ፌዴሬሽኑ የአትሌቶቹን ብቃትና ያስመዘገቡትን ወቅታዊ የውድድር ሚኒማ በሟላት የሚመለመሉበት የማጣሪያ ውድድሮችን በተለያዩ የአውሮፓ አገሮች ሲያካሄድ ሰንብቷል፡፡ በማጣሪያው ከፍተኛ ግምት ተሰጥቷቸው ከነበሩ ቀነኒሳ በቀለና መሰለች መልካሙ የመሳሰሉ ታዋቂ አትሌቶች ከምርጫ ውጪ ያደረጋቸውን ውጤት ማስመዝገባቸው ከወዲሁ ታውቋል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሽኑ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በሆላንድ ሄንግሎ ባዘጋጀው የ10,000 ሜትር ማጣሪያ ውድድር ከ13 በላይ አትሌቶች ተካፋይ ነበሩ፡፡ በውድድሩ ከቀረቡት አትሌቶች መካከል ይገረም ደምበላሽ፣ አባዲ እምባይና በላይ ጥላሁን ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ ይዘው ሲያጠናቅቁ፣ በሴቶች ደግሞ አልማዝ አያና፣ ገለቴ ቡርቃና ጥሩነሽ ዲባባ ተከታትለው መግባታቸው ታውቋል፡፡ ፌዴሬሽኑ በማጣሪያው የተመዘገበውን ሰዓት እንደ መስፈርት የሚጠቀም ከሆነ እነዚህ አትሌቶች ለሪዮ ኦሊምፒክ የሚያበቃቸውን ሚኒማ ማሟላት ይችላሉ ማለት ነው፡፡ ይሁንና ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ በርቀቱ የአገሪቱን ተወካዮች በይፋ አላሳወቀም፡፡ በሌላ በኩል በማጣሪያው ከፍተኛ ግምት ተሰጥቷቸው ወደ ሄንግሎ ካመሩት መካከል በወንዶች ቀነኒሳ በቀለ፣ ኢብራሂም ጀላን፣ ብርሃኑ ለገሰ፣ የኔው አላምረው፣ ኢማና መርጊያና ሙሉ ዋሲሁን በሴቶች ደግሞ መሰለች መልካሙ በሄንግሎ ውድድር የተዘጋጀውን ርቀት ማጠናቀቅ ሳይችሉ መቅረታቸው ታውቋል፡፡ የተቀመጠው ቀነ ገደብም ባለፈው ዓርብ ሰኔ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. አብቅቷል፡፡
በዳይመንድ ሊግና በግራንድ ፕሪ በሚደረጉ የግል ውድድሮች የተሻለ ሰዓት ያላቸው አትሌቶች የሚለዩበት የአምስት ሺሕ ሜትር የማጣሪያ ውድድሩ እስከ ሐምሌ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ እንደሚቀጥል ከፌዴሬሽኑ የወጣው መረጃ አመልክቷል፡፡