በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች በተለያዩ አካባቢዎች በተከሰቱት ግጭቶች የሰው ሕይወት ማለፉንና የንብረት ውድመት መድረሱን አስመልክቶ፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች በሙሉ ጸሎተ ምህላ እንዲይዙና የሰላም ትምህርት ተጠናክሮ እንዲካሄድ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማክሰኞ ነሐሴ 3 ቀን 2008 ዓ.ም. ጥሪዋን አቀረበች፡፡
ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ በክልሎቹ ተከስቶ ያለውን ግጭት፣ ውዝግብና ሁከት ቆም ብሎ ማስተዋል እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል፡፡ የተፈጠሩ ችግሮች ሁሉ በሕጋዊ መንገድ፣ በወንድማማችነት መንፈስና በውይይት እንዲፈቱም አሳስበዋል፡፡
በዋናነት የተፈጠሩ ችግሮች ይፈቱ ዘንድ በመላው ዓለም ያሉ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች በሙሉ፣ አሁን ተይዞ ባለው የፆም ሱባኤ (የፍልሰታ ፆም) በሁሉም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎትና ምህላ፣ እንዲሁም የሰላም ትምህርት ተጠናክሮ እንዲደረግና እንዲካሄድ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ አዛውንት፣ ምሁራን፣ አባወራዎችና እማወራዎች፣ ወጣቶችን በመምከርና በማስተማር ከሕይወት መጥፋትና ከሀብት ውድመት እንዲታደጉ ጠይቀዋል፡፡
ፓትርያርኩ ሁሉም ወገኖች አሉን የሚሏቸውን ጥያቄዎች በሰላማዊ መንገድ ለሚመለከተው አካል በማቅረብ፣ በውይይትና በምክክር በሰላማዊ መንገድ መፍታት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ ሰሞኑን በተፈጠሩ ግጭቶች ሕይወታቸውን ላጡና ንብረታቸው ለወደመባቸው ዜጐች ቤተ ክርስቲያን ጥልቅ ሐዘን እንደገባት አክለዋል፡፡