ለክቡር ሌተና ኰሎኔል ፍሰሐ ደስታ በደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ላይ ያቀረቡት ሐተታ የተዛባ ነው በሞገስ ሀብተ ማርያም (አምባሳደር) ‹‹አብዮቱና ትዝታዬ›› በሚል ርዕስ ያሳተሙትን መጽሐፍ ደጋግሜ አነበብኩት መጽሐፉን ሳነብ በሦስት ክፍሎች መድቤ አየሁት፡፡ በአብዮቱ ዘመን የተከናወኑትን ጉዳዮች በቅደም ተከተል ጥርት ባለ መንገድ አቅርበዋል፡፡ አንዳንድ ጉዳዮችን እንኳንስ ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ በፓርቲና በመንግሥታዊ ከፍተኛ አመራር ቦታ ላይ ከነበራችሁት ሹማምንት ሥር በሥራ ምደባችን ስናገለግል ለቆየው እንኳ አዲስ መረጃ ሆኖ በበኩሌ የተከታተልኩት ከአድናቆት ጋር ነው፡፡ ከደርግ ምሥረታ ጀምሮ አሥራ ሰባት ዓመት ሙሉ በተለያዩ እርከኖች እያለፉ በመጨረሻም ሁለተኛውን የአመራር ምድብ ለመጨበጥ የቻሉ መኰንን ዛሬ ነገሮች ሁሉ ተለዋውጠው ሁሉም ቤቱ ይቻለው በሚባልበት ሰዓት ወደ ኋላ ተመልሰው ራስዎን ለመከላከል በርከት ባሉ የመጽሐፉ ገጾች ተጠቅመዋል፡፡ ራስዎንና የትግራይ ተወላጆች የሆኑትን የእርስዎም የእኛም ጓደኞችን በሚያስነብቡት ጽሑፍ ወደ ኋላ ተመልሰው ከተጠረጠሩበት ወንጀል ሊያድኗቸው ወይም በጊዜው በተፈጸመው ሁኔታ ሊታዘንላቸው ይገባል የሚሉ ይመስላል፡፡ በእርግጥ ድርጊቶች እርስዎ እንዳስቀመጡት የተፈጸሙ ከሆነ ሁላችንም የሐዘንዎ ተካፋይ ለመሆን ዝግጁ ነን፡፡ ይሁን እንጂ ለተሰነዘሩት አስተያየቶች፣ ወቀሳዎችና ትችቶች ማስተባበያ ወይም ማረሚያ ለማቅረብ የሚችል ሰው በሌለበት ሰዓት ይኼን ሁሉ ማተት የእኔን ብቻ አድምጡ የሚሉ አስመስሎብዎታል፡፡ ስማቸውን ካነሷቸው ሰዎች መካከል አብዛኛዎቹ በሕይወት አይገኙም፡፡ ሌላው የደኅንነት መሥሪያ ቤቱን የሚመለከት ነው፡፡ በተለይም ሚኒስትሩ ኰሎኔል ተስፋዬ ወልደ ሥላሴ ለዚህ ከፍተኛ ኃላፊነት እንዴት እንተደመረጠ ጀምረው በሁለታችሁ መካከል የነበረውን ‹‹ጨዋታ›› አትተዋል፡፡ በዚህ ጊዜ የደኅንነቱን የሥራ ተሳትፎ የሚያውቁትን ያህል ለማስረዳት ሞክረዋል፡፡ ኰሎኔል ተስፋዬ ዛሬ በሕይወት ባለመኖሩ እርሱንም ሆነ መሥሪያ ቤታችንን በሚመለከት ላቀረቡት ትችት መልስ ለመስጠት አልታደለም፡፡ ስለዚህ በግል እርሱን በሚመለት ካንዳንድ ነጥቦች በስተቀር ወክዬ መልስ ለመስጠት ባለመቻሌ እያዘንኩ፣ በመሥሪያ ቤቱ ላይ ለተቃጣው ዘለፋና ያልተቆጠበ አስተያየት የበኩሌን ትንሽ ለማለት እገደዳለሁ፡፡ ለ17 ዓመታት የደኅንነቱን መሥሪያ ቤት የመራው ኰሎኔል ተስፋዬ እንዴት ለዚህ የኃላፊነት ቦታ እንደተመረጠ በገጽ 419 ላይ ስላሰፈሩት ጽሑፉ ትንሽ አስተያየት መስጠት ይኖርብኛል፡፡ ተወዳዳሪ ሆነው የቀረቡት ኰሎኔል ተካ ቱሉ እና ኰሎኔል ካሳሁን ታፈሰ ነበሩ፡፡ ሁለቱንም የደርጉ የደኅንነት ኃላፊዎች በነበሩ ጊዜ አውቃቸዋለሁ፡፡ ኰሎኔል ተካ ገና ምክትል የመቶ አለቃ ሳለ ፀጥታ መሥሪያ ቤት ተመድቦ ከገባ በኋላ ሥራውን አልወደውም ብሎ ወደ ፖሊስ ሠራዊት የተመለሰ ነበር፡፡ ከእርሱ ጋር ፀጥታ መሥሪያ ቤት ተመድበው ለበርካታ ዓመታት ካገለገሉ በኋላ እስከ ኰሎኔልነት ማዕረግ ደርሰው በመምርያ ኃላፊነትና በተለያየ የሥራ ምደባ አገልግለው ዛሬ በጡረታ ላይ የሚገኙ አሉ፡፡ እርሱ ግን በፖሊስ ሠራዊት ውስጥ አስከ ሻለቃ ማዕረግ ሐረርጌ ቆይቶ በ1966 ዓ.ም. ደርግ ሲቋቋም ነው አዲስ አበባ የገባው፡፡ እጅግ አስተዋይ፣ ትዕግሥተኛና ለግራ ቀኙ ምክር አካፋይ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ ኰሎኔል ካሳሁን ታፈሰ ደግሞ በጦር ሠራዊት ውስጥ በመረጃ ሥራ እንኳ ተመድቦ የሠራ አይመስለኝም፡፡ እርግጥ ገራገርና ለሰው ቅን የሚያስብ መሆኑን በአንድ አጋጣሚ ልረዳ ችያለሁ፡፡ እንግዲህ እነዚህን ሁለት ሰዎች ነበር በኢንቴለጀንስ ሙያ ሠልጥኖ በተለያየ ቦታ ሲያገለግል ቆይቶ በደርግ ጥሪ የመረጃ ቤቶችን ሥራ እንዲያስተባብር ከተመረጠ መኰንን ጋር ለማወዳዳር የሞከራችሁት፡፡ ይኼ ፈጽሞ ሊሆን የማይገባው ጉዳይ ነበር፡፡ እርግጥ በጊዜው ደርግ ጽሕፈት ቤት እነርሱ የበላይ ሆነው ለደኅንነት አመራር ሲሰጡ ኰሎኔል ተስፋዬ በተለመደ የቻይነት ባህሪው እየተሽቆጠቆ ሲታዘዛቸው ከተመለከቱት ሰዎች አንዱ እኔ ነበርኩ፡፡ ከዚህ ሌላ በ1966 ዓ.ም. ሥልጣን የጨበጠው ወታደራዊ ደርግ እንደመሆኑ ከጦሩ የኢንተለጀንስ ክፍሎች ከእርሱ ጋር ለመወዳደር የሚችሉ መኰንኖች አይኖሩም ማለት አይቻልም፡፡ ይሁን እንጂ እነርሱም ቢሆኑ በጊዜው የነበረውን ወከባና የደርግ አባላትን ቁጣ ተቋቁመው የሚዘልቁ መሆናቸውን እጠራጠራለሁ፡፡ በዚህ ጉዳይ ብዙ ማለት ቢቻልም ይኼንን ከባድ ኃላፊነት ተረክቦ በሥራው ሒደት ከዕድገት ወደ ዕድገት እየተሸጋገረ ለ17 ዓመታት የዘለቀው ኰሎኔል ተስፋዬ ትችት ሊቀርብበት የሚገባ እንዳልሆነ በአጽንኦት ልገልጽ እወዳለሁ፡፡ ኰሎኔል ተስፋዬን እርስዎ እንዳሉት መምረጥዎና ማስመርጥዎ ምንም ጥፋት እንደሌለበት ላረጋግጥልዎ እወዳለሁ፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ወደ ሌሎች ጉዳዮች እንግባ፡፡ ከመጋቢት 30 ቀን 1970 ዓ.ም. ጀምሮ ቀይ ሽብርም ሆነ ነፃ ዕርምጃ መቆሙን ገጽ 247 ላይ አስነብበውን ይኼንንም ለመወሰን የሚችል ከእርሳቸው (ፕሬዚዳንት መንግሥቱ) በስተቀር ሌላ ሰው እንዳልነበረ ገልጸዋል፡፡ እዚህ ላይ ከመነሻው ግልጽ ላደርግ የምፈልገው ጉዳይ፣ የደኅንነቱ መሥሪያ ቤት በክትትል የሚደርስባቸውን መረጃዎችና ጥናታዊ ዝግጅቶች ፖሊሲ ለሚነድፉ የበላይ አካላት እያቀረበ ማስወሰንና በተከታይም በመመርያና በትዕዛዝ መልክ ወደታች የሚንቆረቆሩለትን መፈረምና ማስፈጸም መሆኑን ነው፡፡ በቀይ ሽብር ነፃ ዕርምጃ ላይ ትንሽ ለመናገር፣ በጊዜው በየመንገዱ በተቃዋሚዎች ላይ እየተተኮሰ ሬሳቸው ከቆሻሻ ማጠራቀሚያ ገንዳ አጠገብ ወድቆ የተመለከቱ አንድ ከክፍለ አገር የመጡ አዛውንት መንግሥት ባለው ሥልጣን ማቆያ ቤት አስገብቶ መመርመርና የሚገባቸውን ፍርድ መስጠት ሲችል ለምን በየመንደሩ ይገደላሉ? ለመሆኑ በሚያስተዳድረው አገር ላይ የሸፈተው መንግሥት ነው ወይስ ሌላ? ብለው የሰጡት አስተያየት አንድ መነሻ ሆኖን ነበር፡፡ በሌላ ጊዜ ደግሞ ከጀርመን ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ አዲስ አበባ የተመደበው የደኅንነት ተጠሪ ከአገሩ የመጡ እንግዶችን ይዞ ኰሎኔል ተስፋዬን ለማነጋገር በጊዜው አገር አስተዳደር ወደ ነበረው ቢሮው ሲጓዝ ቴሌ መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት ሲደርሱ፣ የጥቁር አንበሳን ሆስፒታል ግንብ አስደግፈው በወጣቶች ላይ ጥይት ሲያርከፈክፉባቸው ተመልክተው ድርጊቱን ዘግናኛና አስደንጋጭ ስለሆነባቸው ወደ እርሱ ቢሮ መሄዳቸውን ትተው መኪናቸውን አዙረው ኦርቢስ አጠገብ ወደሚገኘው ወደ እኔ ቢሮ መጥተው ያዩትን ሁሉ ገልጸውልኛል፡፡ ለኰሎኔል ተስፋዬ ንገርልን አሉኝ፡፡ ታዲያ የእነርሱም አስተያየት የተረጋጋና በእግሩ የቆመ መንግሥት አይደለም እየመራችሁ ያላችሁት? ለምን ሁሉንም በሕግ አትፈጽሙም? የተመለከትነው ነገር ሁለት የሽፍታ ቡድኖች ጎራ ለይተው እንደሚታኮሱ እንጂ መንግሥት ጥፋተኞች ናቸው በሚላቸው ላይ የወሰደው ዕርምጃ መስሎ አልታየንም፡፡ የተረጋጋ መንግሥት መሆናቸውን ለወዳጅም ለጠላትም አሳዩ እንጂ ብለውን ሄዱ፡፡ እንግዲህ እነዚህን ሁሉና ሌሎችንም ነጥቦች አጠነቃቅረን ለበላይ አካል ማስተላለፋችን ትዝ ይለኛል፡፡ ቀጥሎ ከገጽ 247 ጀምሮ ሶማሊያን በሚመለከት ወዳነሱት ጉዳይ እገባለሁ፡፡ በሲያድ ባሬ እጀምራለሁ፡፡ ጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረች ጊዜ የእነሱ የፖሊስ የበታች ሹም ነበር፡፡ ሃምሳ አለቃ ሲያድ ባሬ ጌቶቹን ተከትሎ መጥቶ ሞጆ ላይ የፖሊስ ጣቢያ አዛዥ ሆኖ አገልግሏል፡፡ ከሶማሊያ ነፃነት በኋላ በጦሩ ውስጥ በተለያዩ ደረጃዎች አልፎ የጄኔራልነት ማዕረግ ካገኘ በኋላ ነበር የጠቅላይ ሚኒስትር ሸርማርኬን መንግሥት ገልብጦ ሥልጣን የያዘው፡፡ አፈወይኒ በሚል የቅጽል ስም መጠራት የጀረመው ገና ሥልጣን ሳይጨብጥ በፊት ጀምሮ ነው፡፡ ትርጉሙም አፈ ሰፊ ማለት ነው፡፡ ልብ ብለው ተመልክተውት እንደሆነ የጆሮ አምላክ ገድቦት ነው እንጂ አፉን ሲከፍት በጣም አስፈሪ ነበር፡፡ እርግጥ ሥልጣን ከጨበጠ በኋላ ብዙ የፖለቲካ ንግግር ስለሚያደርግ አዋቂ ወይም ጥበበኛ ለመምሰል ሲሞክር ታይቷል፡፡ ደቡብ የመን ኤደን ላይ በኩባው መሪ ፊደል ካስትሮና በደቡብ የመን መሪ ሩቢያ ዓሊ ጣምራ ሊቀመንበርንት በሊቀመንበር መንግሥቱና በሲያድ ባሬ መካከል ውይይት በተደረገ ዕለት አዋቂ ለመምሰል በአንድ የንግግር ሥልት ላይ ሲያጠነጥን ተደምጧል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ አብዮተኞች ከኃይለ ሥላሴ ያልተሻለ አስተሳሰብ ይዛችሁ ነው የቀረባችሁት፤›› በማለት የድፍረት ንግግር ሲያሰማ ስብሰባው አዳራሽ ውስጥ ስለነበርኩ ላዳምጠው ችያለሁ፡፡ በዚህ ጊዜ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ያሰሙት አፀፋ መልስ የኢትዮጵያን ኩሩ ሕዝብ ወኔ የተላበሰና ውይይቱንም ይመሩ የነበሩትን ሊቀመናብርት ያስደነቀ ስለነበር ለታሪክ ሲታወስ የሚኖር ጉዳይ ነው፡፡ በዕለቱ ሊቀመንበራችን አንበሳ ሆነው ነበር የዋሉት፡፡ አስተርጓሚያቸው የነበረው ብርሃኑ ዲንቃም (በኋላ ነው አምባሳደር የሆነው) እጅግ የሚያኮራን ሆኖ ነበር የተገኘው፡፡ እርሳቸውም በመጽሐፋቸው ላይ እንደገለጹት አስተናጋጆች ያዘጋጁትን ምግብ እንኳ ሳንቀምስ ነበር ወደ አውሮፕላን ሜዳ ሄደን ጉዞ ወደ ኢትዮጵያ የተጀመረው፡፡ ከዚያ በኋላ በጦር ሜዳ የተከናወነውን ሁሉ በሚገባ ስላስቀመጡት እዚህ ላይ እንደገና ማንሳት አስፈላጊ አይሆንም፡፡ ሆኖም ልዩ ካቢኔ (ወይም የደኅንነቱ የውጭ መረጃ ዋና መምርያ) ስላደረገው አስተዋፅኦ ትንሽ እንኳ ስላልተናገሩልን ከድፍረት ባይቆጥሩብኝ ታዝቤዎታለሁ፡፡ ዝነኛው አየር ኃይላችን የሚናገረው ስለማይጠፋ ወደፊት በሚወጣው ገድል ላይ ይገለጻል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ እንግዲህ ሲያድ ባሬ በትምክህተኝነት በቆሰቆሰው ጦርነት በአብዮቱ ዕርምጃ ላይ መሰናክል መፍጠሩ ባይቀርም፣ የታላቋ ሶሚሊያ ሕልም ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማክተሙን የሚያሳይ ክስተት ሊፈጠር ቻለ፡፡ መሪያቸው በእርግጠኝንነት አሸንፋለሁ ብሎ በለኮሰው እሳት በአገሪቷ ላይ ያደረሰውን ጉዳት የተመለከቱ ባለሥልጣኖቹ ሁሉ እርሱን ከሥልጣን የሚያስወግዱበት መንገድ መፈለግ ጀመሩ፡፡ አንዳንዶቹን እርሱ ቀደም ብሎ ወደ ወህኒ ቤት ቢወረውራቸውም ሚኒስትሮቹና ከፍተኛ የጦር መኰንኖች አፈ ወይኒ ኢትዮጵያ የሰው በላ አገር ነች እያለ ሲያስተምራቸው የነበረውን መነባንብ ተራምደው በጠፍ ጨረቃ ወደ ኢትዮጵያ መግባት ጀመሩ፡፡ በመጀመርያ ወደዚህ የመጡት ሁለት ሚኒስትሮች ሲሆኑ፣ በማከታተል ብዙ በጦር ሜዳ የዋሉ መኰንኖችም በኦጋዴን በኩል መጥተዋል፡፡ በደቡብ በባሌ ግንባር የሶማሊያ ጦር አዝማች ሆኖ ተሠልፎ የነበረው ኰሎኔል አብዱላሂ ዩሱፍ የመጣውና የገባው በኬንያ በኩል ነበር፡፡ እዚህ ላይ ስንደርስ እርስዎ በመጽሐፍዎ ላይ ያስቀመጡትን አገላለጽ እንዳለ ሙጥቀሱ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት በ1973 ዓ.ም. 06 በሚል ስም ፕሮጀክት አቋቁሞ ኤስኤንኤም እና ኤስኤስዲኤፍ የተባሉ ሁለት ድርጅቶችን ማደራጀትና ማስታጠቅ ጀመረ፡፡ ለዚህ ፕሮጀክትም አንድ ኢትዮጵያዊ ከፍተኛ መኰንንና ፊታውራሪ ደምሴንና ባላምባራስ ፈቃደን በአማካሪት መደበ፡፡ …የደርግ ልዩ ካቢኔ እንቅስቃሴውን በበላይነት እንዲከታተል ተደረገ፤›› የሚል ሐተታ አንብቤያለሁ፡፡ ገና በማለዳ የዚህ ዓይነት አደረጃጀት የተሞከረ ቢሆንም ብዙ እንዳልተገፋበት አስታውሳለሁ፡፡ ለመሆኑ ከፍተኛ መኰንን ያሉት ማን ነበር? እነ ፊታውራሪ ደምሴስ ያን ጊዜ ከየት መጥተው ነበር አማካሪ የተባሉት? ልዩ ካቢኔውስ እነዚህ ሁሉ ከተደለደሉለት በኋላ ነበር የሥራው ተካፋይ የሆነው? የሶማሊያን ኮብላዮች እየተቀበለ የማደራጀት ኃላፊነት ከጠዋቱ የተሰጠው ለደኅንነቱ ነበር፡፡ ልዩ ካቢኔው ለዚህ ፕሮጀክት ኃላፊ እንዲሆን ተመድቦ ከመጀመርያው ጀምሮ እስከ ሲያድ ባሬ ውድቀት ድረስ የሶማሊያን ተቃዊሚ ኃይሎች ጉዳይ የተከታተለው መሥሪያ ቤታችን ነበር፡፡ በጊዜው የልዩ ካቢኔ ዋና ሹም የበረው ዘመነ ካሰኝ (በኋላ አምባሳደር) ለፕሮጀክቱ ራሱን የቻለ መምርያ እንዲቋቋም አድርጎ ከሶማሊያ የሚጎርፉትን ብቻ ሳይሆን፣ በዓለም ላይ የተበታተኑትን ሶማሊያዎች ሁሉ በማሰባሰብ ለዚህ ከፍተኛ ዓለማ እንዲሠለፉና በትግሉም እንዲሳተፉ ተደርጓል፡፡ እርግጥ በዚህ ሒደት የሶማሊያዎችን ባሕልና ቋንቋ የሚያውቁ አማካሪዎች መፈለግ እንዳለብን ከጠዋቱ ነበር የተገነዘብነው፡፡ ስለዚህም በአገር አስተዳደር ሚኒስቴር ቋሚ ተጠሪ የነበሩትና የአብዮቱን ዓላማ ሊያራምዱ አይችሉም በሚል በጡረታ የተገለሉትን ፊታውራሪ መሐረነ ምንዳን አስፈልገን አግኝተን እንዲተባበሩን የልዩ ካቢኔ ዋና ሹም በጠየቃቸው ጊዜ፣ ሳልሠራ እንዳልሞት ለምመኘው ሥራ ስለሆነ የጋበዛችሁኝ በማለት ሙሉ ፈቃደኝነታቸውን አሳይተውን ተቀላቀሉ፡፡ በዚህ ጊዜ የአገር አስተዳዳር ሚኒስትሩ፣ ‹‹እኔ በጡረታ ያገለልኳቸውን ደኅንነቱ መልሶ እየቀጠረ ነው›› በሚል ክስ ሲያቀርብ፣ ተው ሥራቸውን አታደናቅፍ መባሉ ትዝ ይለኛል፡፡ ‹‹ከሞኝ ደጃፍ የሞፈር እንጨት ይቆረጣል›› እንደሚባለው መሆኑ ነው፡፡ የሶማሊያ ተቃዋሚ ኃይሎችን ካሰባሰብን በኋላ የዓላማ መተሳሰር ተፈጥሮ ወደፊት ለመግፋት እንዲቻል የመጀመርያው ኮንግረስ የተካሄደው ራስ ካሳ ግቢ ነበር፡፡ ፊታውራሪ መሐረነ ለተወሰነ ጊዜ ካገለገሉ በኋላ ባደረባቸው ሕመም በሞት ተለዩን፡፡ በዚህ ጊዜ እርሳቸውን የሚተካ ሰው ማፈላለጉ አስፈላጊ ሆነና ሥራ ላይ ቆይተው ወደ ጡረታ የተገለሉትን ፊታውራሪ ደምሴን አስገባን፡፡ ኰሎኔል ኃይለ ሚካኤል ዘለለው ደግሞ የሶማሌ ቋንቋ አጥርተው ስለሚያውቁ ባስተርጓሚነት ተመደቡ፡፡ የማደራጀት ሥራችን እየሰፋ ሲሄድ ነው ባላምባራስ ፈቃደን ድሬዳዋ ላይ ለታጋዮቹ ባቋቋምነው ካምፕ ውስጥ በአስተዳዳሪነት እንዲሠሩ የተደረገው፡፡ ሁሉም አዛውንቶች በተሃድሶ ስሜት ያበረከቱትን አስተዋፅኦ ሳስታውስ እጀግ ያኮራኛል፡፡ ከዚህም ሌላ የኤስኤስዲኤፍ ተዋጊ ኃይል ከተደራጀ በኋላ በውጊያው መስመር ወታደራዊ ምክር ለማካፈል እንዲችሉ በልዩ ካቢኔ ውስጥ ኰሎኔል ክንፈ ገብርኤል ድንቁን (በኋላ ሜጀር ጄኔራል) አስመድበን ነበር፡፡ ጡረታ ላይ የነበሩት ብርጋዴር ጄኔራል ምሕረተአብ ተድላ ደግሞ ድሬዳዋ ላይ በተከፈተው ካምፕ ተመድበው የተቻላቸውን የምክር አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ይኼ ፕሮጀክት በቀላሉ የተያዘ አልነበረም የተለያዩ አዋቂዎችንም አሰባስበናል፡፡ አቶ ጌታቸው ክብረት (ሚኒስትርና አምባሳደር የነበሩ) የሕግና የፖለቲካ አማካሪ ነበሩ፡፡ አቶ ሙሉጌታ ሉሌ ከማስታወቂያ ሚኒስቴር የፕሮፓጋንዳው ዘርፍ አስተባባሪና መሪ ሆነው ሠርተዋል፡፡ ታዲያ የዚህ ከፍተኛ ኮሚቴ አባላት አዲስ አበባ ላይ ብቻ ቁጭ ብለን