በሱራፌል ተሾመ
በአገራችን ኢትዮጵያ፣ በተለይም የፌዴራል ሥርዓቱ በተግባር ላይ ከዋለ በኋላ ባሉ ዓመታት፣ አልፎ አልፎ የሚከሰቱ አንዳንድ ጊዜ ሕዝባዊነት ያላቸው፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ በመንግሥት መሥራቹ ፓርቲ ውስጣዊ ግጭት ምክንያት የተነሱ ፖለቲካዊ አለመረጋጋቶች በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች ይስተዋላሉ፡፡ በ1960ዎቹ አብቦ ቀጥሎም በተሰነዘረበት ያልተመጣጠነ ዕርምጃ ከስሞ የቆየው የሲቪል ፖለቲካ እንቅስቃሴም፣ ከወታደራዊው መንግሥት መውደቅ በኋላ እንደገና ሕይወት ዘርቶ በአገሪቱ ፖለቲካ ላይ የራሱን ሚና እየተጫወተ አሁን ያለንበት ደረጃ ደርሰናል፡፡ የምንመራበት የፌዴራል ሥርዓት በዋናነት አረጋግጠዋለሁ የሚለው የብሔር ብሔረሰቦች የጋራ ተጠቃሚነትና እኩልነት ሲሆን፣ ይህንንም ለማስፈጸም መሠረቱን ብሔር ያደረገ የክልሎች አወቃቀር ተግብሯል፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ በተደጋጋሚ የሚነሱ ብሔር ተኮር ግጭቶችን ከማስተናገዳችን አንፃር ፌዴራሊዝማችን ግቡን ለመምታት የሚያስችል ርዕዮተ ዓለማዊና ተግባራዊ ብቃት አለው ወይ የሚል ጥያቄ ከሽግግር መንግሥት አንስቶ ሲሰማ ቆይቷል፡፡ እ.ኤ.አ. ከ2012 ገደማ ወዲህ የተነሱና ዜጎችን አደባባይ ያስወጡ ጥያቄዎችና ግጭቶች ደግሞ ከወትሮው በተለየ መልኩ ረዘም ላለ ጊዜ ከመቆየታቸው ባሻገር በአንድ አካባቢ መወሰን አቁመዋል፡፡ የአገራችን ወቅታዊ ሁኔታም ከመሻሻልና ወደ ብሔራዊ መግባባት ከመድረስ ይልቅ ቀድመው መመለስ በነበረባቸው የማንነትና የድንበር ውዝግቦች ተተብትቧል፡፡
እንግዲህ አሁን ያለንበት የፖለቲካ መድረክ የእነዚህ አለመረጋጋቶች ጥላ ያጠላበት መሆኑን የተረዱ ኃይሎች በጋራና በተናጠል የመፍትሔ ሐሳብ ያፈላልጋሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ መንግሥትና መንግሥትን የመሠረቱ ፓርቲዎች፣ በአገር ውስጥና በውጭ የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚ ድርጅቶች፣ ሰፋ ባለ ሁኔታ ደግሞ ባልተደራጀ መንገድና ወቅቱ በፈቀደው ሁኔታ ድምፁን የሚያሰማውን ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊን እንደ ፖለቲካ ኃይሎች ወስደን፣ የአገሪቱን መፃኢ ዕድል ለመወሰን የሚጠቅሙ የመፍትሔ አቅጣጫዎችን መነጋገር ይኖርብናል፡፡
በዚህ ጽሑፍም ለመዳሰስ የሞክርኩት ከደርግ ውድቀት ጀምሮ ተግባራዊ ያደረግነው ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም ከምን ተነስቶ አሁን ያለበት ደረጃ ላይ ሊደርስ ቻለ? በተለይም ታሪካዊ አንድምታን ባገናዘበ መልኩ ብሔርን መሠረት ያደረገው ፌዴራሊዝማችን ምን አቋም ላይ ይገኛል የሚሉትን ጥያቄዎች ነው፡፡
የጽሑፉ አወቃቀር ይህን ይመስላል፡፡ በመጀመሪያ ክፍል ከ1960ዎቹ እስከ 1983 ዓ.ም. (አሀዳዊ መንግሥት) ቀጥሎም ከ1983 ዓ.ም. እስካሁን ያለውን (ፌዴራል መንግሥት) የቅርብ ጊዜ የፖለቲካ ታሪካችንን በማንሳት፣ ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም እንዴት የኢትዮጵያን የፖለቲካ መድረክ እንደተቀላቀለ እዳስሳለሁ፡፡ በሁለተኛ ክፍል የምንከተለው ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም እስካሁን በምን ዓይነት መንገዶች እንደተጓዘ ለማሳየት መልካም ገጽታዎችን፣ ስህተቶችን እያረመ የመጣበትን መንገድ፣ የፈታቸውና ያልፈታቸው ችግሮችን በመጥቀስ የማንነት ጥያቄን በምን ዓይነት ሁኔታ እንዳስተናገደ ለማሳየት እሞክራለሁ፡፡ በሦስተኛና በአራተኛ ክፍል አሁን ያለንበት የፖለቲካ ትኩሳት ላይ እንዴት ልንደርስ ቻልን? ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝማችን ላይ እርምት ማድረግ ይኖርብናል ወይ? የሚሉትን አንኳር ሐሳቦች አቀርባለሁ፡፡ ጽሑፌን የምጨርሰው የአገር ጉዳይ ይመለከተኛል እንደሚል ማንኛውም ዜጋ ያነሳሁዋቸውን የመወያያ ነጥቦች አብላልቼ ማጠቃለያ የሚሆኑ ግላዊ አስተያየቶችን በመሰንዘር ይሆናል፡፡
ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም እንዴት ልንገነባ ቻልን?
የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዙፋን ኤርትራን ጨምሮ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች በተወረወሩ አመፆች መናጋት ሲጀምር፣ በአገራችን ውስጥ ከዚህ በፊት ትልቅ ቦታ ያልነበራቸው መፈክሮች በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ተማሪዎችና በተለያዩ የሕይወት መስክ ላይ ያሉ የተገዢው መደብ አባላትን አደባባይ ማዋል ጀመሩ፡፡ የአመፅ መንስዔዎቹ እንደተነሱበት ቦታ የተለያየ ይዘት ቢኖራቸውም፣ በግንባር ቀደምትነት የሚመደቡት “የኤርትራ ጉዳይ” እየተባለ ይጠራ የነበረው የመገንጠል ጥያቄ፣ “መሬት ላራሹ ለላብ አፍሳሹ” በሚለው መፈክር የሚታወሰው የመሬት ባለቤትነት ጥያቄና የብሔር ብሔረሰቦች የእኩልነትና የራስን በራስ የማስተዳደር መብት ነበሩ፡፡ የዘውዳዊው ሥርዓት እነዚህን ችግሮች የመፍታት አቅምም ሆነ መሠረታዊ ፍላጎት ባለማሳየቱ፣ በአውሮፓውያን የትግል ሥልት ራሳቸውን አሠልጥነው ካደራጁ ወጣት ምሁራንና በደረሰበት የመልካም አስተዳደር ዕጦት የመፍትሔ ያለህ ሲል የቆየው ወታደር ከወከላቸው መኮንኖች ጋር የአገሪቱን ዕጣ ፈንታ ለመወሰን ግብግብ ጀመረ፡፡
ይህን የታሪክ አጋጣሚ ሰላማዊ በሆነ ለውጥ ወይም የሥልጣን ሽግግር መለወጥ ያልቻለው የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት፣ በአጭር ጊዜ በወታደራዊው ደርግ ሥልጣኑን ተቀምቶ የታሪክ ተመልካች ለመሆን በቃ፡፡ የደርግ መንግሥት የተማሪዎችንና የመላው ኢትዮጵያውያን የትግል አጀንዳ የነበረውን የመሬት ባለቤትነት ጥያቄን በወቅቱ የአብዛኛውን ሕዝብ ቀልብ ተቆጣጥሮ ከነበረው ርዕዮተ ዓለማዊ ፍልስፍና አንድ ገጽ በመጠቀም፣ የገጠር መሬቶችንና የከተማ ቤቶችን ወርሶ ለዜጎች አከፋፈለ፡፡ ይህን ዕርምጃ በበጎ ዓይን ተመልክቶ ነገር ግን ያልተመለሱ ጥያቄዎችንና የሥልጣን ምንጭ ሕዝባዊ ፈቃድ እንጂ ወታደራዊ ኃይል መሆን የለበትም በሚል የኢትዮጵያ ሲቪል ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በህቡዕና በአደባባይ ለጥቂት ጊዜ ቢቀጥልም፣ በአሰቃቂ ሁኔታ ለመክሰም ተዳርጓል፡፡ ከደርግ አደን የተረፉና ቀድሞውንም ተዘጋጅተው ወደ ተራዘመ የትጥቅ ትግል የገቡ ኃይሎች ትግሉን በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ቢያፋፍሙትም፣ የሲቪል የፖለቲካ እንቅስቃሴ ግን ለጊዜውም ቢሆን ተዳፈነ፡፡
የደርግ መንግሥት በአገሪቷ ውስጥ የነበረውን የፊውዳል ሥርዓት በጣጥሶ የአብዮታዊነት መስመርን ቢከተልም፣ አሀዳዊ ማንነት ሳይቀር የማዕከላዊ መንግሥትነት ሚናን መጫወት ጀመረ፡፡ የኤርትራ ጉዳይና የብሔር ብሔረሰቦች የራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ ደርግ በዘረጋው አስተዳደራዊ መዋቅሮችና የፖለቲካ አቅጣጫዎች በበቂ ሁኔታ ሊመለሱ ባለመቻላቸው፣ ከዚህም በተጨማሪ በሰሜናዊው የአገራችን ክፍል የተፋፋመው የትጥቅ ትግል ከብዙ ኢትዮጵያውያን ደም መፋሰስ በኋላ ለፍሬ በቅቶ ወታደራዊው መንግሥትም በዋነኛነት አስከብረዋለሁ ያለውን የኢትዮጵያን ዳር ድንበር ማስከበር እንኳን ሳይችል የፖለቲካውን መድረክ አስረከበ፡፡ በዚህ የፖለቲካ ምዕራፍ ውስጥ በሁለቱም አሀዳዊ መንግሥታት (ንጉሣዊና ወታደራዊ) አስተዳደሮች በአብዛኛው ተዘንግቶ የቆየው የብሔር ብሔረሰቦች የራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄና በተለይም በአፍ መፍቻ ቋንቋ የመማርና የመሥራት መብት፣ ትጥቅ ትግል ለገቡ የፖለቲካ ኃይሎች ግን ዋነኛ የመታገያ አጀንዳ ነበር፡፡ ሁለቱም አሀዳዊ መንግሥታት ተመሳሳይ አስተዳደራዊ አውራጃዎችን መሠረት አድርገው ሥልጣንን በማዕከላዊነት ይዘው በመቀጠላቸው የዜጎች የራስን በራስ የማስተዳደርን ጥያቄ በአጥጋቢ ሁኔታ ለመመለስ ሳይችሉ አልፈዋል ማለት እንችላለን፡፡
