መዛግብቱ እንደሚያስረዱት ዝግባ ብዙ ቅጠልና ዐፅቅ ያለው ዛፍ ነው፡፡ በግእዝ አርዝ፣ በዕብራይስጥ (እስራኤል) ኤሬዝ፣ በሱርስጥ (ሶርያ) አርዛ ይባላል፤ ታላቅ ዛፍ ወፍራም ደንዳና ረዥም ገናና እንደ ጥድና ዝግባ ያለ ነው፡፡ በጥንት ጊዜ በመካከለኛው ምሥራቅ የዝግባ እንጨት ንግድ ትልቅ ቦታ ይሰጠው ነበር። በግብፅና በሜሶጶጣሚያ የነበሩ ሰዎች ቤተ መቅደሶችንና ቤተ መንግሥቶችን ሲሠሩ የዝግባን እንጨት ወራጅ አድርገው ይጠቀሙበት የነበረ ሲሆን ሕንጻዎችን ለማስጌጥም ይገለገሉበት ነበር። የነገሥታት መዛግብት፣ የሥነ ጽሑፍ ሥራዎችና የተቀረጹ ጽሑፎች እንደሚያሳዩት የዝግባ እንጨት ወደተለያዩ የደቡብ ሜሶጶጣሚያ ከተሞች ይላክ እንዲሁም አንዳንድ ጊዜ በምርኮ ይወሰድ ብሎም በግብር መልክ ይሰጥ ነበር። በግብፅ ደግሞ ነገሥታት የሚጠቀሙባቸውን ታንኳዎች አልፎ ተርፎም የሬሳ ሣጥንና ሌሎች ለቀብር ሥነ ሥርዓት የሚሆኑ ቁሳቁሶችን ለመሥራት ያገለግል ነበር። በንቁ መጽሔት እንደተመለከተው፣ የሊባኖስ ዝግባ በጥንካሬው፣ በውበቱና በጥሩ መዓዛው የታወቀ ነበር፤ በምስጥ በቀላሉ የማይበላ መሆኑም ሳይጠቀስ አይታለፍም።