ጆሮ ጭው የሚያደርገው የሉን ጩኸት በቀላሉ ከአዕምሮ አይጠፋም። ይህ ወፍ የሚገኘው በካናዳ፣ በአውሮፓና በሰሜናዊ ዩናይትድ ስቴትስ ባሉ ሐይቆችና ወንዞች አቅራቢያ ሲሆን፣ ኮሽታ በማይሰማባቸው በእነዚህ አካባቢዎች ድምፁ ከርቀት ያስተጋባል።
በውኃ አካላት አካባቢ የሚኖረው ሉን በዩናይትድ ስቴትስ የሚኒሶታ ግዛት መለያ ምልክት ነው፡፡ ሉኒ በተባለው የካናዳ ባለ አንድ ዶላር ሳንቲም ላይም ሥዕሉ ይገኛል። ይህ ወፍ ከቦታ ቦታ የሚፈልስ ሲሆን፣ የቅዝቃዜውን ወቅት የሚያሳልፈው በስተ ደቡብ ባሉ አገሮች ነው።
ሉኖች በጣም አስደናቂ የሆኑ የተለያዩ ድምጾችን ማውጣት ይችላሉ። ምሽት አካባቢ ወይም ማታ ላይ የሚያሰሙት የማላዘን ዓይነት ድምፅ ነው፡፡ ወንድና ሴት ሉኖች እርስ በርስ ለመግባባት አሊያም ከጫጩቶቻቸው ወይም ከሌሎች ሉኖች ጋር ለመነጋገር እንደ ጉጉት ዓይነት ድምፅ ያወጣሉ። አደገኛ ሁኔታ ሲኖር የሚያሰሙት የማስጠንቀቂያ ድምፅም አለ፤ እንደ ማስካካት ያለው ይህ ድምፅ ‹‹የእብደት ሳቅ›› ተብሎም ተገልጿል። ሉኖች በሚበሩበት ጊዜ የሚያሰሙት ድምፅም አለ፡፡
ሉኖች ቀጭንና ወፍራም ድምጾችን እያከታተሉ በማውጣት የሚያሰሙት ድምፅም አለ። እንዲህ ያለውን ድምፅ የሚያወጡት ተባዕቶቹ ብቻ ሲሆኑ፣ በርድዎች ካናዳ የተባለው መጽሔት እንደገለጸው፣ ይህን የሚያደርጉት ‹‹የመኖሪያ ክልላቸውን ለማስከበር ነው፡፡ እያንዳንዱ ተባዕት የራሱ የሆነ የተለየ ድምፅም ያወጣል። የወፉ ክብደት በጨመረ መጠን ድምፁም ጎርናና ይሆናል፡፡ የመኖሪያ አካካቢ ሲቀይርም ድምፁን ይለውጣል፡፡
- ንቁ! ኅዳር 2012 ዓ.ም.