በ2009 በጀት ዓመት 230 ሺሕ ቶን ቡና ለውጭ ገበያ ለማቅረብና 970 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደሚያገኝ ማቀዱን ንግድ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
በንግድ ሚኒስቴር የቡና ገበያ ዳይሬክተር አቶ ጌታሁን ቢኮራ እንደገለጹት፣ ለውጭ ንግድ የሚቀርቡት የሐረር፣ የሲዳማና የይርጋ ጨፌ ቡናዎች ናቸው፡፡ የሰኔ ወር ከመገባደዱ በፊት የታቀደውን ለማሳካት ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የገለጹት ዳይሬክተሩ፣ ቡናን በማስተዋወቅና ሕገወጥ የቡና ንግድን በመከላከል የተደረገው ጥረትም ለውጭ የሚቀርበው ቡና እንዲጨምር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ከሦስት ወራት በፊት በኢትዮጵያ የተካሄደው ዓለም አቀፍ የቡና ጉባዔ የአገሪቱን ቡና በማስተዋወቅ ረገድ እገዛ ማድረጉንም አስታውሰዋል፡፡
ኢትዮጵያ ባለፉት 11 ወራት 174 ሺሕ ቶን ቡና ለውጭ ገበያ ማቅረቧን የጠቆሙት አቶ ጌታሁን፣ ለውጭ ገበያ የቀረበው የቡና መጠን በዕቅድ ከተያዘው 180 ሺሕ ቶን ቡና ጋር ሲነፃፀር አፈጻጸሙ 96 በመቶ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ይገኛል ተብሎ ከተጠበቀው 766 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ የተገኘው 620 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ሲሆን፣ አፈጻጸሙ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ውጤት ጋር ሲነፃፀር የ11 በመቶ ብልጫ እንዳለው አቶ ጌታሁን አስረድተዋል፡፡ ቡና ከኢትዮጵያ ከሚገዙ አገሮች መካከል ጀርመን፣ ሳዑዲ ዓረቢያና አሜሪካ ግንባር ቀደም አገሮች መሆናቸውንም አክለዋል፡፡
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አንደኛ በዓለም ደግሞ አምስተኛ ቡና አምራች አገር ስትሆን፣ ዓረቢካ ቡና በማምረት በዓለም ሦስተኛ አገር ነች፡፡