በደርግ መደምሰስ ማግሥት ታይቶ በማይታወቅ መልኩ አብዛኛውን የፖለቲካ ኃይሎች ያሳተፉ የምክክር መድረኮች ተዘጋጅተውና በአገሪቷ መፃኢ ዕድል ላይ ውይይት ተደርጎ፣ የብሔር ብሔረሰቦች የጋራ ተጠቃሚነትና እኩልነት ያረጋግጣል የተባለ ሕገ መንግሥትና ያንንም የሚተገብር ብሔርን መሠረት ያደረገ የፌዴራላዊ ሥርዓት ሲገነባ፣ የኤርትራ ጉዳይ ደግሞ በኢትዮጵያውያን መካከል የጋራ መግባባት ሳይደረስበት መፍትሔ ተሰጥቶታል፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱም ሆነ የሥርዓቱ መሠረት የሆነው ሕገ መንግሥት በአገሪቱ ውስጥ አንፃራዊ ሰላም በማስፈን ለረጅም ጊዜ የቆየ ኢኮኖሚያዊ መነቃቃት ቢፈጥሩም፣ በመግቢያዬ ላይ በጠቀስኳቸው የብሔር ግጭቶችና የማንነት ቀውሶች ምክንያት ከመነሻው ጀምሮ ከወቀሳ አላመለጡም፡፡
የምንከተለው የፌዴራል ሥርዓት እንደ ኢትዮጵያ ባሉ የተለያየ ማኅበረሰባዊ ማንነት ባላቸው አገሮች ረዘም ላለ ጊዜ ጥቅም ላይ ሲውል ቆይቷል፡፡ የፌዴራል ሥርዓት የሚዋቀረው በውስጡ በሚገኙ ራሳቸውን በራሳቸው ማስተዳደር በሚችሉ አካባቢያዊ መንግሥታትና ሥልጣኑ በተገደበ ማዕከላዊ መንግሥት ነው፡፡ አካባቢያዊ መንግሥታት ሦስቱንም የመንግሥት አውታሮች በክልሉ ነዋሪዎች በማዋቀር ክልላቸውን ሲያስተዳድሩ፣ የፌዴራል መንግሥቱ ደግሞ የሁሉም ክልሎች አንፃራዊ ስብጥርን በማገናዘብ መዋቅሩን በመላው አገሪቱ ይዘረጋል፡፡ የአገራችን ፌዴራል ሥርዓት ከዘጠኝ ክልል መንግሥታት፣ ከሁለት የከተማ አስተዳደሮችና ፓርላሜንታዊ ሥርዓት ከሚከተል ፌዴራል መንግሥት የተዋቀረ ሲሆን፣ ክልሎች ደግሞ በዋናነት ብሔርን መሠረት አድርገው ተካልለዋል፡፡ ክልሎች በዋናነት ብሔርን መሠረት አድርገው ይዋቀሩ እንጂ፣ በውስጣቸው ከአንድ ብሔረሰብ በላይ መያዛቸው አልቀረም፡፡ ይህም የሆነው በአገራችን የሚገኙ ብሔርና ብሔረሰቦች በሕዝብ ብዛትም ሆነ በሚይዙት የቆዳ ስፋት ተመጣጣኝ አቋም ላይ የሚገኙ ባለመሆናቸውና በተለይ እጅግ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ብሔሮች ክልላዊ መንግሥት የመመሥረት አቅም ስለሌላቸው፣ ከሌሎች መሰል ብሔሮች ጋር ተቀናጅተው አቅማቸውን እንዲያጎለብቱ ይመስለኛል፡፡ የምንከተለው የክልሎች አወቃቀር ብሔርን መሠረት ያደረገ ይሁን እንጂ፣ አንድ ብሔር አንድ ክልል የሚል መፍትሔ አይደለም፡፡ ነገር ግን በአገሪቱ ውስጥ የተቋቋሙት ክልሎች ለምን በአሁኑ ሁኔታ እንደተካለሉ የሚያስረዳ አጥጋቢ መልስ ሲሰጥ አይታይም፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተወላጅ ያላቸው ብሔረሰቦች በክልልነት የመደራጀት ዕድል አግኝተው በራሳቸው ቋንቋ የመማርና የመሥራት መብታቸው የተከበረበት ሁኔታ ሲኖር፣ በሌሎች ቦታ ደግሞ በሚሊዮን የሚቆጠር ተወላጅ ያላቸው ብሔረሰቦች በክልል ደረጃ አስተዳደራቸውን የማዋቀር ዕድል አላገኙም፡፡ ሕገ መንግሥቱ አንድ ብሔር በክልልነት ራሱን ለማወጅ የሚያስችለውን ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀምጦ የሚፈቅድ ሲሆን፣ በተግባር ግን ሥራ ላይ የዋለበት አጋጣሚ እስካሁን አልተከሰተም፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የክልሎች አወቃቀር በውስጡ ለአደረጃጀት ጥያቄዎች የተጋለጠ በመሆኑ ብሔሮች የሚያነሱት የወረዳ፣ የልዩ ወረዳ፣ የዞንና የልዩ ዞን ይገባኛል ጥያቄ በተደጋጋሚ ይሰማል፡፡
