የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት በ70 ሚሊዮን ዩሮ ለሚገነባው ዘመናዊ ቄራ፣ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ቀርሳ ኮንቱማ አካባቢ 20 ሔክታር መሬት ተሰጠው፡፡ በዚህ ቦታ ሕገወጥ የተባሉ ግለሰቦች የሠፈሩበት እንደነበር ይታወሳል፡፡ የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ሕገወጥ የተባሉ አካላት እንደተነሱ የተሰጠውን ቦታ የማጠርና ስለሚሠራው ዘመናዊ ቄራ የሚገልጽ ፖስተር መለጠፍ መጀመሩ ታውቋል፡፡ የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ከመሀል አዲስ አበባ ወጥቶ ወደ ከተማው ዳርቻ እንዲሄድ ከተወሰነ አምስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በዚህ ውሳኔ መሠረት የአዲስ አበባ ከተማ መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ለዘመናዊ ቄራ ግንባታ የሚሆን ቦታ በቦሌ ኤርፖርት ክልል ውስጥ ቦታ ሰጥቶ ነበር፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን፣ ቄራዎች በባህርያቸው የተለያዩ አካላትን ትኩረት የሚስብ በመሆናቸው ፕሮጀክቱን ተቃውሟል፡፡ ይህ ውጥን ለዓመታት ሲንከባለል ቆይቶ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ውስጥ ቀርሳ ኮንቱማ በተባለው አካባቢ ይህ ቦታ እንዲሰጥ ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ይህ ቦታም ቢሆን በሰዎች የተያዘ በመሆኑ ቄራዎች ድርጅት ወደ ግንባታ መሸጋገር ሳይችል ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ በቅርቡ ለምክር ቤት እንዳስረዱት ይህ ቦታ ለአጣዳፊ ፕሮጀክቶች የሚፈለግ ነው፡፡ በሕገወጥ የተያዙ ቦታዎች በአስቸኳይ እንዲለቁ ይደረጋል ብለው ነበር፡፡ በዚህ መሠረት ክፍለ ከተማው ሕገወጥ ከተባሉ ነዋሪዎች ጋር ምክክር ቢያደርግም፣ ሰኔ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. በአስተዳደሩ ውሳኔ የተበሳጩ የአካባቢው ነዋሪዎች ለውይይት ከመጡ የመንግሥት አካላት ጋር በመጋጨት የሦስት ሰዎች ሕይወት ሊያልፍ ችሏል፡፡ በዚህ ግጭት የወረዳ አንድ ሥራ አስፈጻሚና ሁለት የፖሊስ ባልደረቦች ሕይወት ሲያልፍ መንግሥት በወሰደው ዕርምጃ በርካታ ሰዎች መጎዳታቸው ይታወሳል፡፡ የተወሰደው ዕርምጃ ቤቶች ማፍረስንም ያጠቃለለ በመሆኑ፣ በዚህ ዘመቻ የተገኘው ቦታ ውስጥ በመጀመርያው ረድፍ ለአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ተሰጥቷል፡፡ የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዘውድነህ አብዲ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ቄራዎች ድርጅት የተረከበውን ቦታ አጥር በማጠር ደኅንነቱን ለማረጋገጥ እየሠራ ነው፡፡ አቶ ዘውድነህ ጨምረው እንደገለጹት የአዲስ አበባ ቄራዎች በመሀል አዲስ አበባ የሚገኙ በመሆናቸውና ከተማውን ለማሳደግ የተያዘውን ዕቅድ፣ እንዲሁም ድርጅቱ ከአፍሪካ ኅብረት ጎን የሚገኝ በመሆኑ ከከተማ መውጣት ይኖርበታል፡፡ ለዘመናዊ ቄራ ግንባታ የሚሆነውን 70 ሚሊዮን ዩሮ ከፈረንሣይ ልማት ድርጅት በብድር የተገኘ ሲሆን፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ሚኒስትር ብድሩን በቅርቡ ያፀድቀዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ይህንን ግንባታ ለማካሄድ የሚያስችል ጨረታ የወጣ ሲሆን፣ የኮንትራክተር መረጣ እየተካሄደ መሆኑን አቶ ዘውድነህ አረጋግጠዋል፡፡