‹‹ጳዝዮን የከበረ ማዕድን ሲሆን እንደ ዕንቁና ወርቅ ያንጸባርቃል፡፡ ላወቀው እንጂ ክቡርነቱ ላላወቀው የትብያ ያህል ነው፡፡ ተራ አልባሌ፡፡ ‘ሰው’ነት ጳዝዮን ነው፡፡ ጊዜና አካባቢ ከእነ ሙላቷ ጳዝዮን ናቸው፡፡ ሃይማኖት፣ ታሪክ፣ ባህልና መሰል አኩሪ እሴቶች ጳዝዮኖች ናቸው፡፡ ለራስህ በምትሰጠው ሚዛን የምትገመት አንተም ጳዝዮን ነህ፡፡ እነዚህ ሁሉ አዋቂ አክባሪና ተጠቃሚ ይሻሉ፡፡ ካላገኙ ተራ ነገር ሆነው ያልፋሉ፡፡›› ይላል መሰንበቻውን ለኅትመት የበቃው የመክት ፋንቱ ‹‹ጳዝዮን›› መጽሐፍ፡፡
በረዥም ልቦለድ ውስጥ በጳዝዮን ሊመስሉ የሚችሉ መልካም ባህሪያት፣ ህልም፣ ዕውቀትና ዕምቅ ክህሎት ትርጉም አግኝተው ለሌላው ተርፈው ሲገኙ፣ ትርጉም ጊዜና ቦታ ተነፍጓቸው ቁጭት ወይም የእግር እሳት ሆነው ተስተውለዋል ይላል ደራሲው፡፡
በመልካም ማንነታቸው የሚወደዱ ገጸ ባህርያቱ ቅርብ ሆነው የዕውነት በዕውነት ሊዋደጇቸው የሚናፈቁ ናቸው፡፡ እንደ አባት ይከበራሉ፣ እንደ ወንድም ያስመካሉ፣ እንደ እህት ይናፍቃሉ፣ እንደ ጓደኛ ለምክርና ጨዋታ ይፈልጋሉ፡፡ የሚጠቅሙ ጳዝዮኖች ይሆናሉ፡፡ ከርሰ ምድር ቆፍረው ትብያ አራግፈው አንጸባራቂ ጳዝዮን ያገኙ ዕድለኛ ያደርጋሉ፡፡ አካባቢያቸውን አክብረው የከበሩ ጳዝዮኖች የሚተዋወቁበት ሲሆን ራስን አስመርምረው ከእነሱ እንደ አንዱ ለመሆን የሚያስመኙ፣ የሚያወስኑም፣ ለጳዝዮንነት ራስን የሚያሳጩ ናቸው፡፡
ደራሲው በመግቢያው እንዳመሠጠረው፣ በአንፃሩ ጳዝዮን ትርጉም አጥቶ እንደ ትብያ መረጋገጫ ሲሆን ያስቆጫል፡፡ ያንገበግባል፡፡ ያበሳጫል፡፡ ለጥቅም እንጂ ለጥፋት የተፈጠረ ምንም የለምና ያስቆጨ፣ ያንገበገበ፣ ያበሳጨ ቆም ብሎ ነገን ከእነ በረከቷ በማመን የጳዝዮን አካል በመሆን ክብርና ሞገስ ያጎናጽፋል፡፡
በዮናስ መጽሐፍ መደብር አከፋፋይነት የቀረበው ባለ 264 ገጽ ጳዝዮን በብር 81.40 ይሸጣል፡፡