ሳይሆን በነጄኔራል ደምሴ ቡልቶ አማካይነት ጠረፍ ድረስ እየተመላለስን ትግሉን አስተባብረናል፡፡ ወደ አደረጃጀቱ ጉዳይ ዘልቀን ስንገባ ደግሞ ኤስኤንኤም እና ኤስኤስዲኤፍ የተቋቋሙት ጎን ለጎን አልነበረም፡፡ በመጀመርያ አንድ ድርጅት ብቻ ተቋቁሞ ሁሉም የተካተቱት በእርሱ ሥር ነበር፡፡ በኋላ ግን የሰሜን ሶማሊያ ተወላጆች በደቡብ አመራር ሥር ሆነው መታገል እጅግ ጎታች ሆነብን ብለው ስላመለከቱ የበላይ ውሳኔን ስንጠበቅ ለብቻቸው እንዲደራጁ ተወስኖ አስደናቂ ዕርምጃ ሊታይ ችሏል፡፡ በተለይ ከኤስኤንኤም ታጋዮች ጋር በነበረን ግንኙነት በጊዜው በሚያገኙት ድል ዙሪያ ብቻ ሳይሆን የምንወያየው፣ ከዚያም ባለፈ ከሐረርና ጂጂጋ በሐርጌሳ በኩል አልፎ እስከ በርበራ ይዘልቅ የነበረውን የጥንት የንግድ መስመር ለመክፈትና ከኢትዮጵያ ጋር እጅግ የጠበቀ ግንኙነት ይኖረናል ብለው በሚመኙት ሐሳብ ዙሪያም ሐሳብ እንለዋወጥ ነበር፡፡ ይኼ አመለካከት ዛሬ ፍሬ አፍርቶ ኢትዮጵያ ሐርጌሳ ላይ ቆንስላ አቋቁማ፣ ባንክ ቤት ከፍታ፣ የአየር መጓጓዣ ተዘርግቶ ማየት እጀግ አስደሳች ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ለብዙ ዓመታት ትግሉን በማስተባበር ተግባር የቆየሁ ቢሆንም፣ የመጨረሸውን የድል ጉዞ አቅጣጫ ለማስጨበጥና ለበላዮች ለማቅረብ አልታደልኩም ነበር፡፡ ይሁንና ቀድሞ የነበሩት የሥራው የቅርብ ተከታታዮችና እኔን የተኩ ኃላፊዎች ተግባራቸውንና ኃላፊነታቸውን በሚገባ ስለተወጡ በበኩሌ ላመሰግናቸው እወዳለሁ፡፡ የዚህን ታላቅ ሥራ ሒደት በዝርዝር እንደሚያቀርቡትም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ መቼም በሥራ ምክንያት በአካባቢው ባልገኝም በሳዑዲ ዓረቢያ በአምባሰደርነት ተሰይሜ በምሠራበት አንድ ዕለት የማላውቃቸው ሰዎች ሰብሰብ ብለው ወደ ኤምባሲያችን በመምጣት አምባሳደሩ ዘንድ መቅረብ እንፈልጋለን ይላሉ፡፡ ምንድናቸው ስል ሶማሌዎች መሆናቸው ይነገረኛል፡፡ በዚህ ጊዜ እንዲገቡ አድርጌ ቁጭ ካሉ በኋላ ከመካከላቸው አንዱ ብድግ ብሎ፣ ‹‹ሶማሊያን ነፃ ለማውጣት በኤስኤንኤም አመራር ሥር ሆነን ከታገልነው መካከል በሥራ ሳቢያ ሪያድ ወስጥ የምንገኘውን ጓደኞቼን ወክዬ በእርስዎ ፊት ንግግር ለማድረግ በመቻሌ ደስተኛ ነኝ፡፡ የትግል መሪያችንን የአህመድ ሞሐመድን (በሁኑ ጊዜ የሶማሌላንድ ፕሬዚዳንት እርሳቸው ናቸው) ሰላምታ አቀርብለዎታለሁ፡፡ ኤስኤንኤም በድል አድራጊነት ሐርጌሳ ገብቶ የመልሶ ማቋቋም ተግባሩን ቀጥሏል፡፡ እርስዎና የሥራ ጓደኞችዎ ለትግል ግንባራችን ያደረጋችሁት አስተዋፅኦ ለሁልጊዜም ሲታወስ ይኖራል፤›› ብሎ ንግግሩን ጨረሰ፡፡ እኔም ከአብዮታዊ መሪያችንና ከበላይ አመራር ሰጪዎች በተሰጠን ኃላፊነት ሶማሊያን ከአስከፊው የሲያድ ባሬ አስተዳደር ለማላቀቅ ያደረግነው ጥረት ለሶማሊያ ሕዝብ ያስገኘው ውጤት አስደሳች ነው በማለት ተናግሬ ሻይ ቡና ተገባብዘን ሸኘኋቸው፡፡ ይኼንኑ በሪፖርት ሳልገልጸው የቀረሁ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም የደኅንነቱ ትሁት አስተዋፅኦ እንዲሁ ተልኮስኩሶ እንዲቀር ስላልፈለኩ ነው፡፡ በተለይም ታጋዮቹ እኔ ካለሁት ቦታ ድረስ ተወካዮቻቸውን ልከው ያቀረቡልኝ ምሥጋና ላበረከትኩት አስተዋፅኦ ክቡር ምስክር ሆኖ ስላገኙሁት ሁሉጊዜም ሳስታውሰው የምኖር ስሜት ፈጥሮብኛል፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ከላይ ከተገለጸው ከሶማሊያዎች ትግል ጋር ተመሳሳይ ከሆነውና ደኅንነቱ ጎን ለጎን ሲያስተናብር ወደቆየው ወደ ደቡብ ሱዳን ታጋዮች ጉዳይ እንገባለን፡፡ በጃንሆይ ዘመነ መንግሥት የአንያንየ ታጋዮችን እነ መቶ አለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ (በኋላ ሻለቃ) ከሚያሠለጥኑበት ጊዜ ጀምሮ የፀጥታው መሥሪያ ቤት በማደራጀቱ ሥራ ተከፋይ ነበር፡፡ ይሁንና ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ጆሴፍ ላጉን ከኒሜሪ ጋር ካስታረቁና ከፍተኛ ዝና ካገኙበት በኋላ ደቡቦቹን የማደራጅቱ ተግባር ተቋርጦ ነበር፡፡ እንግዲህ ጄኔራል ጆሴፍ ላጉ የምክትል ፕሬዚዳንትነቱን ሥፍራ ጨብጦ ጦሩም ከተዋሀደ በኋላ የሰሜኑ መሪዎች በብልጠት ደቡቡን ከሥራቸው አድርገው ለመደቆስ ተዘጋጁ፡፡ የሸሪአ ሕግም አውጥተው ማስተዳደር ጀመሩ፡፡ በሱዳን የዑማ ፓርቲ መሪ የነበረው ሳዲቅ አልማህዲ ቀደም ብሎ ‹‹መላው የደቡብ ግዛት የእስልምና ሃይማኖት እንዲቀበል ማድረግ አለብን›› ብሎ መጽሐፍ የጻፈውን ተግባራዊ ለማድረግ ሙከራ መታየት ጀመረ፡፡ በዚህ ጊዜ ከመነሻው የእርቁ ጉዞ ያልጣማቸው አንዳንድ ደቡብ ሱዳናውያን ሹልክ እየሉ ወደ ጋምቤላ በመግባት ለመልሶ መደራጀት ራሳቸውን እያዘጋጁ ሀብታም በሆነው በጋምቤላ አውራጃ ውስጥ ተሰባስበው ነበር፡፡ የዚህ ስብሰብ መሪ ነኝ ብሎ ተከታዮቹን እያሳመነ የቆየው ጎርደን የተባለ ሰው ነበር፡፡ ከጓድ ፍሰሐና ከመሩት ቡድን ጋር በመጀመርያ የተገኘው ይኼው ሰው ነበር፡፡ ከአብዮቱ ፍንዳታ በኋላ በጋምቤላም ሆነ በሌሎቹ ክፍላተ አገሮች ደኅንነቱ ገና በጥንካሬ ስላልተቋቋመ የእነህን ሰዎች መምጣት ተከታትሎ የሚገልጽ የደኅንነት ኃይል ባካባቢው እንዳልነበረ የተገለጸው እውነት ነው፡፡ እንግዲህ እነ ጎርደን ጋምቤላ ውስጥ እንዳሉ ነው ደቡብ ሱዳን ቦር ከተባለ ቦታ ላይ የነበረ ጦር አመፅ ያስነሳው፡፡ ዓላማውም የደቡብ ሱዳንን ዜጎች መብት ለማስጠበቅ የተነሳ መሆኑን በማወጅ ተንቀሳቀሰ፡፡ የአመፁ መሪ ዶ/ር ኰሎኔል ጆን ጋራንግ ነበር፡፡ ጋራንግ በመጀመርያ በአንያንያ የትግል አመራር ሥር በታጋይነት ከቆየ በኋላ ዕርቅ እንደወረደ በሱዳን ጦር ውስጥ እስከ ሻምበልነት ማዕረግ ካገለገለ በኋላ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ አሜሪካ ተልኮ በእርሻ ኢኮኖሚ የፒኤችዲ የትምህርት መረጃ የጨበጠ ነበር፡፡ ከአሜሪካ ሲመለስ በሱዳን ጦር ውስጥ የልማት ምክትል ኃላፊ ሆኖ ይሠራ ነበር፡፡ ባልሳሳት የቦር አመፅ ከከሸፈ በኋላ ሻለቃ ካርቢኖ ከጋራንግ በፊት ወደ ጋምቤላ የመጣ ይመስለኛል፡፡ ለማናቸውም ጓድ ፍሰሐ ቀጥሎ ያገኙት ጆን ጋራንግን ነበር፡፡ ከእርሳቸው ተከታይ ቡድን ውስጥ እኔም ነበርኩበት፡፡ በዚህ ጊዜ ጋራንግ የመጣበትን ዓላማ በዝርዝር ከተረዱ በኋላ ወደ እኔ ዞር ብለው ‹‹ሞገስ እንግዲህ እወቅበት›› እንዳሉኝ ትዝ ይለኛል፡፡ ተዘንግቷቸው ይሁን ወይም የደኅንነቱን ተካፋይነት ላለመግለጽ እንደሆነ አይታወቅም በመጽሐፋቸው ላይ ይኼንን አልጠቆሙትም፡፡ ለማናቸውም ጋራንግ ከጋምቤላ ተንደርድሮ ወደ ኢትዮጵያ ከፍተኛ አመራሮች ዘንድ አልደረሰም፡፡ ጋምቤላ ሳለ ቀዳሚ ዝግጅቱን አድርጎ ወደ አዲስ አበባ ለመምጣት ሲያስብ የሚያሳውቀን ባልደረባ ተደርጎለት ጥቂት ጊዜ ከቆየ በኋላ ወደዚህ መጣ፡፡ በዚህ ጊዜ ደኅንነቱ ልዩ ቦታ አዘጋጅቶ ጠበቀው፡፡ ከእርሱ ጋር የዲንካ ተወላጅ የሆነ ሸማግሌና የዱር አራዊት ጥበቃ የሥራ ክፍል አባል የሆነ ኰሎኔል እንደነበሩ አስታውሳለሁ፡፡ እንግዲህ በዚህ ማረፊያ ቤት አንድ ወር ያህል የትግል ዓላማውን ንድፍ ሲያዘጋጅ ከቆየ በኋላ ነበር ወደ ጓድ ፕሬዚዳንት ያቀረብነው፡፡ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ከጠዋቱ ነበር በጋራንግ አስተዋይነትና ብልህነት የተማረኩት፡፡ ስለዚህም ብዙ ጊዜ የሱዳን ተቃዋሚዎችን የማደራጀት ጉዳይ ችላ እየተባለ የቆየው አሁን ይሁንታ አግኝቶ ኃላፊነቱ ለእኛ እንደተሰጠ አስታውሳለሁ፡፡ እርግጥ ለሶማሊያ ታጋዮች ወታደራዊ ጠበብቶት እንደተመደቡላቸው