የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥትና የግል አጋርነት ረቂቅ አዋጅ፣ የፌዴራል መንግሥት ፕሮጀክቶችን ብቻ የሚመለከት እንዲሆን ማሻሻያ በማድረግ አፀደቀ።
አዋጁ የፌዴራል መንግሥት ፕሮጀክቶችን ብቻ የሚመለከት እንዲሆን ከተደረገው መሠረታዊ ማሻሻያ ውጪ፣ ሌሎች ማሻሻያዎችም በረቂቁ ላይ ተደርገዋል።
ባለፈው ዓመት መጨረሻ ለምክር ቤቱ የቀረበው ይህ አዋጅ የተፈጻሚነት ወሰንን የሚገልጸው አንቀጽ፣ ‹‹ለክልል መንግሥታት በሚሰጥ ልዩ ድጋፍ የሚከናወኑ ፕሮጀክቶች›› በመንግሥትና በግል አጋርነት ማዕቀፍ ውስጥ እንዲካተቱ የሚያደርግ ነበር።
በረቂቁ ላይ የራሱን ምርመራና ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት በማድረግ ሐሙስ ጥር 17 ቀን 2010 ዓ.ም. የውሳኔ ሐሳቡን ይዞ የቀረበው፣ የበጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በረቂቁ ላይ የተደረጉትን ማሻሻያዎች አቅርቧል።
ከነዚህም መካከል ለክልል መንግሥታት በሚሰጥ ልዩ ድጋፍ የሚተገበሩ ፕሮጀክቶች በመንግሥትና በግል አጋርነት ማዕቀፍ እንዲከናወኑ የሚለውን አንቀጽ በማሻሻል፣ በፌዴራል መንግሥት በሚከናወኑ ፕሮጀክቶች ላይ ብቻ የሚፈጸም እንዲሆን ማሻሻያ አድርጓል።
ይህ ማለት ክልሎች በራሳቸው ሥልጣን ተመሳሳይ የሕግ ማዕቀፍ ከማዘጋጀት የሚከለክላቸው እንደማይሆን፣ ይልቁንም የክልሎችን ሥልጣን ለመጠበቅ ታስቦ የተደረገ ማሻሻያ መሆኑን ባለሙያዎች ይገልጻሉ።
ሌላው ማሻሻያ የተደረገበት ጉዳይ በሕግ ማዕቀፉ ሊለሙ ከማይችሉ ፕሮጀክቶች መካከል ‹‹የከርሰ ምድር ሀብት›› የሚለው እንዲወጣና በሕግ ማዕቀፉ እንዲካተት ማሻሻያ ተደርጎበታል።
በተጠቀሰው አጋርነት የሚተገበሩ ፕሮጀክቶችን ለመለየትም ሆነ አጠቃላይ አተገባበሩን ለመምራትና ለመከታተል በሚቋቋም ቦርድ ውስጥ የግሉ ዘርፍ ይወከላል የሚለው፣ የግሉን ዘርፍ ውክልና ያሳነሰ እንዲሁም የግሉን ዘርፍ የሚወክል ማለቱ ለትርጉም ክፍት ስለሆነ፣ የግሉ ዘርፍ ያልተስማማበትና መንግሥት የመረጠው እንዲወከል የሚያስችል እንደሆነ ትችት ሲቀርብበት ነበር።
በዚህ የረቂቅ አዋጁ አንቀጽ ላይም ማሻሻያ የተደረገ ሲሆን፣ ‹‹የግሉን ዘርፍ ከሚወክሉ ተቋማት›› በቦርዱ እንደሚወከሉ ማሻሻያ ተደርጎ ረቂቅ አዋጁ ፀድቋል። ይኼ አዋጅ በዋናነት በኤሌክትሪክ ኃይል ፕሮጀክቶች ለመሳተፍ የሚፈልጉ የውጭ ኩባንያዎች በጉጉት ሲጠብቁት የነበረና በዓለም ባንክ ውትወታ ሲደረግበት የቆየ ነው።