Sunday, September 24, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

​​​​​​​የኢሕአዴግ ቀጣይ የቤት ሥራዎች

የ2008 የበጀት ዓመት ሊጠናቀቅ ጥቂት ቀናት ይቀሩታል፡፡ የበጀት ዓመቱ መጠናቀቁን ተከትሎ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕረፍት ይወስዳል፡፡ በመሆኑም በዚህ የዕረፍት ወቅት የሕዝብ ተመራጮች ወደተመረጡበት አካባቢ ተመልሰው ከመረጣቸው ሕዝብ ጋር በመገናኘት የሕዝቡን ትርታ መስማት የሚችሉበት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡

ይህ የበጀት ዓመት ከሌሎች ዓመታት በተለየ ለአገሪቷም ሆነ ለሕዝብና ለመንግሥት ፈታኝ እንደነበረ ጥርጥር የለውም፡፡ ባለፉት ወራት በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተነሱት ግጭቶች፣ የመልካም አስተዳደር ችግር መንሰራፋት፣ የመንግሥት አካላት የአፈጻጸም ማነስ፣ በአገሪቷ የተከሰተው ድርቅና የጎርፍ አደጋ፣ እንዲሁም በቅርቡ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የተፈጠረው ግጭት ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ እነዚህን ችግሮች ለመፍታት የኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት ከፍተኛ እንቅስቃሴ አደርጋለሁ ቢልም፣ በአብዛኛዎቹ ላይ የታየው ውጤት ግን አመርቂ እንዳልሆነ ሕዝብም መንግሥትም ጠንቅቆ ያውቁታል፡፡ ይህም በመጪው የክረምት ወራት መንግሥት ከፍተኛ የሆነ የቤት ሥራ እንደሚጠብቀው ያሳያል፡፡

  1. የመልካም አስተዳደር ችግሮች

በበጀት ዓመቱ መባቻ አካባቢ የአገሪቱ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ለሕዝብ በቴሌቪዥን በተላለፈ ስብሰባ፣ የመልካም አስተዳደርን ችግር አንገብጋቢነት ነቅሶ በማውጣት ወደ ዘላቂ መፍትሔ ለመሄድ ቁርጠኝነት ያሳዩበት መድረክ ነበር፡፡ በወቅቱ በከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናቱ የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ የታየው ቁርጠኝነት፣ በሕዝቡ ዘንድ ትልቅ ተስፋን የፈነጠቀ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ሕዝቡ የሰነቀው ተስፋ ከመሬት ወርዶ ሊያየው አልቻለም፡፡

ሕዝብን ተስፋ እያስቆረጠ የመጣው ነገር በዋነኛነት አገልግሎት ሰጪ የመንግሥት ተቋማት በተለይ በገቢዎችና ጉምሩክ፣ በመሬት አስተዳደር፣ በፍትሕና በሌሎች የመንግሥት ተቋማት የግዴለሽነትና የማንአለብኝነት በሽታ አለመቀረፉ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ኢሕአዴግ ራሱ በተደጋጋሚ እንደሚያምነው ሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነት አሁንም ሕዝብ እያማረሩት ነው፡፡ ዜጐች መብታቸውን የሆነውን አገልግሎት ለማግኘት ወደ እነዚህ ተቋማት በሚሄዱበት ወቅት፣ ከትንሹ የመንግሥት ሠራተኛ እስከ ትልቁ ኃላፊ ድረስ ጉቦ መቀበልን እንደ ብቸኛ አማራጭ ማየታቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ ይህም ለሥርዓቱም ሆነ ለአገሪቱ ትልቅ አደጋ ነው፡፡ ይህን አንገብጋቢ ችግር መንግሥት በአፅንኦት ተመልክቶና እንደ ትልቅ የቤት ሥራ ወስዶ ሳይውል ሳያድር በአፋጣኝ መፍትሔ ሊያበጅለት ይገባል እንላለን፡፡   

  1. ከሕዝብ ጋር መታረቅ

በዚህ ዓመት በተለየ ሁኔታ በአገሪቱ ላይ ከፍተኛ ውጥረት ሰፍኖ ነበር፡፡ በበርካታ የኦሮሚያ አካባቢዎችና በአንዳንድ የአማራ ክልል አካባቢዎች እንዲሁም በጋምቤላ ክልል ግጭቶች ተከስተው ነበር፡፡ እነዚህም ግጭቶች አስከፊ ለሆነ ውጤት ዳርገዋል፡፡ በርካታ ዜጐችም ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን፣ በዜጐችም ላይ ከፍተኛ የሆነ የአካል ጉዳት ደርሷል፡፡ ከዚህም ባለፈ በሕዝብና በአገር ሀብት ላይ ከፍተኛ ውድመት ደርሷል፡፡