ሁሉ፣ ፕሬዚዳንቱ ጄኔራል መስፍንን ለኤስፒኤልኤም በወታደራዊ ጉዳዮች ምክር እንዲያካፍልና አሠልጣኞች እየመደበ እንዲያስተምር ማድረጋቸው ትክክል ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ወደ ጋምቤላ ብዙ ጊዜ አብረን ተመላልሰናል፡፡ ለማናቸውም ከጄኔራል መስፍን ጋር መሥራት በመግባባትና በመተባበር እንደነበር ሳልናገር ማለፍ የለብኝም፡፡ በተለያየ ጊዜ ፕሬዚዳንቱ ጆን ጋራንግን ጥሩልኝ እያሉ ወይም እርሱ ላነጋግራቸው እፈልጋለሁ ሲል ሁለታችን ይዘነው እየቀረብን እነርሱ ሲወያዩ፣ አንዳንድ መመለስ ያለብንን ጥያቄዎች እየመለስን መመርያም ሲሰጥ እየተቀበልን ተካፋይ መሆናችን አሁንም ትዝ ይለኛል፡፡ ጋራንግ በአፍሪካና በአውሮፓ አገሮች እየተዘዋወረ የትግል ዓላማውን ሲያስረዳ ፕሮግራም አዘጋጀቶና ባልደረባ መድቦ ያንቀሳቀሰው ደኅንነቱ ነበር፡፡ አንባቢ ልብ ሊል የሚገባው በሶማሊያም ሆነ በደቡብ ሱዳን የትግል እንቅስቃሴ ሥር የተደራጁት ኃይሎች ትግል ሲጀምሩ በያዙት ስያሜ ላይ የተደረገውን ጥንቃቄ ነው፡፡ በሶማሊያ በኩል ኤስኤስዲኤፍ ወይም ኤስኤንኤም አንዳቸውም ሪጅናቸውን የሚጠቁም ስያሜ አልያዙም፡፡ በዚህም በኩል ሱዳን ፒፕልስ ዴሞክራቲክ ፍሮንት በተለይ ለደቡብ ሱዳን ብቻ የተደራጀ ኃይል እንደሆነ የሚያመለከት ነገር የለውም ነበር፡፡ በዚህ አኳኋን ኤስፒኤልኤ የደቡብ ሱዳንን ክልል እያለፈ የሰሜኑ ክፍል በሆኑት ደቡብ ካርዶፋንና ብሉ ናይል ፕሮቪንስ ድረስ እየገባ እንዲያውም አንዳንዴ ለካርቱም መቶ ኪሎ ሜትር እስኪቀረው እየዘለቀ ከባደ ኦፕሬሽን እያካሄደ፣ የሱዳንን ጦር ባርበደበደው ጊዜ የሱዳኑ መሪ ጄኔራል ኒሜሪ አንድ አዋጅ አወጡ፡፡ ይኼውም የደቡቦችን የፖለቲካ ተካፋይነት ጉልህ ቦታ ለመስጠት ነው በሚል አስተሳሰብ ዶ/ር ጆን ጋራንግን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አድርጌ ሾሜያቸዋለሁ የሚል ነበር፡፡ ታዲያ በቀልድ መልክ ጋራንግን እንግዲህ ሹመት ተሰጥቶሃል ከዚህ ወዲያ ምን ልታደርግ አስበሃል? ስንለው ‹‹ኔሚሪ ሞኝ ነው፣ እኔ ይኼን ሁሉ ኃይል አሠልፌ የምዋጋው የግል ሥልጣኔን ለማደላደል መስሎት ወንበሬን ለቅቄልሃለሁ አለማለቱም ገርሞኛል፤›› እያለኝ መነጋገራችንና መሳቃችን ትዝ ይለኛል፡፡ የኒሜሪን መንግሥት ለማንገዳገድ አስተዋጽኦ ካደረገት አንዱና ዋናው የኤስፒኤል ትግል መሆኑ አይካድም፡፡ ታዲያ ኒሜሪ ለጉብኝት ወደ ውጭ አገር ሄደው ሳለ በጄኔራል ሰዋር አልደሃብ የተመራ ወታደራዊ አመፅ ተቀስቅሶ እ.ኤ.አ. በ1985 እርሳቸው እንደወጡ ቀሩ፡፡ ግን የንቅናቄው መሪ ጄኔራል ሰዋር አልደሃብ አዲስ ሕገ መንግሥት እንዲቀረፅና የቀድሞ የፖለቲካ ፓርቲዎች ዝግጅት እያደረጉ እንዲቆዩ አድርገው እ.ኤ.እ. በ1986 ከአንድ ዓመት በኋላ በሳዲቅ አልማህዲ የሚመራው ዑማ ፓርቲ አብላጭውን ወንበር አግኝቶ መንግሥት አቋቋመ፡፡ እንግዲህ ሱዳን እንደገና ወደ መድበለ ፓርቲ አስተዳዳር ተመለሰች ማለት ነው፡፡ በፓርላማው መክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ ለመገኘት ከኢትዮጵያ የተላከውን ቡድን የመራሁት እኔው ራሴ ነበርኩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሳዲቅ አልማህዲንና የሁሉንም ፓርቲዎች መሪዎች ተዘዋውረን ካነጋገርን በኋላ ዝርዝር ሪፖርት ሊኢሠፓ የውጭ ጉዳይ መምርያና ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስለቀረበ ሳይመለከቱት የቀሩ አይመስለኝም፡፡ በተለይም ለብዙ ዓመታት በኅቡዕ ይንቀሳቅ የነበረው የሱዳን ኮሙዩኒስት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ ኢብራሂም ኑጉድ በይፋ ብቅ ብሎ የምክር ቤት ወንበር ይዞ ስለነበር ከሱዳን መንግሥት ጋር ስለሚኖረን ግንኙነት ጠቃሚ ምክሮችን አካፍሎንም ስለነበር የእርሱንም ሐሳብ በሪፖርታችን ውስጥ አካትተነው ነበር፡፡ በመጽሐፍዎ ገጽ 298 ላይ ኰሎኔል መንግሥቱ አንደኛው ጎማ ተንፍሷል፣ ሁለተኛው (የሱዳን ማለታቸው ነው) በቅርቡ ይተነፍሳል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ያሉት በመጀመርያ ከሥልጣኑ የተፈናቀለው ኑሜሪ ስለነበር በእርሱ ጊዜ የተናገሩት ይመስለኛል፡፡ እንግዲህ የደቡብ ሱዳኖችን ትግል በዚህ አኳኋ እያስተባበርን ሳለ እኔ በሥራ ምድብ ወደ ውጭ ስለተላክሁ መጨረሻውን ለማየት አልበቃሁም፡፡ ሆኖም ከሱዳን ባለሥልጣናት ጋር ለስብሰባ በተገናኘን ቁጥር ተጨባጭ መረጃ እያቀረብን የሚፈጸሙብንን በደል ስናስረዳ እውነተኛውን ነገር እየካዱ ሲያላግጡብን የቆዩትን ያህል፣ በአጸፋ ምት ልናንበረክካቸው በመቻላችን ከተደሰቱት ሰዎች አንዱ እኔ ነበርኩ፡፡ ከዚህ በኋላ በመጽሐፍዎ ላይ ካነበብኳቸው ውስጥ አንዳንዶቹን ጉዳዮች እያሰባሰብኩ ወይም በተናጠል የማውቀውን ለመናገርና ግንዛቤ ለማስጨበጥ እሞክራለሁ፡፡ ገጽ 297 ላይ ስለኮሎኔል አብዱላሂ ዩሱፍ የገለጹትን እንዲሁ ላልፈው አልፈለኩም፡፡ ኮሎኔል አብዱላሂ ወደ እስር ቤት የተላከው በአንዲት የአፍ ወለምታ ነው፡፡ አሻጥር የተባለችውም እርሷ ናት፡፡ ከዚህ ሌላ በትግሉ ውስጥ ተቃዋሚዎቹን አስገድሏል ለሚባለው አፍ ሞልቶ መመስከር የሚቻል አይመስለኝም፡፡ ትግሉ ውስጥ የነበሩት አብዱራህማን አይዲድና መሐመድ ዲከር የተባሉት ሞስኮና ፕራግ ሄደው በአይዲዮሎጂው ተጠምቀው የተመለሱት ከኮሎኔል አብዱላሂ ጋር መግባባት ቢያጡም፣ እስከ ሞት የሚያደርስ ዕርምጃ ይወሰድባቸዋል ለማለት አስቸጋሪ ነው፡፡ ለትግሉ ድጋፍ እንሰጣለን በማለት ሊቢያውያን በአካባቢው ያንዣብቡ እንደነበር መዘንጋት የለበትም፡፡ ሌላም ግምት ማቅረብ ይቻላል፡፡ ብቻ ሁሉም ነገር ተድበስብሶ በመቅረቱ ያሳዝናል፡፡ የኮሎኔል አብዱላሂ የአፍ ወለምታ ከኦፕሬሽን ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የተሰማውን ቅሬታ ለመግለጽ አንድ ቃል በመናገሩ ሪፖርት ተደርጎበት ወደ ወታደራዊ ፖሊስ ተልኮ ታሰረ፡፡ ሰውየው አገሩ ሳለ በሲያድ ባሬ ታስሯል፡፡ እኛ ዘንድ መጥቶ ብዙ ከለፋ በኋላ ለሌላ እስር ሲዳረግ ዕድለ ቢስ መሆኑን ተመልክቼ ለዚያች ስህተቱ ምሕረት ተደርጎለት እንዲፈታ ብዙ ወትውቼ አይቻልም ተብሎ መቆየቱን አስታውሳለሁ፡፡ ሆኖም ባለቤቱና አራት ልጆቹ መጉላላት ስለማይገባቸው በስደት ወደ ሌላ አገር እንዲሄዱ አድርገናል፡፡ ለማናቸውም በአብዱላሂ መታሰር ምክንያት ትግሉ ባለመቋረጡ ግንባሩ ምን ዓይነት ጠንካራ መሠረት ላይ እንደቆመ ማረጋገጫ ተገኝቷል፡፡ በመጽሐፍዎ በተከታዩ ገጽ ላይ የሞቃዲሾ መንግሥት እየተጠናከረ ሲመጣ ያልተከለለው የድንበር ጉዳይ፣ እንዲሁም የሶማሊያ ፍላጎት እንደገና ማገርሸቱ አይቀርም ያሉት ትክክለኛ ግምት ነው፡፡ በ13/10/2001 ዓ.ም. አዲስ ነገር በተባለች ጋዜጣ ላይ የዋሽንግተን ፖስት ዘጋቢ ‹‹በሞቃዲሾ ያልተሞከረው ስትራቴጂ›› በሚል ርዕስ ያወጣው ጽሑፍ ተጨባጩን የሶማሊያ ችግር ያልዳሰሰና አርኪ ሆኖ ስላላገኘሁት፣ በዚሁ አዲስ ነገር በተባለ ጋዜጣ ላይ በ23/01/2002 ዓ.