የራሳችንን ዕድል በራሳችን ለመወሰን ቆርጠን የተነሳነው እኛ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በሚል ጭብጥ የሚጀምረው የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግሥት ራስን በራስ የማስተዳደር ነፃነትን የሚፈቅድ ቢሆንም፣ ያንን ለመተግበር የመረጠው የክልሎች አወቃቀር ግን ከላይ ለጠቀስኳቸው የብሔረሰብ ጥያቄዎች መንስዔ ሆኗል፡፡ ሕገ መንግሥቱ እንዲህ ዓይነት የማንነት ጥያቄዎችን የሚያስተናግድበት የራሱ አካሄዶች ቢኖሩትም፣ ችግሮቹ በዘላቂነት የሚፈቱት ብሔራዊ መግባባት የተደረሰበት የክልሎች ማንነት አወሳሰን ሲኖር ነው የሚል አመለካከት አለኝ፡፡ ይህንን ርዕስ በአራተኛው የጽሑፌ ክፍል ለመዳሰስ የሞከርኩ ሲሆን፣ በሚቀጥለው ክፍል ደግሞ የምንከተለው ብሔርን መሠረት ያደረገ የክልሎች አወቃቀርን ወደ ፖለቲካው መድረክ ያስተዋወቀው የኢትዮጵያ ፌዴራሊዝም እንዴትና በምን ሁኔታ አሁን ወዳለንበት አቋም እንደ ደረሰ አቀርባለሁ፡፡
ብሔርን መሠረት ያደረው ፌዴራሊዝም እስካሁን እንዴት ሊቀጥል ቻለ?
የፌዴራል ሥርዓቱ ይዞ የመጣው በአፍ መፍቻ ቋንቋ የመማርና የመሥራት መብት፣ ክልላዊና አካባቢያዊ መንግሥት የመዘርጋት ዕድል በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍል በመልካም ገጽታነት እንደተወሰደ በሰፊው ይታመናል፡፡ ይህን መብትና ዕድልንም በመጠቀም ክልሎችና በውስጣቸው የሚኖረው ሕዝብ በርካታ አዎንታዊ ዕርምጃዎችን ተራምደዋል ብንል ድፍረት አይሆንም፡፡ በአገራችን የሚገኙ ቋንቋዎች በንግግርም ይሁን በጽሕፈት መስክ ዕድገት ማሳየታቸው፣ ያልተማከለ አካባቢያዊ አስተዳደሮች በመፈጠራቸው ምክንያት የሚስተዋለው የብሔር ብሔረሰቦች ራሳቸውን በራስ የማስተዳደር ልምድ ማካበት፣ ከዚያም በተረፈ በተግባር ላለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት በአገሪቱ ውስጥ አንፃራዊ ሰላም በማስፈን ለረጅም ጊዜ የቆየ ኢኮኖሚያዊ መነቃቃት መፍጠሩ፣ የፌዴራል ሥርዓቱ የሚታወስባቸው መልካም ገጽታዎች ሆነው ይቆጠራሉ፡፡
በአገራችን የሚገኙ ዘጠኝ ክልሎች የተቋቋሙት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 47 መሠረት ሲሆን፣ ማናቸውም ኢትዮጵያዊ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ሆነው ለመቋቋም የሚያስችላቸው መብትና የአሠራር ሒደትም በዚሁ አንቀጽ ተቀምጧል፡፡ ይሁንና የፌዴራል ሥርዓታችን ወጥ የሆነ የክልሎች ማንነት አወሳሰን አይታይበትም፡፡ አስቀድሞ በተጠቀሰው አንቀጽ ሥር የተዘረዘሩት ክልሎች በምን መሥፈርት የክልልነት ማዕረግ እንደተጎናፀፉ፣ ሌሎች ከፍተኛ የተወላጅ ቁጥር ያላቸው ብሔርና ብሔረሰቦች ደግሞ በአንድ ላይ ተዋህደው አንድ ክልል እንዲመሠርቱ እንደተገደዱ የሚተነትን ወጥ መሥፈርት ተቀምጧል ለማለት አያስደፍርም፡፡ ይህ በመሆኑም በአንዳንድ አካባቢዎች በመቶ ሺሕና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ተወላጅና ተናጋሪ ያላቸው ብሔረሰቦችና ቋንቋዎች በመማር ማስተማሩ ሒደትና በክልላዊ መንግሥት የሥራ ቋንቋነት የማገልገል ዕድል በማግኘታቸውም፣ ቋንቋዎቹም ሆነ ተናጋሪዋቻቸው ዘርፈ ብዙ ጥቅሞችን ሲጎናፀፉ ሌሎች ተመጣጣኝ የተወላጅ ቁጥር ያላቸው ብሔረሰቦችና ያንኑ ያህል ተናጋሪ ያላቸው ቋንቋዎች ግን ከዚህ ጥቅም መቋደስ ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ ይህ በመሆኑም አልፎ አልፎ የሚገነፍሉ በአብዛኛው ግን ተዳፍነው የሚቆዩ የክልልነት ይገባኛል ጥያቄዎች ከየአቅጣጫው ብቅ ማለታቸው አልቀረም፡፡