የእነዚህ ግጭቶች መከሰት አሳዛኝ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን ዋናው ጉዳይ ከዚህም በኋላ ተመሳሳይ ግጭቶች እንዳይነሱ ኢሕአዴግ የታችኛው የኅብረተሰብ ክፍል ድረስ ወርዶ ከሕዝብ ጋር እርቅ ማድረግ፣ በመቀጠልም የችግሮቹን ትክክለኛና ዋነኛ መንስዔዎች ነቅሶ አውጥቶ ዘላቂ የሆነ መፍትሔ ማበጀት አለበት እንላለን፡፡ ይህም ለኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት ሌላው ወሳኙ የቤት ሥራ ነው እንላለን፡፡

  1. የአፈጻጸም ብቃት

በዚህኛው የበጀት ዓመት ከታዩ ችግሮችና እየተባባሱ ከመጡት መካከል የአፈጻጸም ብቃት ማነስ ተጠቃሽ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል በቅርቡ ኦዲተር ጀነራል ለሕዝብ ተወካዮች ያቀረበው ሪፖርት፣ ከዚህ ቀደም የነበሩ ችግሮች ከመቀረፍ ይልቅ መባባሳቸውን የሚያመለክት ነበር፡፡ ከዚህም ባለፈ በዚሁ በጀት ዓመት በአገሪቱ ትልቅ ግምት ከሚሰጣቸው ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ የሆነው የስኳር ፋብሪካዎች ሲሆን፣ የስኳር ኮርፖሬሽን ኃላፊዎች ለፓርላማው ያቀረቡት ሪፖርት ግን ሕዝቡንም መንግሥትንም አንገት ያስደፋ ነበር፡፡

ኢሕአዴግ በእነዚህና በሌሎች ተመሳሳይ ችግሮች ላይ የሚታየውን የማስፈጸም ብቃት ማነስ ችላ እያለው ይገኛል፡፡ ኢሕአዴግ ለዘመናት ሲወቀስ ከነበረባቸው ችግሮች መካከል አንዱ የሆነው የፓርቲ ታማኝነትን ከብቃት ማስበለጡ ነው፡፡ ይህም አሁን እየተከሰቱ ላሉ የአፈጻጸም ችግሮች እንደ ዋነኛ ምክንያት ይጠቀሳል፡፡ በመሆኑም መንግሥት ይህ የአፈጻጸም ብቃት ማነስ ራሱ መንግሥትንም ሆነ አገርን ዋጋ እያስከፈለ መሆኑን ተገንዝቦ፣ በአፋጣኝ ብቃት ተኮር የሆነ አሠራር መዘርጋት አለበት፡፡ በመሆኑም የአፈጻጸም ብቃት ማነስ ሌላው የመንግሥት የቤት ሥራ ነው እንላለን፡፡

  1. ድርቅና ጐርፍ

በአገሪቱ የተከሰተው ድርቅ ሕዝብና መንግሥትን ሲፈታተን እንደነበር ይታወቃል፡፡ ከድርቁም ባሻገር በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች የደረሰው የጐርፍ አደጋም በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ ክፉኛ አገሪቱን ጐድቷታል፡፡ የተፈጥሮ አደጋዎች ሊደርሱ አይችሉም እያልን አይደለም፡፡ ነገር ግን በተፈጥሮ የሚከሰቱ አደጋዎች በሕዝብና በአገር ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዳያደርሱ፣ የቅድመ ዝግጅት ሥራ ሊሠራ ይገባል፡፡

እንደ በፊት ዘመናት አገሪቱ እንደዚህ አደጋዎች ሲከሰቱ የለጋሽ አገሮችን እጅ እንድታይ ተገዳለች፡፡ ይህ እንደ መፍትሔ መታየት የለበትም እንላለን፡፡ እንዲያውም መሆን ያለበት የራስን ችግር በራስ መፍታት ነው፡፡ ኢሕአዴግ በተደጋጋሚ ድህነትና ኋላቀርነት ዋነኞቹ ጠላቶቼ ናቸው እንደሚለው፣ ለእነዚህ ችግሮች ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ የኢትዮጵያን ገበሬዎች ከድህነት መንጋጋና ከኋላቀርነት እስራት ማላቀቅ አለበት፡፡ ተመሳሳይ ችግሮችም እንዳይከሰቱ መንግሥት የቅድመ ዝግጅት ሥራውን በሚገባ መሥራት አለበት፡፡ ይህም ሌላኛው የኢሕአዴግ ወሳኝ የቤት ሥራ ነው እንላለን፡፡