ም. ‹‹ሌላው የሶማሊያ መንገድ›› በሚል ርዕስ አንድ ጽሑፍ በስሜ አቅርቤ ነበር፡፡ እዚያ ላይ ሶማሊያ በጊዜው ያለችበትን ሁኔታ አትቼ ወደፊት ምን ሊከተል እንደሚችል በትንሹ ዕውቀቴ አንድ ዘገባ አቅርቤ ነበር፡፡ እርስዎ የወረወሩትን አስተያየት የሚደግፍና የሚያጠናክር ስለሆነ እንዲያነቡት እልክልዎታለሁ፡፡ ከዚህ በኋላ አሰባስቤ የምመለከታቸው ሦስት ጉዳዮች አሉ፡፡ የመጀመርያው በገጽ 318 ላይ ትሪፖሊ ኮሎኔል ጋዳፊ ዘንድ ቀርባችሁ በምትነጋገሩበት ጊዜ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሬገንን ለማስገደል አምስት የሠለጠኑ ሊቢያውያንን ያዘጋጁ መሆኑን ነገሩን፡፡ በዚህ ጊዜ የአሜሪካ የስለላ ድርጅት የመረጃ ምንጭ ከመካከላችን እንደነበረ አልጠረጠሩም ብለዋል፡፡ ይኼ እጅግ ከባድ ውንጀላ ነው፡፡ ኮሎኔል ጋዳፊ ስለዚሁ ዝግጅታቸው ቀደም ብለው አዲስ አበባ ሄደው ሳለ ለኮሎኔል መንግሥቱ የነገሯቸው ከሆነ፣ ወሬውን ለማስተላለፍ እሳቸውም በጥርጣሬ ቀለበት ውስጥ ሊገቡ ነው ወይ? ጽሑፍ ለማሳመር ከሆነ አብዮታዊ መሪያችንንም እጠረጥራለሁ ሊሉ ይችሉ ነበር፡፡ ውስብስብ የመረጃ የሥራ ሒደቶችንና የኢንተለጀንስን ኤቢሲ የሚያውቁ ከፍተኛ የደርግ ባለሥልጣን ጉዳዩን በጥልቀት መመልከትና መመርመር ይችላሉ ብዬ ስለምገምት፣ በኢንተለጀንስ ሪፖርት አቀራረብ ምንጩ A – 1 ተብሎ ይታይልኛል ብለው ያቀረቡት ጽሑፍ ምንም ማስረጃ ከኋላው ስላላስደገፈ ከሚቀጥለው ዕትምም ላይ ቢሰርዙት ይሻላል ብዬ እመክርዎታለሁ፡፡ ኮሎኔል ተስፋዬ ስለኢንተለጀንስ ጠልቆ የሚያውቅ ሰው ነበር፡፡ ሲአይኤ በኢትዮጵያ ውስጥ ያካሂድ የነበራቸውን ሚስጥራዊ ኦፕሬሽኖች እጅግ በረቀቀ ጥበብ እያጋለጠ መሬት ላይ ያነጠፈ ከፍተኛ የመረጃ መኮንን የአገሩንና የወዳጅ መንግሥት ሚስጥር አሳልፎ ይሰጣል ማለት በምንም ዓይነት ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ቦብ ውድወርድ የተባለው የዋሽንግተን ፖስት ዘጋቢ በጊዜው የሲአይኤ ዳይሬክተር የነበረውን ዊልያም ኬሲን ተጠግቶ ‹‹The Veil›› በሚል ርዕስ የጻፈውን መጽሐፍ እንዳነብ የመከሩኝ በመጀመርያ የፍትሕ ሚኒስትር በኋላ ደግሞ በፓሪስ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው የሄዱት አቶ ጌታቸው ክብረት ነበሩ፡፡ በመጽሐፉ ላይ የተጠርጣሪውን ሰው ስም ሳይጠቅስ ለእርሱ እንደ ተራ ወሬ ለእኛ ደግሞ አሳሳቢና ከባድ ምርመራ ልናደርግበት የሚገባን ጉዳይ አካፍሎናል፡፡ በጊዜው የተለያዩ የማጣሪያ ዘዴዎችን ተጠቅመን ለሲአይኤ ሚስጥር ሊያቀብል ይችላል የሚባለውን ሰው ለማጋለጥ ብርቱ ጥረት አድርገናል፡፡ በዚህ ጥርጣሬ ውስጥ ብዙ ሰዎች ሊገቡ ይችላሉ፡፡ በአንድ ሰው ላይ በቀጥታ ለመመስከር ግን ህሊናን የሚፈታተን ጉዳይ ነው፡፡ ቪዛ ሳያስመቱ አሜሪካ አገር ሰተት ብለው የገቡ ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንዳንዶቹ እርስዎ በመጽሐፍዎ ላይ ያወደሷቸው ናቸው፡፡ ይሁንና አሁንም ቢሆን በማናቸውም ላይ ደኅንነቱ በእርግጠኝነት ቆሞ ጣቱን የሚቀስርባቸው አይሆኑም፡፡ የአሜሪካ መንግሥት የሚስጥር ሰነዶችን አውጥቶ ለንባብ እስኪለቅ ብንጠብቅ አይሻልም? ዕድሜ ሰጥቶን ለማወቅ ያብቃን፡፡ ብርሃኑ ዲንቃ በሌለ ወንጀል ያላንዳች ማስረጃ ለሦስት ዓመታት ታስሮ ተፈታ ብለዋል፡፡ ገጽ 374 ላይ፡፡ በወዳጄና በማከብረው ብርሃኑ ላይ መረጃ የሰበሰበውና ምርመራ አካሂዶ ለደኅንነቱ ያስተላለፈው ሌላ አካል ነው፡፡ ማዕከላዊ ምርመራ ይቆይ ተብሎ ወደኛ በተላለፈ ጊዜ ለማንም ታሳሪ ያልተደረገውን እንክብካቤ እያደረገ ያቆየው ሚኒስትራችን ነበር፡፡ ቶሎ ከእስር እንዲለቀቅም ብዙ ሙከራ ተደርጓል፡፡ እኔም የውጭ ጉዳይ ሰዎች እንጎብኘው ሲሉ አብሬአቸው እየሄድኩ አጽናንተነዋል፡፡ በሕይወት ቢኖር ኖሮ ይኼንን ይመሰክር ነበር፡፡ ስለዚህ መረጃውም ማስረጃውም የቀረበው በላይ ቤት በኩል ስለሆነ ደኅንነቱን ለቀቅ ቢያደርጉት ይሻላል፡፡ ገጽ 405 ላይ በደኅንነቱ የመሠረታዊ ድርጅት ስብሰባ ላይ . . . ‹‹በወሬና በአሉባልታ ወይም ለግል ጥቅም ሳይሆን፣ ጥራትና ጥናት በተሞላበት ሁኔታ መሥራት አለባችሁ፣ ሕዝቡን በቅንነት ማገልገል አለባችሁ ብዬ ምክር አካፈልኩ›› ያሉትን ደኅንነቱ በፀጋ ነው የተቀበለው፡፡ የኢንተለጀንስ ኮርስ የሚካፈሉ ወጣቶች ሥልጠናቸው ተጠናቆ ሲመረቁ ሁልጊዜም ሥራ ከመጀመራቸው በፊት የምንሰጣቸው ምክር ከእርስዎ ሐሳብ ጋር የሚመሳሰል ነው፡፡ ለግል ጥቅም ተብሎ ወይም ሠራተኛ ለመምሰል የሚቀርብ የሐሰት ሪፖርት የሚያስከትለው ጥፋት ብዙ ስለሆነ ለአባሎቻችን ብርቱ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ እናስተምራለን፣ እንመክራለን፣ እናስጠነቅቃለን፡፡ እርስዎ የተገኙት በሴሚናሩ መዝጊያ ላይ ነበር፡፡ ከዚያ በፊት ግን ለስምንት ቀናት በተካሄደው ውይይት ላይ የብሔረሰቦች ኢንስቲትዩት አባላትና የዩኒቨርሲቲ መምህራን ያደረጉልን ገለጻና ያካፈሉን ምክር እጅግ ጠቃሚ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ የሴሚናሩ መዝጊያ ሥነ ሥርዓት ከተካሄደ በኋላ ለእርስዎ ክብርና ትምህርት ለሰጡን ምሁራን መለስተኛ ግብዣ አድርገን ብርጭቆ ስናጋጭ አጠገብዎ የነበረው ፕሮፌሰር መስፍን፣ ‹‹ጓድ ፍሰሐ ከአብዮቱ ጀምሮ የወደቀውን መንግሥት መደብደባችሁን ለምን አትተውም?›› ያለዎትን ያስታውሳሉ? በዚህ ጊዜ እኔና አለቃዬ ጎን ለጎን ተቀምጠን ስለነበር፣ ንግግሩ እርስዎ ያከሉበት ሳይደመር እኛው ዘንድ የተዘጋጀ ስለነበር ኮሎኔል ተስፋዬ ቀስ ብሎ፣ ‹‹እኛ ምን እናድርግ እነሱ እንዲህ ካላልን ደስ አይላቸውም፤›› ማለቱ ይታወሰኛል፡፡ አዎ ኮሎኔል ተስፋዬ ብዙ ጉዳዮችን በጥንቃቄ እንደሚከታተል አውቃለሁ፡፡ ገጽ 406 ዓይ ጓድ ካሳ ገብሬና ኮሎኔል ተስፋዬ ያሉበትን ቡድን መርተው በኢጣሊያ በኩል ሲያልፉ ሮም ከተማ ላይ የታየውን ድራማ ጠለቅ ብሎ ለማየት አልሞክርም፡፡ ይሁን እንጂ ወደ ዩጎዝላቪያ ከማምራታችሁ በፊት፣ ‹‹እኔ ወደ አገሬ አልመለስም ብዬ ወጥቼ ወደ ከተማ ሄድኩ፤›› ያሉት የቴአትሩ ዓቢይ ክፍል ሆኖ ነው የቀረበው፡፡ ኮሎኔል ተስፋዬ እርስዎ ከኢትዮጵያ ውጭ ሄደው እንደማይቀሩ ገና ከአዲስ አበባ ሳትነሱ ነው የሚያውቀው፡፡ ለዚህ አንድ ምሳሌ ልስጥዎት፡፡ በአብዮቱ ዘመን ባልና ሚስት ልጆቻቸውን ጨምረው በአንድነት ወደ ውጭ እንዲሄዱ አይፈቀድም ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ የእኔ ሚስት ልጆቻችንን ይዛ ወደ አንድ አገር ሄዳ ሳለ እኔ ለሥራ ጉዳይ ወደ ውጭ እንድሄድ ተዘጋጅ እባላለሁ፡፡ ይኼኔ አለቃዬ ቤተሰቤ ወደ ውጭ መሄዳቸውን አላወቀ ይሆናል ብዬ ወደ ቢሮው ሂጄ የእነሱን ውጭ መሆን ነግሬው እኔ ደግሞ መውጣቴ ደንቡን መተላለፍ አይሆንም ወይ? ስለው እባክህን ቀልዱን ተውና ዝግጅትህን ቀጥል፣ ትሄዳለህ አለኝ፡፡ በእውነቱ በእኔ ላይ ያሳየው መተማመን መንፈሴን እጅግ ነበር ያሞቀው፡፡ እርስዎም በዚህ ዓይን ቢያዩት መልካም ነበር፡፡ ስንት ጊዜ ዴሌጌሽን እየመሩ ወደተለያዩ አገሮች የተጓዙ የደርጉ ቁንጮ አባል ውጭ ሄደው ይቀራሉ ማለት ዘበት ነው፡፡ እንዲያውም እርስዎ ሆቴሉን ለቀው ሲወጡ ‹‹የት ሲፈነጥዝ እንደሚውል (ይቅርታ ቃሉን በመጠቀሜ) አይታችሁ ንገሩኝ፤›› ብሎ የተለያዩ ቡድኖች ሳይልክብዎ የቀረ አይመስለኝም፡፡ በመጽሐፍዎ ላይ ያልገለጹት አንድ የውጭ አገር ጉብኝት አለ፡፡ ይኼውም በኬንያ ፕሬዚዳንት አራፕ ሞይ አሥረኛ ዓመት በዓለ ሲመት (ኛኞ ኤራ) ላይ ለመገኘት ወደ ናይሮቢ ሲሄዱ ከተከታዮችዎ አንዱ እኔ ነበርኩ፡፡ ከኬንያ ባለሥልጣናት ጋር ያደረጉትን አስደሳች ውይይት እንተወውና በአምባሳደሩ አማካይነት በአገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንዲሰበሰቡ ተደርጎ በተለያየ ምክንያት ካገራቸው ወጥተው የቀሩ ግማሾቹ እያለቀሱና ደርግን እያማረሩ ሲናገሩ፣ ሌሎቹ ደግሞ በፍርኃትና በልመና ችግራቸውን ሲያመለክቱ፣ ከከበደ ሚካኤል መጽሐፍ ላይ ያነበቧቸውን ግጥሞችና ምሳሌዎች እያንቆረቆሩ ሲሰጡ የነበረው