ከክልል እስከ ወረዳና ቀበሌ የሚዘልቀው የአስተዳደር ይገባኛል ጥያቄና ውዝግብ የመንግሥት መዋቀር ጥያቄ ብቻ ሳይሆን፣ ተያይዞ ከሚነሳ የማንነት ጥያቄ ጋር ጎን ለጎን የሚሄድ የሕዝቦች እንቅስቃሴ መሆኑን ማወቅ ግድ ይለናል፡፡ ከዚህ አልፎም በክልል ድንበር አካባቢ የሚገኙ አስተዳደራዊ መዋቅሮችና ሕዝቦች በየትኛው ክልል ይጠቃለሉ የሚለው ጉዳይም፣ በክልሎች መካከል ያልተቋጩና ውስብስብ የማንነት ንትርክ ከመፍጠራቸው ባሻገር በየጊዜው ለዜጎች ሕይወት ማለፍና መፈናቀል ምክንያት ሆነዋል፡፡
የሃያ ስድስት ዓመት ዕድሜ ያለው የአገራችን ፌዴራሊዝም በክልሎች አወሳሰን ላይ ምንም ዓይነት የማሻሻያ ዕርምጃ ሳይወስድ የወረዳ፣ የልዩ ወረዳ፣ የዞንና የልዩ ዞን ጥያቄዎች ላይ ብቻ መጠነኛ ማስተካከያዎችን እያደረገ እስካሁን ቀጥሏል፡፡ የክልልነት ይገባኛል ጥያቄዎች እንዳሉ ቢታወቅም፣ ከሕገ መንግሥቱ መፅደቅ አንስቶ የነበረው የክልሎች ቁጥር አልተቀየረም፡፡
በዚህ ሁኔታ ነው እንግዲህ ብሔርን መሠረት ያደረገው ፌዴራሊዝማችን 20ኛውን ተሻግሮ ወደ 21ኛ ክፍለ ዘመን ከመድረስ ባሻገር አሥርት ዓመታት መቁጠር የጀመረው፡፡ ከላይ ለማስቀመጥ እንደተሞከረው የኢትዮጵያ ፌዴራሊዝም የስኬትና የግድፈት ፉርጎዎችን አጣምሮ በአንድ ላይ በመያዝ የሚምዘገዘግ ባቡር ይመስላል፡፡ የስኬት ፉርጎዎች ለባቡሩ ፍጥነትና ምቾት አስፈላጊ በመሆናቸው ማብዛትና ይዘን መቆየት እንደሚኖርብን ሁሉ የግድፈት ፉርጎዎችን ቢቻል መጠገን፣ የማይቻል ሲሆን ደግሞ ለተሳፋሪውና ለባቡሩ ደኅንነት ሲባል ተወግደው መተካት ይኖርባቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አስተዳደርና የሲቪል ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ
ስለአገራችን ፌዴራላዊ አስተዳደር ሥርዓት ስናነሳ ከጥንስሱ አንስቶ እስካሁን ድረስ አብሮት የዘለቀውን የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት፣ በዚህ ሥርዓትም ብቸኛ የሥልጣን ተቆናጣጭ መሆን የቻለውን የገዥ ፓርቲዎች ስብስብን ማንሳት ግድ ይላል፡፡ ይህ ስብስብ የዘጠኙም ክልላት ምክር ቤቶችንና ክልላዊ አስተዳደሮችን ሙሉ በሙሉ በተቆጣጠሩ ዘጠኝ ፓርቲዎች የተዋቀረ ሲሆን፣ አስኳሉ ደግሞ የፌዴራል መንግሥት ከፍተኛ የሥልጣን ምንጭ የሆነውን የተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ ድምፅ በጋራ የያዙ አራት ፓርቲዎች ያቋቋሙት ግንባር ነው፡፡ ከግንባሩ ውጭ ያሉ የገዥ ፓርቲ ስብስብ አባላት በተለምዶ አጋሮች በሚል ስያሜ ሲጠሩ፣ ከክልላዊ መንግሥት ባሻገር በተወሰነ ደረጃ የፌዴራል መንግሥት ሥልጣን ሲካፈሉ ይስተዋላል፡፡ በአጭሩ ሪፐብሊካችን ውስጥ በየእርከኑ ያሉ ሕግ አውጪና ሕግ አስፈጻሚ አካላት ሙሉ በሙሉ በግንባሩና አጋሮቹ የበላይነት የተዋቀረ እንደሆነ እናያለን፡፡
