ከጥቂት ቀናት በፊት ከዱባይ ተይዘው የመጡት የዙና ትሬዲንግ ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘሪሁን ጌታሰው፣ ዙና ትሬዲንግ የጭነት መኪናዎችን ያስመጣል በማለት ከሰበሰቡት 71 ሚሊዮን ብር ግማሹ ወይም 50 በመቶ የሚሆነው መገኘቱን ምንጮች ለሪፖርተር ጠቆሙ፡፡
እንደ ምንጮቹ ገለጻ፣ ግለሰቡ ከአገር መጥፋታቸው እንደታወቀ ጉዳዩ በመገናኛ ብዙኃን ይፋ ሲሆን፣ ከደንበኞች ተሰበሰበ የተባለው ገንዘብ 71 ሚሊዮን ብር የነበረ ቢሆንም አቶ ዘሪሁን እሳቸው እጅ የደረሰው 61 ሚሊዮን ብር ብቻ ነው፡፡ ቀሪው አሥር ሚሊዮን ብር እሳቸው አገር ውስጥ ባልነበሩበት ወቅት በሠራተኞቻቸው የተሰበሰበ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
አቶ ዘሪሁን ከሰበሰቡት ገንዘብ ላይ 25 ሚሊዮን ብሩን መኪኖች እንዲያመጡላቸው ለአንድ ግለሰብ መስጠታቸውን በመግለጻቸው ከእኚህ ግለሰብ መኖሪያ ቤት ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ እንዲሁም 269,000 ዶላር የሚሆን መገኘቱን ምንጮች አመልክተዋል፡፡ ግለሰቡ በአቶ ዘሪሁን እንዲያስመጡ ከተጠየቁት ሲኖ ትራኮች ስምንት አስመጥተው መኪኖቹ ጂቡቲ ወደብ ላይ እንደሚገኙም መናገራቸውን ጠቁመዋል፡፡
የዙና ትሬዲንግ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘሪሁን ከሰበሰቡት 18 ሚሊዮን ብር የሚሆነውን ደግሞ ሌላ ግለሰብ ሰሊጥ እንዲያስመጣላቸው መስጠታቸውን መጠቆማቸውን ምንጮቹ ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ስለዚህኛው ገንዘብ ወይም ገንዘቡ ተሰጣቸው ስለተባለው ግለሰብ ግን እስካሁን የተገኘ ማስረጃ እንደሌለ ከምንጮቹ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
በሌላ በኩል በአቶ ዘሪሁን አዲስ አበባ ውስጥ የተያዙ ስምንት መሬቶች እንደነበሩ፣ ከእነዚህ መካካል ስድስቱን እንደሸጧቸው፤ ነገር ግን በለገጣፎ የሚገኙ 500 ካሬ ሜትር ሁለት መሬቶችን መምራታቸውን ከምንጮቹ የተገኘው መረጃ ያሳያል፡፡ ቀደም ብለው በግላቸው ዙና ትሬዲንግ ላይ ክስ የመሠረቱ ደንበኞች በተለምዶ ወርቁ ሠፈር ከሚባለው አካባቢ በአቶ ዘሪሁን ስም የተያዘ መሬት አግኝተው ማሳገዳቸውንም ምንጮቹ ይናገራሉ፡፡
እንደ ምንጮቹ ገለጻ የተገኘው ዶላር ወደ ፌዴራል ወንጀል ምርመራ ዘርፍ (ማዕከላዊ) ሲላክ ብሩ ደግሞ መገናኛ ቅርንጫፍ ንግድ ባንክ እንዲገባ ተደርጓል፡፡
ምንጮቹ እንደተናገሩት አቶ ዘሪሁን ዓርብ ሰኔ 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው የነበረ ሲሆን፣ ጉዳዩን ዳግም ለመመልከት ፍርድ ቤቱ ለሰኔ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጣይ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