  1. የኢትዮ ኤርትራ ግጭት

በቅርቡ የተከሰተው የኢትዮጵያና የኤርትራ ግጭት ሕዝብና ዓለም አቀፉን ማኅበረሰብ ግራ ከማጋባቱ ባሻገር ሥጋት ውስጥ የጨመረ ነበር፡፡ የአንድ አገር ዕድገት እየጨመረና እየተጠናከረ የሚሄደው ሰላምና መረጋጋት ሲኖር ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ዕድገት እያስመዘገበች ቢሆንም፣ በእንደዚህ ዓይነት ግጭት ውስጥ መግባቷ እየተመዘገበ ያለውን ዕድገት ወደኋላ የሚጐትት ነው፡፡ ምክንያቱም እንደዚህ ዓይነቱ አካሄድ አገሪቷን ለከፍተኛ ኪሳራ ያጋልጣታል፡፡ ለዚህ ችግር መፍትሔው አንድና አንድ ነው፤ እሱም ሰላም መፍጠር ነው፡፡ ለዚህም ደግሞ የሁለቱ አገሮች መንግሥታት ብቸኛው መፍትሔ ሰላም መሆኑን ተረድተው፣ ችግሮቻቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት አለባቸው እንላለን፡፡ ይህም ሌላኛው የመንግሥት የቤት ሥራ ነው፡፡

ከላይ የተጠቀሱትን አምስት ነጥቦች እንደ ዋነኛ ማሳያ ጠቀስናቸው እንጂ የመንግሥት የቤት ሥራዎች እነዚህ ብቻ ናቸው እያልን አይደለም፡፡ ሕዝብ መንግሥትን የመረጠው መብቶቼን ያስከብርልኛል እንዲሁም ያገለግለኛል ብሎ ስለሆነ፣ ኢሕአዴግም ይህን ተገንዝቦ ከሕዝብ ጋር በቅርበት በመሥራት ለእነዚህና ለሌሎች ችግሮች በአፋጣኝ መፍትሔ ማበጀት አለበት እንላለን፡፡ በመሆኑም መንግሥት ከፊቱ ያሉትን የቤት ሥራዎች በብቃት ይወጣ እንላለን፡፡

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

በቀይ ባህር ፖለቲካ ላይ በመከረው የመጀመሪያ ጉባዔ ለዲፕሎማቲክና ለትብብር አማራጮች ትኩረት እንዲሰጥ ጥሪ ቀረበ

ሰሞኑን በአዲስ አበባ ለመጀመርያ ጊዜ በቀይ ባህር ቀጣና የፀጥታ...

የቤት ባለንብረቶች የሚከፍሉትን ዓመታዊ የንብረት ታክስ የሚተምን ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጀ

በአዋጁ መሥፈርት መሠረት የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የንብረት ታክስ መጠን...

እንደ ንብረት ታክስ ያሉ ወጪን የሚያስከትሉ አዋጆች ከማኅበረሰብ ጋር ምክክርን ይሻሉ!

የመንግሥትን ገቢ በማሳደግ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳላቸው የሚታመኑት የተጨማሪ እሴት...

ለዓለምም ለኢትዮጵያም ሰላም እንታገል

በበቀለ ሹሜ ያለፉት ሁለት የዓለም ጦርነቶች በአያሌው የኃያል ነን ባይ...

የመጀመርያ ምዕራፉ የተጠናቀቀው አዲስ አበባ ስታዲየም የሳር ተከላው እንደገና ሊከናወን መሆኑ ተሰማ

እስካሁን የሳር ተከላውን ጨምሮ 43 ሚሊዮን ብር ወጪ ተደርጓል ዕድሳቱ...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

በአገር ጉዳይ የሚያስቆጩ ነገሮች እየበዙ ነው!

በአሁኑም ሆነ በመጪው ትውልድ ዕጣ ፈንታ ላይ እየደረሱ ያሉ ጥፋቶች በፍጥነት ካልታረሙ፣ የአገር ህልውና እጅግ አደገኛ ቅርቃር ውስጥ ይገባና መውጫው ከሚታሰበው በላይ ከባድ መሆኑ...

የትምህርት ጥራት የሚረጋገጠው የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ሲወገድ ነው!

ወጣቶቻችን የክረምቱን ወቅት በእረፍት፣ በማጠናከሪያ ትምህርት፣ በበጎ ፈቃድ ሰብዓዊ አገልግሎትና በልዩ ልዩ ክንውኖች አሳልፈው ወደ ትምህርት ገበታቸው እየተመለሱ ነው፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ሰኞ መስከረም...

ዘመኑን የሚመጥን ሐሳብና ተግባር ላይ ይተኮር!

ኢትዮጵያ በአዲሱ ዓመት ዋዜማ ሁለት ታላላቅ ክስተቶች ተስተናግደውባት ነበር፡፡ አንደኛው የታላቁ ህዳሴ ግድብ አራተኛ የውኃ ሙሌት ሲሆን፣ ሁለተኛው ኢትዮ ቴሌኮም በአዲስ አበባ ከተማ ያስጀመረው...