ግብፅ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ለሚገኘው የልብ ሕሙማን ማዕከል 600,000 ዶላር የሚያወጣ ሲመንስ ካቲተር የተባለ መሣሪያ በዕርዳታ ሰጠች፡፡ ለቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅም የሕክምና ቁሳቁስ ተለግሷል፡፡
መሣሪያውን እሑድ ኅዳር 24 ቀን 2008 ዓ.ም. የማዕከሉ ዳይሬክተር ዶ/ር በላይ አበጋዝ በይፋ በተቀበሉበት ወቅት እንደተናገሩት፣ መሣሪያው በ48 ሰዓታት ውስጥ 20 ልጆች ደረታቸው ሳይከፈት የልብ ቀዶ ሕክምና ተሰጥቷቸው ከሆስፒታሉ እንዲወጡ ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር በላይ እንደተናገሩት፣ መሣሪያው የሰዎችን ሕይወት ለማዳን የሚደረገውን ሩጫ ያፋጥናል፡፡ ‹‹መሣሪያው ሆስፒታሉ የሚሰጠውን አገልግሎት የተሻለ ያደርጋል፡፡ ደረታቸው ሳይከፈት ሕክምና የተሰጣቸው ልጆች፣ ከሆስፒታሉ በአፋጣኝ ሲወጡ ከማየት በላይ ምን መልካም ነገር አለ፤›› ብለዋል፡፡
ለዓመታት ከዶ/ር በላይ ጋር የሠሩትና መሣሪያውን በዕርዳታ ለማስመጣት ከፍተኛ ሚና የተጫወቱት ፕሮፌሰር መግደይ ያኰብ፣ ‹‹መሣሪያው እንደ ኤክስሬይ ማሽን ነው፡፡ የሰው ደረት ሳይከፈት ቀዶ ሕክምና መስጠት ያስችላል፡፡ በአገሪቱ ብቸኛ በሆነው የልብ ሕክምና ማዕከሉ አገልግሎት ለማግኘት የሚፈልጉ ብዙዎች ከመሆናቸው አንጻር በጣም አስፈላጊ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ዶ/ር በላይ ከዶ/ር መግደይ ጋር ተመሳሳይ ሐሳብ እንዳላቸው ገልጸው፣ ‹‹በመሣሪያው ተጠቃሚ በሚሆኑ የኢትዮጵያ ሕፃናት ስም፣ ምሥጋናዬን አቀርባለሁ›› ብለዋል፡፡
ከ39 ዓመታት በፊት ማዕከሉን የመመሥረት ሐሳብ ሲጠነሰስ፣ ለሆስፒታሉ መሣሪያና የሰው ኃይል ማሟላት እንዲሁም ቀጣይነቱን ማረጋገጥ ቅድሚያ የሰጧቸው እንደነበሩ ተናግረዋል፡፡ አሁን በሆስፒታሉ ሙያዊ አገልግሎት ከሚሰጡ የሌሎች አገሮች ባለሙያዎች በተጨማሪ፣ መሣሪያዎችም ከውጪ በዕርዳታ እየተገኙ ነው፡፡ አገሪቱ በራሷ አቅም የጤና ዘርፍ ችግሮችን መፍታት እስከምትችልም ተመሳሳይ ዕርዳታዎች ያላቸውን ጠቀሜታም አስረድተዋል፡፡
የኢጅፕሺያን ኤጀንሲ ኦፍ ፓርትነርሺፕ ፎር ጄቨሎፕመንት ሴክረተሪ ጄኔራል አምባሳደር ሐዘም ፋህሚ በበኩላቸው፣ ለዘመናት የዘለቀው የኢትዮጵያና የግብፅ ወዳጅነት በሕክምናው ዘርፍም መቀጠሉን ተናግረዋል፡፡ ‹‹ዕውቀትና ቴክኖሎጂን በመጋራት የሰዎችን ሕይወት ከማትረፍ በላይ ትልቅ ነገር የለም፡፡ በግብፅና በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የአፍሪካ አገሮች መካከልም ተመሳሳይ ትስስር መኖር አለበት፤›› ብለዋል፡፡
ግብፅ ከዚህ ቀደምም የሕክምና መሣሪያዎችን ለኢትዮጵያ በዕርዳታ መስጠቷ ይታወሳል፡፡ በአንድ ወቅት ለጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሕክምና ቁሳቁሶችን ያበረከተች ሲሆን፣ በሌላ ጊዜ ደግሞ ለቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የኩላሊት ሕክምና የሚያገለግሉ መሣሪያዎች ተለግሰዋል፡፡ በሁለቱ አገሮች መካከል ያለውን ትስስር የገለጹት በኢትዮጵያ የግብፅ አምባሳደር አቡበከር ሀፍኒ መሐመድ፣ ለጤናው ዘርፍ የሚደረገው ዕርዳታ ከምንም በላይ ቦታ የሚሰጠው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ለልብ ሕሙማን ማዕከል የተለገሰው ማሽን ከተጎበኘ በኋላ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የሚገኘውን የግብፅ ኢንዶስኮፒ ማዕከል ጎብኝተዋል፡፡ ለሆስፒታሉ ኢአርሲፒ ማሽን የተለገሰ ሲሆን፣ በሆስፒታሉ ግብፃውያን የጤና ባለሙያዎች የሚሠሩበት የኩላሊት እጥበት ማዕከልም ተዘዋውረው ጎብኝተዋል፡፡
ከግብፅ ኤምባሲ ባገኘነው መረጃ መሠረት፣ ግብፅ ለ400 ኢትዮጵያውያን የትምህርት ዕድል የሰጠች ሲሆን፣ ከእነዚህ 14 በጤናው ዘርፍ ናቸው፡፡