የገዥ ፓርቲዎች ስብስብ ልክ እንደ ፌዴራል ሥርዓታችን ሁሉ በዋነኛነት ብሔርን መሠረት ያደረገ መዋቅር መርጧል፡፡ ይህም በመሆኑ ከፌዴራል ሥርዓቱ በቀጥታ የሚወርሰው ወጥነት የጎደለው መርህ ይኖራል ማለት ነው፡፡ በክልል አወቃቀር ላይ የታየው ወጥ ያልሆነ መርህ በገዥ ፓርቲው ስብስብም በግልጽ ይስተዋላል፡፡ በአንዳንድ አካባቢ ከፍተኛ የተወላጅ ቁጥር ያላቸው ብሔሮች በራሳቸው ተደራጅተው የራሳቸውን ፓርቲ መሥርተው የፖለቲካውን ሜዳ ሲቀላቀሉ፣ ሌሎች ተመሳሳይ ወይም አብላጫ የተወላጅ ቁጥር ያላቸው ብሔሮች ይህን ዕድል በገዥ ፓርቲ በኩል ሳያገኙ ቀርተዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከግንባሩ ጋር በአጋርነት የተሠለፉ ድርጅቶች ምንም ያህል ታማኝና የዓላማ አንድነት ቢኖራቸውም፣ ከአጋርነት አልፈው አስኳል መሆን ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ ወደ አስኳልነት የሚቀይራቸውም አሠራር እስካሁን አልተቀረፀም፡፡
ጥንታዊ የሕዝቦች ትስስርና ፍልሰትን ባስተናገደችው አገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖሩ ብሔር ብሔረሰብ ተወላጆች፣ በተለያየ የታሪክና የሕይወት አጋጣሚዎች ምክንያት ወደ ተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በማቅናት ኑሯቸውን መሥርተው መኖር ከጀመሩ ትውልዶች ተቆጥረዋል፡፡ የሕዝቦች ከቦታ ቦታ የመዘዋወርና ኑሮ የመመሥረት መብት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 31 መሠረት ጥበቃ የሚደረግለት በመሆኑ፣ በዘመናዊቷ ኢትዮጵያም አያሌ ዜጎች ወደ ተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በመንቀሳቀስ ሕይወታቸውን መሥርተው ይገኛሉ፡፡ በዚህ ምክንያት በዘጠኙም ክልሎች ውስጥ የክልሉ ገዥ ፓርቲ የማይወክላቸው ኢትዮጵያውያን በብዛት ከመገኘታቸው በላይ፣ በክልላቸውና በፌዴራል መንግሥት ውስጥ ፋይዳ ባለው ደረጃ ድምፃቸውን የማሰማት መብታቸው ትልቅ እክል አጋጥሞታል፡፡
ሕዝቦች ከቦታ ቦታ በመንቀሳቀሳቸውና በተለይም ከከተማ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ወሰን ሳይኖራቸው በመቀላቀል ሃይማኖት፣ ባህልና ቋንቋቸውን ተካፍለዋል፡፡ በተወላጆች መካከልም ከእልፍ ዓመታት የዘለቀ እርስ በርስ መጋባትና መዋለድ ምክንያት ከፍተኛ ቁጥር ያለው ጉራማይሌ ብሔር ሕዝብ ተፈጥሯል፡፡ ይህ ሕዝብ ከማንነቱ የተወሰነውን ብቻ መርጦ ካልሆነ በስተቀር ሙሉ ማንነቱን ይዞ የዚህ ብሔር ተወላጅ ነኝ ማለት የማይችል ሲሆን፣ በዚህም ምክንያት ሙሉ ማንነቱን አስጠብቆ የገዥ ፓርቲው ስብስብን መቀላቀል የማይችልበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ የዚህ ሕዝብ ሙሉ ማንነት የሚወከለው ኢትዮጵያዊነት በሚለው ጥላ ሥር ብቻ ሲሆን፣ ይህን ይዞ በፖለቲካው ውስጥ የራሱን አሻራ ማሳደር የሚችለውም በክልላዊ ወይም ብሔር ተኮር ሳይሆን በአገራዊ ፓርቲ ሲታቀፍ ነው፡፡
ከብሔር ተኮር አደረጃጀት በተጨማሪ ኅብረ ብሔራዊ ቅርፅ የያዘ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በአገራችን የተፈቀደና አያሌ አቀንቃኞችን ያፈራ ሆኖ ሳለ፣ ይህን የፖለቲካ እንቅስቃሴ በማድረግ የፖለቲካ ምኅዳሩን የተቀላቀለው ከገዥ ፓርቲ ስብስብ ውጪ ያለው የሲቪል ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ ብቻ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህ ማኅበረሰብ ከደርግ ውድቀት ማግሥት አንስቶ በግለሰብ፣ በብሔርና፣ በኅብረ ብሔር ቅርፅ ሰፊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ በማድረግ በአንድ ወቅት ገዥ ፓርቲን የመገዳደር አቋም ላይ መድረስ ሲችል፣ በሌላ ጊዜ ደግሞ ያለ እስካይመስል ድረስ በጭላንጭል ብቻ ተወስኖ ቆይቷል፡፡ በአጠቃላይ ከገዥው ፓርቲ ስብስብ ውጪ ያለው የሲቪል ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ በፌዴራል ሥርዓቱ በማናቸውም ደረጃ የሥልጣን ባለቤት መሆን ባይችልም፣ በተለያዩ ጊዜያት የክልልና የፌዴራል ሕግ አውጪ አካላትን በአናሳነት ለመቀላቀል የበቃበት ሁኔታ ነበር፡፡ ባለፉት ሁለት ምርጫዎች ደግሞ ይህ ቁጥር ከማሽቆልቆል አልፎ በማዕከላዊም ሆነ በክልል ደረጃ ያለው ውክልና ፈጽሞ ጠፍቷል፡፡
የአገራችን ሲቪል ፖለቲካ እንቅስቃሴ ለምን አሁን ያለበት አቋም ላይ እንደ ደረሰ ለማስረዳት የሚደረገው ክርክር በገዥው ፓርቲና በተቃዋሚዎቹ በሚቀርቡ የሰማይና የምድር ያህል ልዩነትና ተቃርኖ ባላቸው የመከራከሪያ ነጥቦች የተሞላ ነው፡፡ በተከራካሪዎች በኩል ስሜታዊነትን ከሚጭሩ ጉዳዮች መካከል በመሆኑና ከዚህም አንፃር በዚህ ጽሑፍ አንድ አንቀጽ ወይም አንድ ክፍል ብቻ አመክንዮአዊ ትንተና ለመስጠት ከመሞከር፣ በሌላ ጽሑፍ ልመለስበት ቃል በመግባት በሁለቱም ወገን የሰላ የሐሳብ ፍጭት ተደርጎ አገራዊ መግባባት ላይ ካልደረስንባቸው አያሌ ጉዳዮች ተርታ መድበን ወደሚቀጥለው ክፍል እንለፍ፡፡
ብሔርን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም ማብቂያው መቼ ነው?
በዓለም ዙሪያ የፌዴራሊዝም ሥርዓትን በመገንባትና ለአስተዳደር በማዋል አገራችን ኢትዮጵያ ከአርፋጆች ቢሆን እንጂ ከቀዳሚዎች የምትመደብ አገር አይደለችም፡፡ዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ፣ ህንድ፣ አውስትራሊያና ካናዳን የመሳሰሉ ግዙፍ ዴሞክራሲዎች ከምዕተ ዓመታት በፊት ይህን የመንግሥት አወቃቀር የተገበሩ ሲሆን፣ ከፍተኛ ስብጥር ያለውን ሕዝባቸውን በአንድነት ጠብቀው ለምዕተ ዓመታት የዘለቀ ጉዞ ማድረግ በመቻላቸው የፌዴራሊዝም ስኬት ማሳያ ተደርገው ይወሳሉ፡፡ በአንፃሩ ደግሞ የባልካን አገሮች ጥምረት የነበረው የዩጎዝላቪያ ፌዴራሊዝም ስኬታማነቱን ጠብቆ መቀጠል አቅቶት ለመበታተንና ለእርስ በርስ ጦርነት መዳረጉ የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡
ፌዴራሊዝም እንደ ኢትዮጵያ ውስብስብ የሆነ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ትስስር ላላቸው ሕዝቦች አመቺ የሆነ የመንግሥት መዋቅር መሆኑ ባይካድም፣ አንድ አገር የፌዴራል ሥርዓትን በመከተሏ ምክንያት ብቻ የአገሪቱም ሆነ የሕዝቧ ጥቅም ይከበራል ማለት አይደለም፡፡ የፌዴራል ሥርዓት ሲገነባ የዜጎችን አብሮነት የሚያበለፅግና በውስጡ ያሉ ክልሎችን ለአንድ ብሔራዊ ህልውና የሚያሠልፍ መንገድ ካልተከተለ፣ በሒደት የአገሪቱን ህልውና ለአደጋ የሚያጋልጥ ክፍፍል ዕጣ ፈንታው ሊሆን ይችላል፡፡
የአገራችን ፌዴራል ሥርዓትም ይህ አደጋ በተወሰነ መልኩ እንዳንዣበበት ለመረዳት በየጊዜው በክልሎችና በብሔሮች መካከል የሚነሱ የማንነት፣ የድንበርና የሥልጣን ጥያቄዎች ማሳያ ይሆናሉ፡፡ የፌዴራል ሥርዓታችን ብሔርን መሠረት ያደረገ በመሆኑም የሚነሱ ግጭቶች በአካባቢያዊ አስተዳደሮች መካከል የተደረጉ ብቻ ሳይሆኑ፣ በብሔሮች ብሎም በሕዝቦች መካከል የተደረጉ ቅራኔዎች የሚሆኑበት ዕድል ይፈጠራል፡፡ በሥልጣን ላይ ያለው የፓርቲዎች ስብስብም እንዲሁ ብሔርን መሠረት ያደረገ መዋቀር የሚከተል ነውና በብሔሮች መካከል የሚፈጠር ቅራኔ ወዲያውኑ በአባል ፓርቲዎች መካከል የሚፈጠር ቅራኔን መጫሩ አይቀርም፡፡
