን ታሪክ የሚያሳይ የአቪዬሽን ሙዚየም፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎችና ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ የሚከራዩ ሕንፃዎች ግንባታን ያካተተ ነው፡፡ ለሕንፃው ዲዛይን ሥራ በወጣው ጨረታ ሦስት ኩባንያዎች ተወዳድረው ኬቱኤን የተሰኘው አገር በቀል አማካሪ ድርጅት አሸናፊ ሆኗል፡፡ አማካሪ ድርጅቱ የሠራው የአቪዬሽን ኢንዱስትሪውን የሥራ እንቅስቃሴ የሚያንፀባርቀው የሕንፃ ንድፍ በዕለቱ ለዕይታ ቀርቧል፡፡
የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኮሎኔል ወሰንየለህ ሁነኛው ስለፕሮጀክቱ በሰጡት ማብራሪያ፣ የባለሥልጣኑ ዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ የተገነባው ከ50 ዓመታት በፊት በመሆኑ ዛሬ ባለሥልጣኑ ለደረሰበት የዕድገት ደረጃ በቂ እንዳልሆነ ጠቁመዋል፡፡ አገሪቱ ከ70 ዓመት በላይ የዘለቀ ረዥም የአቪዬሽን ታሪክ ቢኖራትም፣ ይህንን ታሪክ የሚዘክር ሙዚየም እስካሁን አለመኖሩን የጠቀሱት ኮሎኔል ወሰንየለህ የአገሪቱ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ያለፈበትን የዕድገት ደረጃ የሚያሳይ የአቪዬሽን ሙዚየም እንደሚገነባ ተናግረዋል፡፡ ‹‹በሙዚየሙ ውስጥ ምን ምን ነገሮች ይቀመጡ የሚለውን ከአሁኑ ማሰብ ይኖርብናል፡፡ የድርጅቱ ባለሙያዎች ብቻ ሳይሆኑ በአገር ውስጥና በውጭ ያለ ማንኛውም የዘርፉ ባለሙያ አስተዋጽኦ ሊያደርግ ይችላል፤›› ብለዋል፡፡
የሕንፃው ግንባታ አጠቃላይ ወጪ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ሲሆን፣ በ2009 ዓ.ም. ሥራውን ለማስጀመር 50 ሚሊዮን ብር በጀት ጥያቄ ለገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር መቅረቡን የገለጹት ኮሎኔል ወሰንየለህ፣ ፕሮጀክቱ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ የሚጠይቅ በመሆኑ ግንባታውን በአምስት ዓመታት ለማጠናቀቅ መታቀዱን አስረድተዋል፡፡
በ1937 ዓ.ም. የተመሠረተው የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ለአየር መንገዶችና ተጓዳኝ ድርጅቶች ፈቃድ መስጠት፣ አየር መንገዶችንና አውሮፕላኖችን በመመርመር የብቃት ማረጋገጫ ሠርተፊኬት መስጠት፣ ለአብራሪዎች፣ ለቴክኒሺያኖችና ለሌሎች የአቪዬሽን ባለሙያዎች የሙያ ፈቃድ መስጠት፣ የአውሮፕላን ጥገና ማዕከላትን መፈተሽ፣ የበረራ ፈቃድና የኤር ናቪጌሽን አገልግሎት የሚሰጥ መንግሥታዊ ድርጅት ነው፡፡ እ.ኤ.አ. በ2025 ከአደጋ ሥጋት የፀዳ የአየር ክልል የማስተዳደር ራዕይ ሰንቆ የሚንቀሳቀሰው ባለሥልጣኑ ደኅንነቱ የተጠበቀ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ኅብረተሰቡ እንዲያገኝ አሠራሩን በማዘመን፣ ዘመናዊ የበረራ መቆጣጠሪያ መሣሪያዎችን ገዝቶ በመግጠምና የአቪዬሽን ባለሙያዎችን በስፋት በማሠልጠን ላይ መሆኑን ከኃላፊዎቹ ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