ምንም ዓይነት ሕመም ሳይኖርበት ታማሚ በመምሰል መንገድ ላይ በመተኛት ሲለምን ነበር ተብሎ የተጠረጠረ ወጣትና ግብረ አበሩ፣ ከልመና ካገኙት 350 ሺሕ ብር ጋር በቁጥጥር ውለው ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
ተከሳሾቹ የ25 ዓመት ዕድሜ ያለው ወጣት ብርሃኑ ቦጋለ የሳንባ ሕመምተኛ በመሆን መንገድ ላይ የሚተኛ መሆኑን፣ የ26 ዓመት ዕድሜ ያለው ቢሻው የኔው የተባለው ግብረ አበሩ ደግሞ ልመናውን ያስተባብርለት ነበር ተብሏል፡፡ ሁለቱም በየካ ክፍለ ከተማ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ነዋሪ መሆናቸውን፣ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ የመሠረባቸውን ክስ ያስረዳል፡፡
በማታለል ወንጀል በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቀራኒዮ ምድብ ወንጀል ችሎት ክስ የተመሠረተባቸው ሁለቱ ግለሰቦች እጅ ከፍንጅ መያዛቸው በክሱ የተገለጸው፣ በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 02 ልዩ ቦታው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ረጂ ቅርንጫፍ አካባቢ ነው፡፡ የሕዝብን ልብ በሚነካና የሐዘኔታ ስሜት በሚፈጥር የድረሱልን ዓይነት የማታለል ተግባር ላይ እንዳሉ፣ ፖሊስ ተጠራጥሮ ባደረገው ክትትል መያዛቸው ተገልጿል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ፍርድ ቤት ቀርበው ዋስትና ተፈቅዶላቸው ለጥቅምት ወር 2009 ዓ.ም. የተቀጠሩ ቢሆንም፣ ‹‹ወንድማችሁን አትለፉት በሳንባ ሕመም የሚሰቃይ ወጣት…›› በማለት ሕዝብን በማሳዘን ልመናውን ሲያስተባብር ነበር የተባለው ቢሻው የኔው ድርጊቱን በማመን፣ ተሰብሮ እንዲታይለት ለፍርድ ቤቱ በማመልከቱ ሐምሌ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. የቅጣት ውሳኔ ተሰጥቶበታል፡፡ በመሆኑም በድርጊቱ ተፀፅቶ በማመኑና የፍርድ ቤቱንም የሥራ ጊዜ ባለመሻማቱ በአሥር ወራት ፅኑ እስራትና በ500 ብር እንዲቀጣ ተወስኗል፡፡
የሳንባ ሕመምተኛ በመምሰል ነጠላ ለብሶ፣ ሻሽ አስሮና አፉን በበሽታ መከላከያ ሸፍኖ መሬት ላይ ተኝቶ የነበረው ብርሃኑ ቦጋለ፣ በቀጠሮው ጊዜ ጥቅምት ወር ላይ ይቀርባል፡፡
ከሁለቱ ተከሳሾች ላይ የተገኘው 350 ሺሕ ብር ፖሊስ በኤግዚቢት እንደያዘው ለማወቅ ተችሏል፡፡