መልስ እጅግ በሳልና አስደናቂ ነበር፡፡ እንዲያውም የተሰበሰበው ሰው ጊዜ ጨምሩልን እያለ ሲወተውት አምባሳደሩ ምን ፈርቶ እንደሆነ አይታወቅም ውይይቱ እንዲቋረጥ አደረገ፡፡ ታዲያ በእኔ በኩል ከሁላችሁም ባለሥልጣናት ጋር ወደተለያዩ ጎረቤት አገሮች ተከታይ ሆኜ ስሄድ ልዩ ሪፖርት ለማቅረብ ባልገደድም ጓድ ፍሰሐ መድረሻ ላጡ ኢትዮጵያውያን ያደረጉት ገለጻና ያስተላለፉት ምክር በጣም ጠቃሚ ነበር ስል ለአለቃዬ የቃል መግለጫ አቀረብኩ፡፡ በዚህ ጊዜ እርስዎ ቢያምኑትም፣ ባያምኑትም ፍሰሐ እኮ ጎበዝና እምነት የሚጣልበት ሰው ነበር ያለኝ፡፡ ደኅንነቱ እውነት መስካሪ ነው፡፡ ገጽ 420 ላይ ለእርስዎና ለኮሎኔል ተስፋዬ አለመግባባት መነሻ የሆነው በየሳምንቱ ከደኅንነቱ በሚላክልዎ የግልጽ ምንጭ ሪፖርት ላይ አቀራረቡን በመተቸት ለፕሬዚዳንቱ አንድ የጥናት ሪፖርት ካቀረቡ በኋላ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ በመሠረቱ እርስዎ ደኅንነቱን በበላይነት ይመለከቱ ስለነበር ጉዳዩን ወደ ላይ ከማሰቀል ኮሎኔል ተስፋዬን ጠርተው በዚህ ጉዳይ እንዲህ ያለ አመለካከት አለኝ ቢሉት ኖሮ ካላሰባችሁት አለመጣጣም ውስጥ አትገቡም ነበር፡፡ በእውነቱ እርስዎ እንዴት እንዳዩት አላቅም እንጂ ቢሯችን የዓለምን ትኩስ ዜናዎች ሞኒተር የሚያደርግባቸው ልዩ ልዩ መንገዶች ነበሩት፡፡ ከማስታወቂያ ሚኒስቴር በተከራየነው ቴሌፕሪንተር ሮይተር፣ አዣንስ ፍራንስ ፕሬስና አሶሼትድ ፕሬስ ደቂቃ በደቂቃ የሚያስተላልፉትን ዜና እንቀበል ነበር፡፡ ከዚህ ሌላ ከቮይስ ኦፍ አሜሪካና ከቢቢሲ በእንግሊዝኛ የሚለተላለፉትን እንዲሁም ከመካከለኛው ምሥራቅና ከጎረቤት አገሮች በፈረንሣይኛ፣ በዓረብኛና በሶማሊኛ የሚተላለፉትን ሞኒተር የሚያደርጉ ብዙ ቋንቋ አዋቂዎች ቀጥረን ስለነበር ወደ አማርኛ እየተተረጎሙ በታይፕ ተጽፈው፣ በማግሥቱ ጠዋት ቢሮ ስንገባ በመጀመርያ እየቀረቡልን እናነብ ነበር፡፡ ታዲያ ሁሉንም በጅምላ ሳይሆን ከኢትዮጵያ ሁኔታ ጋር ተዛማጅነት ያላቸውንና የአገራችንን ጥቅምና ደኅንነት ለማስጠበቅ የሚረዱትን አንቂ ይሆናሉ የምንላቸውን የግልጽ ምንጭ ሪፖርቶች እንጂ ሁሉንም አናግበሰብስም ነበር፡፡ ከውጭ አገር የምናስመጣቸው አፍሪካ ኮንፊደንሻል፣ ዘኢኮኖሚስትና ሌሎችም የኢንተለጀንስ ዘገባዎች የሚያቀርቡ መጽሔቶችም ነበሩ፡፡ በስተመጨረሻ ቤቱን በዓረብኛና በሶማሊኛ ቋንቋ አዋቂዎች አጥለቅልቀው እንደነበር ትዝ ይለኛል፡፡ እጅግ አስቸኳይ ነገር ከተገኘ እስኪነጋ ሳይጠብቁ ቤቴ ስልክ ደውለው ዜናውን ያሰሙኝ ነበር፡፡ ሀቅ እንናገር ከተባለ እርስዎ በየዕለቱ ሬዲዮ እያዳመጡ፣ ጋዜጣና መጽሔት እያገላበጡ የዓለምን ሁኔታ እንደሚከታተሉ ሳልጠራጠር የእኛ ሳምንታዊ የግልጽ ምንጭ ሪፖርት ቆረፈደብኝ ቢሉ ባለመገረም፣ ለመሆኑ እላይ ቤት የእርስዎ ጓደኛ የሆነ ከሬዲዮ የሚተላለፈውን ዜና እንተወውና አንድ ገጽ ጽሑፍ ሳያነብ የሚውል እንደነበረ አያስታውሱም፡፡ ከዚህ በላይ ማለት ስለማልፈልግ ይኼን አርዕስት በዚሁ እዘጋለሁ፡፡ በኢንተለጀንስ ሪፖርት አቀራረብ ግልጽ ምንጭ በመቶኛ የተወሰነ ደረጃ ግምት ይሰጠዋል፡፡ ይኼ በብዙ አገሮች የሚሠራበት ስለሆነ ዝርዝር ጉዳይ ውስጥ አልገባም፡፡ በመጽሐፍዎ ገጽ 412 ላይ ሚኒስትሩና መሥሪያ ቤቱ በሕወሓትና በሻዕቢያ ውስጥ መረጃ አቅራቢዎች ሳያስገቡ ቀርተው መረጃ አያገኙም ነበር ብለዋል፡፡ እንግዲህ እዚህ ላይ ወደ መረጃ ሥውር ምንጭ አቀራረብ ገባን ማለት ታዲያ የሥውር ምንጭ የሥራ ሒደትን በአደባባይ ለመነጋገር በጣም አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ መቼም እርስዎ የሰነዘሩትን አስተያየት አንባቢ ምንም መመራመሪያ መንገድ ባይኖረውም አምኖ ይቀበላል ብዬ አልገትም፡፡ ለመሆኑ ገና በጠዋቱ ወያኔ በበረሃ ተቋቁሞ በየአቅጣጫው ለመዘረጋጋት እንቅስቃሴ በጀመረበት ሰዓት፣ ከውስጥ የተገኙትን መረጃዎች ምርኩዝ በማድረግ አደገኛ አካሄድ መሆኑን በካርታ ላይ እየጠቆመ በሥዕላዊ መግለጫ ኮሎኔል ተስፋዬ ሪፖርት በቀረበበት ዕለት ከማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት የተሰነዘረበትን ትችት ያስታውሱታል? በመከላከያ ሚኒስትሩ ግንባር ቀደምትነት፣ ‹‹ለመሆኑ ደኅንነቱ ካርታ አዥጎርጉሮ የሚያቀርበው እኛ የት ነው ያለነው? ከዚህ ሁሉ የድል ጉዞ በኋላ ምን እያወራ ነው?›› አልነበረም የተባለው፡፡ ገጽ 551 ላይ፣ ‹‹. . . መንግሥት ወያኔን አሳንሶ በማየት በወቅቱ ዕርምጃ ባለመወስዱ ወያኔ ፈጣን ወታደራዊ ዕድገት እያሳየ መጣ፤›› በማለት የሰጡት አስተያየት ትክክለኛና የደኅንነቱን ጥረት ግልጽ አድርጎ የሚያሳይ ነው፡፡ ጓድ ፍሰሐ የመረጃ ምንጭ የሌለው የደኅንነት መሥሪያ ቤት 17 ዓመታት ሙሉ ለመታገል አይችልም፡፡ የመረጃ ምንጭ የላቸውም ያለዎት ሰው ካለ ወደ ውስጥ ሳይገቡ እንዲሁ ሊታዘቡት ይገባል፡፡ በመጽሐፍዎ በተከታታይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ኮሎኔል ተስፋዬ፣ – ወያኔ እርስዎን ለማስወገድ ባደረገው ሙከራ እርሱ ተባባሪ እንደሆነ፣ – የሻዕቢያ ብቻ ሳይሆን የአሜሪካኑ የስለላ ድርጅት ሲአይኤ ተባባሪ እንደነበር በርካታ ማስረጃዎች እንዳለዎት፣ – ኤርትራን ለማስገንጠል በተወሰዱት ዕርምጃዎች ተባባሪ እንደነበር በራሱ አንደበት አረጋግጧል፣ በማለት ምሕረት የለሽ ውንጀላ ከወረዱበት በኋላ ገጽ 419 ላይ ደግሞ፣ ‹‹ተስፋዬ እንደሚነገርለት የጠለቀ የኢንተለጀንስ ባለሙያ፣ ተመራማሪና ፖሊሲ ቀያሽ ሳይሆን ጥሩ የመረጃ ወኪልና ወሬ አቀባይ ነው ብለውታል፡፡ ይኼ እንግዲህ እርስ በርሱ የሚቃረን አገላለጽ ነው፡፡ ለመሆኑ ከፕሬዚዳንት መንግሥቱ ጀምሮ በከፍተኛ አመራር ቦታ ላይ የነበሩት ጓዶች ሁሉ እንደ እርስዎ እያሰቡ እርስዎ ካስቀመጡት ድምዳሜ ላይ ደርሰው ነበር? ይኼም ካልሆነ እርስዎ በተራቀቀ መንገድ ተከታትለው የደረሱበትን ጉዳይ ለምን አጀንዳ አስይዘው የፖሊት ቢሮው እንዲነጋገርበት አላደረጉም? እንደኔ አስተያየት ይኼ ሊታለፍ የሚገባው ጉዳይ አልነበረም፡፡ ከዚህ ቀጥሎ አንባቢን ግራ የሚያጋባ እርስዎ በመጽሐፍዎ ላይ ያሰፈሩትን ጽሑፍ እንዳለ አስቀምጥና ተገቢውን መልስ ለመስጠት እሞክራለሁ፡፡ ‹‹. . . መረጃ መለዋወጥ በሚል ሰበብ በንጉሡ ጊዜ ጀምሮት የነበረውን የሞሳድና የሲአይኤ የወኪልነት ሥራውን ቀጠለበት፤›› ብለዋል፡፡ ይኼንን ላም ባልዋለበት ኩበት…. ብዬ ባልፈው በወደድኩ ነበር፡፡ ነገር ግን እርስዎ ነበር ያሉት ግንኙነት ደርግ ከመጣ ጀምሮ በፍፁም መቋረጡን በቅድሚያ ሳረጋግጥ፣ የግንኙነቱም ዓይነት እርስዎ እንዳሉት አለመሆኑን በማከል ነው፡፡ በመጀመርያ ነገር መረጃ መለዋወጥና መተባበር ሲባል የአገርን ሚስጥር እያወጡ መዘርገፍ አይደለም፡፡ የአገራችንን ጉዳይ ለማወቅ እነሱ ብዙ መንገድ እንዳላቸው ደግሞ መታወቅ አለበት፡፡ እኛ እነዚህ በዓለም ፖለቲካ ግዙፍና ኃያላን የሆኑትን አገሮች የውስጥ ሚስጥራችሁን ንገሩን ብለን እንደማንጠይቃቸው ሁሉ፣ እነሱም የእኛን የውስጥ ጉዳይ ለማወቅ ጥያቄ አያቀርቡም፡፡ ከአብዮቱ ፍንዳታ ወዲህ ጎራ የለወጥን እንደመሆናችን ምንም ዓይነት የትብብር መንገድ አልነበረንም፡፡ ታዲያ ቀድሞም ቢሆን በጊዜው ወዳጅ ከነበሩት አገሮች ጋር የነበረው ግንኙነት በቀጥታ እጅ እስከመስጠት የሚደርስ አልነበረም፡፡ እዚህ ላይ ለመተንተን አስቸጋሪ ይሆንብኛል፡፡ እርስዎ ግን ለማወቅ ጉጉት ካለዎት በቆይታ በደንብ ላብራራልዎት እችላለሁ፡፡ መቼም ከአብዮቱ ፍንዳታ በኋላ አዲስ ካፈራናቸው ወዳጆቻችን ጋር መቀራረብና መግባባት እንዳለብን ባይካድም፣ የአሠራሩ ፕሪንስፕል ፈጽሞ አልተለወጠም፡፡ የኢትዮጵያ ሚስጥር አይሸጥም አይለወጥም፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ሚኒስትራችን ኮሎኔል ተስፋዬ እኔ በእርሱ ሥር እሠራ እስከነበርኩበት ጊዜ የአሠራሩን ፕሪንስፕል አዛንፏል ብዬ አላምንም፡፡ ሆኖም ከጊዜ በኋላ መለወጡንና ከአሜሪካኖች ጋር መመሳጠሩን እናውቃለን ያሉኝ ሰዎች አሉ፡፡ የዚህን ሒደት ወደፊት ለብቻው እናየዋለን፡፡ መቼም ከእርስዎ መጽሐፍ ላይ በማስታወሻ የያዝኳቸው ነጥቦች ብዙ ናቸው፡፡ መልስ ወይም አስተያየት ሳልሰጥባቸው ጽሑፌን ማጠቃለል የማይገባኝ ሁለት ወይም ሦስት ጉዳዮች ስለቀሩ እንደሚከተለው አብራራለሁ፡፡ የመጀመርያው የደኅንነቱ መሥሪያ ቤት አወቃቀር በማንና እንዴት እንደተዘጋጀ የጻፉት ነው፡፡ በአብዮቱ መጀመርያ ዓመታት የታየው ትርምስ አብቅቶ ሶማሊያም የሞከረችው ወረራ በድል ከተጠናቀቀ በኋላ ለደኅንነቱ አዲስ መዋቅር ተዘጋጅቶ፣ ሁሉንም የመረጃ ቤቶች የሚያሰባስብ መሥሪያ ቤት እንዲቋቋም በበላይ አካል ውሳኔ መተላለፉ ይታወሳል፡፡ ለዚህ ዝግጅት ኃላፊነቱን የወሰደው ኮሎኔል ተስፋዬ ነበር፡፡ የደኅንነቱን አመራር ለመረከብ ደረስን፣ ደረስን ከሚሉ የኢንተለጀንስ ኦፊሰሮች ጋር ዝግጅቱን የመራሁት እኔው ራሴ ነበርኩ፡፡ ቀደም ባሉት ዓመታት ብዙ የአሠራር ልምዶችን ቀስመን ስለነበር በእውነቱ ማዋቀሩ ችግር አልፈጠረብንም ነበር፡፡ እርግጥ አጠቃላይ መዋቅሩን ነድፈን የሥራ ድርሻው ምን እንደሚሆን ካረቀቅን በኋላ የመዋቅር ሥራ ኤክስፐርቶች የሆኑት እነ ማንደፍሮ ተገኝ ዳስሰውና መርምረው ነበር የመጨረሻ ቅርፁን ይዞ እንዲወጣ የተደረገው፡፡ በመጽሐፍዎ ገጽ 419 ላይ፣ ‹‹በ1971 መዋቅሩ በምሥራቅ ጀርመን ባለሙያዎች የአገርና ሕዝብ ደኅንነት ሚኒስቴር ተብሎ ጥናቱ ለመንግሥት ቀርቦ ተቀባይነት አገኘ፤›› የሚል አንብቤያሁ፡፡ ይኼ ፈጽሞ የተሳሳተ መግለጫ ነው፡፡ ይልቅስ መዋቅሩን በምናዘጋጅበት ጊዜ ከሶቪየት ኅብረት ጀምሮ ከኩባ፣ ከምሥራቅ ጀርመን፣ ከቼኮዝሎቫኪያና ከሌሎችም ሶሻሊስት አገሮች የደኅንነት ተጠሪዎች ጋር እየተገናኘን የልምድ ልልውጥ እናደርግ ስለነበር፣ በዚያን ጊዜ ካጋጠሙን ነገሮች አንድ ሁሉን ላጫውትዎት፡፡ ይኼን ሥራ የምንሠራው በልዩ ካቢኔ አነስተኛ አዳራሽ ውስጥ ስለነበር የየዕለቱን የሥራ ሒደት ኮሎኔል ተስፋዬ ስልክ እየደወለ ይጠይቅ ነበር፡፡ አንድ ቀን በወቅቱ የነበረው የአገር አስተዳደር ሚኒስትር መዋቅሩ እየተዘጋጀ ያለው አዲስ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ለመፍጠር ስለሆነ ይኼ ትክክል አይደለም፣ እንደ ቀድሞው በምክትል ሚኒስትር ደረጃ አገር አስተዳደር ውስጥ የደኅንነቱ ዘርፍ እንዲኖር ማድረግ አለብን በማለት ይከራከር እንደነበር ከአንድ ምንጭ ተረዳን፡፡ ታዲያ ይኼንኑ ለኮሎኔል ተስፋዬ ስንነግረው እኔው ራሴ እወያይበታለሁ በማለት እንደሚያሳስብ ነገረን፡፡ በሌላ ጊዜ ከምሥራቅ ጀርመን በዚሁ ጉዳይ ምክርና ሐሳብ እንዲያካፍለን የተላከው ጄኔራል ኖይቨር የተባለ የደኅንነት ከፍተኛ መኮንን በተለያዩ አገሮች አብዮት ሲፈነዳ የደኅንነቱን ሥራ ለመምራት የሚመረጠው ከሠራተኛው ወገን ነው፣ ለምሳሌ በኒካራጉዋ ለዚህ ሥራ የተመረጠው ልኳንዳ አራጅ ነው፣ በሌላ አገር ደግሞ (የአገሩ ስም ጠፋኝ) ጫማ ሰፊ ነው… እያለ ሲተነትን ቆይቶ ሄደ፡፡ በተለመደው አኳኋን ኮሎኔል ተስፋዬ ደውሎ የዕለቱ ውሏችን እንዴት እንደሆነ ሲጠይቀኝ ሰውየው ያካፈለንን ልምድ ነገርኩት፡፡ ታዲያ እርሱ ለዚህ የሰጠው አስተያየት ምን መሰለዎት? ‹‹አይ ሰውዬው ልምዱን ማካፈሉ ክፉ አይደለም፡፡ ነገር ግን ደኅንነቱን የሚመራ ሰው ቄራ ወርጄ እስክፈልግ ሌላ ሌላውን ቢያስተምረን ጥሩ ነው፤›› ብሎ ንግግሩን አቆመ፡፡ ይኼው የጀርመን ጄኔራል ኃይለኛ ስለነበር ጠረጴዛ እየደበደበ የኔን ሐሳብ ካልተቀበላችሁ እያለ ስለነበረ ገለጻ የሚያደርግልን፣ የዕለቱ ውይይታችን አብቅቶ ለማግሥቱ ሌላ ቀጠሮ ይዘን ስንለያይ የኮሚቴው አባላት ወደኋላ ቀረት ብለው የምንጠይቅህ ነገር አለ አሉኝ፡፡ ምንድነው? ስላቸው ይኼው ሰውዬ ልምዱንና ዕውቀቱን እንዲያካፍለን ነው እንጂ የምንወያየው እንዲህ እየደነፋ መናገሩ ለምንድነው? አንተም ዝም ማለትህ ትክክል አይደለም አሉኝ፡፡ እኔም ይኼ እኛን ለማስተማር የመጣውን የወዳጅ አገር እንግዳ ሳናስቀይም በብልኃት ብናስተናግደው ይሻላል ብዬ ነው እንጂ ለተከታዩ ጊዜ ንግግራችን ብልኃት እንፈልጋለን አልኳቸው፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ እኔ ከሰውየው ጋር አተካራ ብገጥም ፈጥነው ለፖለቲካው ክፍል ወሬ አስተላልፈው ያስደፉኛል ብዬ ፈርቼ ነው እንጂ የተቆጠብኩት፣ እንዴት እንደማስተናግደው አጥቼበት አልነበረም፡፡ ለማናቸውም በተከታዩ ጊዜ መጥቶ በለመደው አኳኋን መረር እያለ ሲናገር ሐሳቡን እስኪደመድም ጠበቅኩና ‹‹ኮምሬድ ጄኔራል በዙሪያዬ ያሉት መኮንኖችና እኔ በኢንተለጀንስ ሙያ ሰፊ ልምድ ያለን ነን፡፡ ትናንት ነፃ እንደወጡት አንጎላና ሞዛምቢክ ከሥር ሀ ብለን ትምህርት የሚሰጠን አይደለንም፡፡ የሰሞኑና የዛሬው ግንኙነታችን የሶሻሊስት አገሮችን ልምድና አሠራር እየቀሰምን ለእኛ በሚስማማ መልክ ለመንደፍ ስለሆነ አቀራረብዎን በዚህ አኳኋን ቢያስተካክሉልን ይሻላል…›› ስል በእውነት ነው የምልዎት ሰውየው ሰግጠጥ ሲል፣ የእኔ ጓደኞች ደግሞ በደስታ መቀበላቸው ከጠረጴዛው ሳንነሳ ይነበብ ነበር፡፡ ይኼ የውስጥ ጉዳይ እንደዚህ በስፋት የሚተነተን መሆን አልነበረበትም፡፡ ዝርዝር ነገር ውስጥ ያስገባኝ እርስዎ በመጽሐፍዎ ላይ የምሥራቅ ጀርመን ደኅንነት መዋቅሩን እንዳዘጋጀልን አድርገው የጻፉት ወደ ኋላ ተመልሼ ብዙ ነገሮች እንዳስታውስ ስላደረገኝ ነው፡፡ ምዕራባውያን አገሮች ደኅንነት በምሥራቅ ጀርመን ደኅንነት ወይም ስታዢ ሥር ገብቷል እያሉ ያናፍሱ የነበሩትን መጨበጫ የሌለው ወሬ እርስዎም በመጽሐፍዎ ላይ ደግመውት በማየቴ በጣም አዝኛለሁ፡፡ የኢትዮጵያ የመረጃ ድርጅት የማንም ጅራት ሆኖ አያውቅም፡፡ ይልቁንም ምዕራቡም ምሥራቁም ለኢትዮጵያ ደኅንነት መሥሪያ ቤት ያዥጎድጉዶ የነበሩትን አድናቆት ከሚያውቁ ገለልተኛ ሰዎች ጠይቀው ቢረዱ መልካም ነው፡፡ ምናልባት እርስዎ አለቃችንና እኛ ትሁት ጭፍራዎችዎ የሥራ ውጤታችን በዓለም እንዲናኝ ለማድረግ የቤቱ ዲሲፕሊን ገድቦ ስለያዘን መናገር እያፈርን ቆየን እንጂ፣ የውስጥ ግብግቡን መልክ አስይዘን በዓለም አቀፍ ደረጃ ፍልሚያውን እንደተያያዝነው አሌ የማይባል ሀቅ ነው፡፡ ዛሬ ሁሉም ነገር ስላለፈ ጠላቶቻችንም ሆኑ ወዳጆቻችን ቢጠየቁ በግልጽ እንደሚናገሩ አልጠራጠርም፡፡ ገጽ 442 ላይ ‹‹. . . በዓሉ ግርማ በደኅንነት በኩል ዕርምጃ ተወስዶበታል የሚል የራሴን ግምት ወሰድኩ፤›› ካሉ በኋላ፣ ‹‹በዓሉን የመሰለ ታዋቂ ሰው በተስፋዬ ወልደ ሥላሴ ውሳኔ ሊሆን እንደማይችልም በእርግጠኝነት መናገር ብቻ ሳይሆን ከደኅንነት ሚኒስትሩ አረጋግጫለሁ፤›› ብለው በዚህ አኳኋን ሁኔታዎችን አመሳክረው ወቀሳውን ሙሉ በሙሉም ባይሆንም፣ ከኮሌኔል ተስፋዬ ትከሻ ላይ በማውረድዎ አመሰግንዎታለሁ፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ሌላ አስተማማኝና ጠጣር መረጃ ልሰጥዎት ብችልም ለጊዜው በዚህ ብንገታ መልካም ይመስለኛል፡፡ አሁንም ደኅንነቱን ለቀቅ ያድርጉት፡፡ ገጽ 496 ላይ ከአሜሪካ ከኤምባሲ አንደኛ ጸሐፊ ጋር ፕሬዚዳንት መንግሥቱን ከሥልጣን በማስወገድ ዙሪያ እንዴት በግብዣ ላይ በግልጽ እንደተወያያችሁ ገርሞኛል፡፡ በመጀመሪያ ነገር አጠገብዎ የፕሮቶኮል ሰዎች አልነበሩም? እንዴትስ ከእርስዎ ደረጃ ጋር ከማይስተካከል ሰው ጎን አስቀምጡዎት? በማስከተል በደርግ መንግሥት ከፍተኛ አመራር ውስጥ ላሉት ሰው ኰሎኔል መንግሥቱን ከሥልጣን አስወግዱ ብሎ በግልጽ ምክር ያካፍላል? ኩዴታ አብዛኛውን ጊዜ በረቀቀ ሚስጥር ተይዞ ይበስልና ፈንድቶ ሲወጣ ብቻ ነው ድንገተኛ ጉዳይ ሆኖ የሚታየው፡፡ በሱዳን እ.