የዓለም ባንክ ከመደበው 450 ሚሊዮን ዶላር በጀት 70 በመቶ ድርሻ የያዘው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ በተያዘው በጀት ዓመት ከድህነት ወለል በታች የሚገኙ 200 ሺሕ ነዋሪዎችን በምግብ ዋስትና ፕሮግራም እንደሚያቅፍ አስታወቀ፡፡
አስተዳደሩ ከተያዘው በጀት 32 ሺሕ ለሚጠጉ ከድህነት ወለል በታች የሚገኙ አቅመ ደካሞች ቀጥታ ወርኃዊ ክፍያ ለመፈጸም፣ 168 ሺሕ የሚሆኑ ነዋሪዎች ደግሞ በማኅበረሰብ አቀፍ ፕሮግራም ታቅፈው የተለያዩ ሥራዎችን ሠርተው ወርኃዊ ክፍያ እንዲያገኙ ዕቅድ አውጥቷል፡፡
ይህ ፕሮግራም ባለፈው ዓመት ሲጀመር ከድህነት ወለል በታች የሚገኙ 19 ሺሕ አቅመ ደካሞች በቀጥታ ተካፋይ ሲሆኑ፣ 123 ሺሕ የሚሆኑ ደግሞ በማኅበረሰብ አቀፍ ሥራዎች ተሳታፊ ሆነው ክፍያ እንደተፈጸመላቸው ተገልጿል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤፍሬም ግዛው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በዚህ ፕሮግራም የደሃ ደሃ የሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች ይደገፋሉ፡፡
‹‹ክፍያው በአንድ ሰው 170 ብር ነው፡፡ አንድ ቤት ውስጥ አራት ሰዎች እንደሚኖሩ ታሳቢ ተደርጎ ይህ ክፍያ በአራት ሲባዛ 680 ብር ይሆናል፡፡ ፕሮግራሙን ፋይናንስ የሚያደርገው የዓለም ባንክ በመሆኑ፣ በቅርቡ ብር ከዶላር ጋር ያለው ምጣኔ በ15 በመቶ እንዲቀንስ በመደረጉ ልዩነቱ በቅርቡ ይጨመራል፤›› ሲሉ አቶ ኤፍሬም አስረድተዋል፡፡
አቶ ኤፍሬም እንዳሉት በተያዘው በጀት ዓመት በ55 ወረዳዎች የሚገኙ 200 ሺሕ የደሃ ደሃ ነዋሪዎችን ለመደገፍ የመለየት ሥራ ተከናውኗል፡፡ ፕሮግራሙ ከ2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለአሥር ዓመታት ተግባራዊ የሚደረግ በመሆኑ፣ በዚህ ጊዜ ውስጥ በአዲስ አበባ ብቻ እስከ 600 ሺሕ ነዋሪዎች ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሏል፡፡ የመሥራት አቅም ያላቸው ነዋሪዎች በከተማ ፅዳት፣ በአረንጓዴ ልማትና በመሳሰሉት የሥራ መስኮች እንደሚሳተፉ ተገልጿል፡፡