አስተዳደራዊ ግጭቶች አስተዳደራዊ መፍትሔን ይሻሉ፡፡ የብሔር ግጭቶች ግን በአስተዳደራዊ ወይም በኃይል መፍትሔዎች ብቻ በዘላቂነት መፍታት አይቻልም፡፡ ይልቁንም ከመንግሥት የሚመጡ መፍትሔዎች እንደ ባዕድ የሚቆጠሩና ግጭትን የሚያባብሱ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በመንግሥትና በፓርቲ አወቃቀር ላይ የሚታየው ብሔርን መሠረት ያደረገ ሽንሸና፣ በብሔሮች መካከል ለሚፈጠር ግጭት ከመፍትሔነቱ ይልቅ መንስዔነቱ ያመዝናል፡፡ የአንድ አገር ሕዝብ ዘር ቆጥሮና ብሔር ለይቶ የገባበት ግጭት ውጤቱ እንደማያምር ለማስረዳት በ1990ዎቹ መጀመሪያ በሩዋንዳና በቦስንያ ሄርዞጎቪኒያ የተከሰቱ የብሔር ግጭቶችንና በእነዚህ አገሮች የተከሰቱትን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ከምንም በላይ ደግሞ ሥነ ልቦናዊ ጠባሳዎችን በምሳሌነት መጥቀስ እንችላለን፡፡ በአጭሩ ይህ ዓይነት ጦስ ለአገራችን አይደለም ለጠላታችን የማንመኘው ነው፡፡
ይህን በማየት ብሔርን መሠረት ያደረገው ፌዴራሊዝማችንና ይህንንም የሚተገብረው ብሔር ተኮር የፖለቲካ ጥምረት፣ የችግሩ አካልና መነሻ መሆኑን መገንዘብና ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ አካሄዱን አገራዊ ማንነት ላይ ባተኮረ ፍልስፍና የሚቀይርበት ጊዜ ደርሷል ለማለት እደፍራለሁ፡፡ እስካሁን የሄድንበት መንገድ ያስመዘገባቸውን ማናቸውንም ዓይነት ድሎች ሳንጥል የወደፊት ዕጣ ፈንታችን በወንድማማችነታችንና አብሮና ተከባብሮ የጋራ ማንነትን በማበልፀግ ላይ መሥርተን፣ የብሔር ግጭትና መቃቃርን ታሪክ አድርገን ማስቀረት ይኖርብናል፡፡ ይህም ኃላፊነት በቅድሚያ የአገራችንን ሁለንተናዊ ጉዞን በመምራት ላይ የሚገኘው የገዥ ፓርቲዎች ስብስብ ላይ ይወድቃል፡፡
ማጠቃለያ
የሲቪል ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በተፈቀደባቸውና ይህ መብት በተገደበባቸው ወይም በተከለከለባቸው አገሮች ሳይቀር፣ ዜጎች የተለያዩ ፖለቲካዊ አመለካከቶችን አንስተው ይነጋገራሉ፡፡ የሐሳብ ልዩነቶችና አንድነቶች በዚህ ሒደት ውስጥ የሚከሰቱ ተፈጥሮዓዊ ሁነቶች ናቸው፡፡ አንዲት አገር በውስጧ ባሉ የፖለቲካ ኃይሎች መካከል መፈጠራቸው የማይቀረውን የሐሳብ ልዩነቶች የምታስተናግድበትና የምትፈታበት ጥበብ፣ የራሷን ሁለንተናዊ ዕጣ ፈንታ የሚወስን ሒደት ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ለመዳሰስ የሞከርኩት ከ1983 ዓ.ም. ጀምሮ በተግባር ላይ ስላዋልነው ብሔርን መሠረት ያደረገ የፌዴራል ሥርዓት አወቃቀር ሲሆን፣ ለአገራችን ያስገኛቸውን ጥቅሞችን ሳንክድ በአፈጻጸምም ይሁን በርዕዮተ ዓለም ደረጃ ጉዳታቸው ያመዘኑ ጉዳዮችን ነቅሰን በማውጣት መጠገን፣ ካልሆነም መቀየር ይኖርብናል የሚለውን ጭብጥ ነው፡፡ ፍሬ ነገሩ ብሔርን መሠረት ያደረገ ሽንሸና እንጂ ፌዴራሊዝም የችግሩ ምንጭ አለመሆኑንም ለማስረዳት የቀረበ ትንተና ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡
ያልተዳሰሱና በበቂ ሁኔታ ያልተብራሩ ርዕሶች እንደሚኖሩ አልጠራጠርም፡፡ ዓባይን በጭልፋ ዓይነት ሊባልም ይችላል፡፡ ወደፊት ከየወቅቱ የፖለቲካ ሁኔታ ጋር እያስታከኩ አስተያየቶቼን እንደምሰጥ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