ኤ.አ. በ1971 በፕሬዚዳንት ኑሜሪ ላይ የቅርብ ረዳቶቻቸው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ለማድረግ በጠራራ ፀሐይ ሲንቀሳቀሱ ገና ሳይመሽ ኒሜሪ ከእጃቸው አምልጠው ጦር አስተባብረው እንደደቆሷቸው ይታወሳል፡፡ ይኼው አካሄድ በጄኔራል መርዕድ ንጉሤ ሲደገም እንዴት በሌላ አገር ከተደረገው ሙከራ ትምህርት አልቀሰሙም ብለን ነበር፡፡ አሁን ደግሞ በምግብ ጠረጴዛ ዙሪያ የመንግሥት ግልበጣ ውይይት ተደረገ ያሉት በጣም ገርሞኛል፡፡ የኰሎኔል ተስፋዬ ተካፋይነትስ እንዴት ነበር ብዬ አልጠየቅዎትም፡፡ ይልቅስ ነገርን ነገር ያነሳዋልና እርስዎ እኮ የጄኔራሎቹን የመፈንቅለ መንግሥት ሴራ ደርሰውበት እንዴት እንደሚያስተናብሩት ጠፍቶዎት ሙከራውን ለማክሸፍ ከጓደኞችዎ ጋር ብዙ ልፋት ውስጥ ገብተዋል፡፡ በዋዜማው ጓደኛዎ መጥቶ ሲነግርዎት ሌሎች ሰዎችን ፍለጋ ጋራ ለጋራ ከመዞር መቼም ለወዳጅዎ ለኰሎኔል ተስፋዬ ይንገሩ ብዬ ሐሳብ ባላቀርብም ፕሬዚዳንቱ ለርስዎ ሩቅ አልነበሩም፡፡ ለእንደዚህ ያለ ነገር ጊዜ መስጠት አያስፈልግም ነበር፡፡ የጋዜጣ ሪፖርተር ይመስል በጠዋት በማስታወቂያ ሚኒስቴር በኩል ዞረው ለምን ወደ ቢሮዎ ሄዱ? ኩዴታው መጀመሩን ለማብሰር ነው? ወይስ ከዕይታ ገለል ብለው ለማድፈጥ? ለሁሉም በተከታታይ ሙከራውን ለማክሸፍ የተጫወቱት ሚና ዋጋ የሚሰጠው ነበርና በዚሁ እናካክሰዋለን፡፡ ስለደርግ ብርታት/ድክመት በመጽሐፍዎ ላይ ብዙ ሐተታ ማስፈርዎን ተመልክቻለሁ፡፡ የኔ ትኩረት ደግሞ ደኅንነቱን በሚመለከት በተባለው ላይ ስለሆነ አጠቃላይ ጉዳይ በጥልቀት ለማየት አልፈለግሁም፡፡ ሆኖም ለደርግ ውድቀት የተለያዩ ምክንያቶች እንዳሉ ገጽ 564 ላይ ጨረፍ ጨረፍ አድርገው የጻፉትን ስላየሁ፣ ቀድሞ በጃንሆይ ዘመነ መንግሥት በምንጽፋቸው ጥናታዊ ሪፖርቶች ‹‹ሳይሰበር ጠግን፣ ሳይሸበር ለጉም›› እያልን እንደመከርን ሁሉ፣ የደርግ ሥልጣን ከማክተሙ በትንሹ ከሦስት ዓመት በፊት ደግሞ ልዩ ጥናታዊ ሪፖርት ማቅረባችንን አስታውሳለሁ፡፡ የዚህኛው የአቀራረብ ዘይቤ ደግሞ ‹‹ሳይቃጠል በቅጠል›› የሚል እንደነበረ ዕድሜ ሰጥቶኝ የሥራው ተካፋይ ስለነበርኩ በሚገባ አስታውሰዋለሁ፡፡ የደርግ የትግል ጉዞ ፈጣን እመርታ ሲያሳይ ቆይቶ በአንድ ወቅት ዕርምጃው ከመገታቱም ባሻገር ቁልቁል የመውረድ አዝማሚያ በታየበት ጊዜ ደኅንነቱ የራሱን ጥናትና ምርምር አካሂዷል፡፡ በዚህ ዓቢይ ተግባር ተካፋይ የነበሩት መሥሪያ ቤታችን በልዩ የጥናት ግብረ ኃይል ያደራጃቸው ጓዶች ነበሩ፡፡ የጥናቱን ቡድን የመራው አንድ ከፍተኛ የኢንተለጀንስ መኰንን እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡ ከ12 በላይ የሚሆኑ የጥናቱ አባላት በቡድን ተከፋፍለው የአገሪቱን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊና የወታደራዊ ጉዳዮች በጥልቀትና በጥራት መርምረው በጊዜው የደረስንበትን ደረጃ ገምግመው በጣም ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው ጥናት አቅርበው ነበር፡፡ የዚህ ጥናት ቡድን ሥራ ተፈጭቶና ተሰልቆ እንዳበቃ በሚኒስትራችን መሪነት እኔና የዋና መምርያ ኃላፊዎች በትምህርት ቤቱ የሰብሰባ አዳራሽ ተሰብስበን ሰፊ ውይይት አካሂደናል፡፡ ውይይቱን ስናደርግ በቪዲዮ እየተረቀረጽን ስለነበር አንዳንድ ጉዳዮችን ስናነሳ እንኳ ምንም ዓይነት መቆጠብ አልነበረብንም፡፡ ለማናቸው የደኅንነቱ ከፍተኛ አመራሮች የሚታረሙ፣ የሚስተካከሉና የሚመረመሩ ነጥቦችን እየጠቆምን ጥናቱ የመረጃ ቅርፁን ካገኘ በኋላ ኢንሳይሎፒዲያ የሚያህል ጥራዝ ተሠርቶ ለፕሬዚዳንቱ እንዲቀርብ መዘጋጀቱን አስታውሳለሁ፡፡ መቼም የዚያን ጊዜ ሁኔታ ሳስታውስ ዝግጅቱ ምንም ዓይነት ችግር ሳይፈጥርብን የተካሄደ ቢሆንም፣ በአቀራረቡ ላይ ግን የሚኒስትራችን ጭንቀት እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ ለሁሉም ደኅንነቱ የቤት ሥራውን በተገቢው ሰዓት መርምሮ ስላቀረበ ዛሬ ወደኋላ ተመልሶ ነበሩ የሚባሉ ጉድለቶች ዝርዝር አቅራቢ አይሆንም፡፡ በዚህ አኳያ አንዳንድ ነገሮች ጠቋቁሜአለሁ ብሎም በትምክህት ማስታወሱም ከእርሱ የሚጠበቅ አይሆንም፡፡ ባለቀ ሰዓት ምን ለመሆን? እ.ኤ.አ. በ1960ዎቹ በቅኝ ግዛት ሥር የነበሩት የአፍሪካ አገሮች ለነፃነት ትግል በሚያደርጉበት ጊዜ አንድ የአፍሪካ መሪ (የአልጄሪያ ፕሬዚዳንት ቤንቤላ ይመለስሉኛል) መድረክ ጨብጠው ለአርነት ታገዮች ትንሽ፣ ትንሽ እንሙትላቸው እንዳሉት ሁሉ የከፍተኛው አመራር አባላት ሁሉንም ነገር አጥርታችሁ ስለምታውቀት፣ ዛሬ ይኼን የመሰለ ትንታኔ ውስጥ ገብቶ ጊዜ ከማጥፋት ለውድቀት ምክንያቶች ናቸው ከተባሉት ውስጥ ደረጃው ቢለያይም ትንሽ፣ትንሽ ተቋድሶ ሌላውን ለታሪክ ትቶ መግፋቱ የተሻለ ይመስለኛል፡፡ መልስ ያልሰጠሁባቸው ሌሎች ጥቃቅን ጉዳዮች እንዳሉ ባውቅም በዚሁ ባበቃ የተሻለ ይመስለኛል፡፡ በመጨረሻ ግን አንድ ሐሳብ ብወረውር ምን ይመስልዎታል? የጄኔራሎቹን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ለማክሸፍ በዕለቱ ብዙዎቻችሁ ተረባርባችሁ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ እርስዎም በዙሪያዎ የተመለከቱትን አሰባስበው ከአንድ ዕይታ ውስጥ አስገብተውናል፡፡ ይሁን እንጂ መጀመርያ መረጃ ያቀረበለዎት ሰው በግብግቡ መሀል የት እንደደረሰ አልገለጹልንም፡፡ የመረጃ ምንጭን መሸፈን ትክክል ስለሆነ ለምን ስለእርሱ አልጻፉም ብለን መጠየቅም የለብንም፡፡ ነገር ግን እርስዎ ያ ወዳጅዎ ያቀረበልዎትን መረጃ አፍኖ ከማስቀረት በማንም በኩል ይሁን ስለጉዳዩ አስቸኳይ ውይይት አድርገው ለዕርምጃ አወሳሰድ ቢሰለፉ ኖሮ፣ ሙከራውን ያከሸፉ ተብሎ እጅግ ከፍተኛ አድናቆት ያተርፉ ነበር፡፡ እንደ እርስዎ ከውጭ ሆኖ ሳይሆን መፈንቅሉን ካደራጁት ሰዎች መካከል ሰርጎ ገብቶ ቀደም ብሎ ዕርምጃ ያላስወሰደ አንድ ሌላ ሰው አለ፡፡ በእርስዎ ትንታኔ ውስጥ ስሙን አላነሱትም፡፡ በማክሸፉ ዙሪያ የእርሱስ ተሳትፎ እንዴት ይገመገማል? ሌሎች ደግሞ መሀል ሰፋሪ ሆነው ቆይተው ቁርጡ ሲታወቅ ተሳታፊ የሆኑ እንዳሉ ይታወቃል፡፡ መቼም የልጅ አዋቂ ያሉትን የሻምበል መንግሥቱ ገመቹ ቁርጠኛ አቋምና የላቀ ተሳትፎ ልዩ ቦታ እንደሚሰጡት አልጠራጠርም፡፡ ዝናሩን ግጥም አድርጎ ጠመንጃውን አንግቦ ሳትጠሩት ከች ያለው ጓድ ካሳ ገብሬም ሌላው ተደናቂ የአብዮቱ ወገን ነው፡፡ ስለኰሎኔል ተስፋዬ ምንም ነገር ማለት ስለማይፈልጉ የእርሱን ለሌሎች ቢተው ይሻላል፡፡ ዞሮ ዞሮ ያ ደርግን ለማስወገድ የተደረገ እንቅስቃሴ በምን፣ በማንና ለምን እንደ ከሸፈ ለታሪክም ቢሆን ቢመረመር ጥሩ ሳይሆን አይቀርም፡፡ እርስዎ ቢጽፉ ይጻፉ፣ ስላልጻፉት ግን እኔም ትንሽ ትንሽ ያወቅኋቸው ጉዳዮች ስላሉ ለአንባቢያን መወርወሬ አይቀርም፡፡ ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው በቀድሞ መንግሥት የአገርና የሕዝብ ደኅንነት ጥበቃ ምክትል ሚኒስትር፣ ከዚያም በሳዑዲ ዓረቢያ የኢትዮጵያ መንግሥት ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ነበሩ፡፡ ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