አገር አቀፍ የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ሐምሌ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. የተበሰረ ሲሆን፣ ምዝገባውም ሐምሌ 30 ቀን በይፋ ተጀምሯል፡፡
በአዲስ አበባ ሒልተን በተከናወነው ሥነ ሥርዓት ላይ ተገኝተው ምዝገባውን ያበሰሩት ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ እንደተናገሩት፣ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ አሠራር መርህን የተከተለ ዘመናዊ የወሳኝ ኩነት የአመዘጋገብ ሥርዓት ለማከናወን የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍም ሆነ የአሠራር ሥርዓት እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ አልነበረም፡፡ አገሪቷም የገባቻቸውን ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ከሟሟላትና ምዝገባው የሚሰጠውን ጠቀሜታ ከማረጋገጥ አንፃር ከፍተኛ ክፍተት ነበረበት፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ በመንግሥታዊ አስተዳደር ተቋማት፣ በተለይም በከተማ አስተዳደሮች ወጥነት በሌለው መመሪያ ላይ በመመሥረት የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ደረጃውን ባልጠበቀና በተበታተነ ሁኔታ ምዝገባው ሲከናወን የቆየ ሲሆን፣ ይህም በየጊዜው ሊዘጋጁ የሚገባቸው የሕዝብ ብዛትና ምጣኔ እንዲሁም ወሳኝ የማኅበራዊና የልማት መለኪያዎች አግባባዊውን አሠራር ተከትለው እንዳይከናወኑ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡
ሐምሌ 30 ቀን የተጀመረው የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ግን፣ የነበሩትን ችግሮች የሚቀርፉ ይሆናል፡፡
በሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት አቶ ጌታቸው አምባዬ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ፣ በኢትዮጵያ የወሳኝ ኩነቶች አሠራርን ለማቋቋም ጥረት የተደረገው ከአፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ጊዜ ጀምሮ መሆኑን፣ ለመጀመሪያ ጊዜ የአገሪቱ የሕግ አካል ሆኖ የተደነገገው ደግሞ በ1952 ዓ.ም. በወጣው የፍትሐ ብሔር ሕግ እንደሆነ፣ ይሁንና ላለፈው ግማሽ ምዕት ዓመት ከልማዳዊ አሠራር የተላቀቀና አስፈላጊውን ደረጃ ያሟላ የዜጎች የምዝገባ ሥርዓት በአገሪቱ ተግባራዊ እንዳልተደረገ ተናግረዋል፡፡
መንግሥት የዜጎች መረጃ ምዝገባ ሥርዓትን ዕውን ለማድረግ ይቻል ዘንድ፣ የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ብሔራዊ መታወቂያ አዋጅ 760/2004 እና የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 278/2005 በማውጣት የፌዴራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደር ወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ኤጀንሲዎችን በማቋቋም ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን አቶ ጌታቸው ገልጸዋል፡፡
ለአገሪቱ ወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ሥርዓት ግንባታ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሕፃናት ልማት ፈንድ (ዩኒሴፍ) ኢትዮጵያ የፋይናንስና የቴክኒክ ድጋፍ በማድረግ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው ትብብር ማድረጉን አቶ ጌታቸው አስታውቀዋል፡፡
ወ/ሮ ኤልሳ ተስፋዬ የፌዴራል የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ዋና ዳይሬክተር፣ የፌዴራል መንግሥት በመላ አገሪቱ የምዝገባውን ሥራ ለማስጀመር የሚያስችል ሁለንተናዊ ድጋፍ ማድረጉን፣ ከዚህም ሌላ የምስክር ወረቀት፣ የክብር መዝገብና መመርያ ለማከናወን ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ መመደቡን ተናግረዋል፡፡
ሚስ ጁሊያን ሜልሶፕ የዩኒሴፍ ኢትዮጵያ ተወካይ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በ2003 ዓ.ም. ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች ከሆኑት ሕፃናት መካከል ሰባት ከመቶው ብቻ የልደት ምዝገባ ማካሄዳቸውን፣ ይኽም ከአሥር ሕፃናት መካከል ዘጠኝ ያህሉ ሳይመዘገቡ መቅረታቸውን፣ ቅንጅት የጎደለውና ምቹ ያልሆነ የልደት፣ የሞትና የጋብቻ ሠርቲፍኬቶች ከሆስፒታሎች፣ ከአብያተክርስቲያናትና ከማዘጋጃ ቤቶች ይሰጡ እንደነበር አስረድተዋል፡፡