አሌክሳንደር ፑሽኪን እ.ኤ.አ. ሰኔ 6 ቀን 1799 ተወለደ፡፡ በአባቱ በኩል የጥንታዊት ሩሲያ መሳፍንት ዘር ሲሆን በእናቱ ወገን ደግሞ ቅድመ አያቱ ከአፍሪካ ግንድ ከኢትዮጵያ/አቢሲኒያ የሆነው አብርሃም ሃኒባል ነው፡፡ የቤተሰቡ ታሪክ እንደሚያወሳው ከሆነ አብርሃም ሃኒባል የአንድ ኢትዮጵያዊ መስፍን ልጅ ነው፡፡ አብርሃም ሃኒባል ማለትም የአሌክሳንደር ፑሽኪን ቅድመ አያት በሩሲያ ንጉሠ ነገሥት የታላቁ ጴጥሮስ ልጅ ሆኖ አደገ፡፡ በኋላም ተምሮ በመንግሥት አገልግሎት በመሰማራትም እስከ ጀነራል ማዕረግ ደርሷል፡፡ ኢትዮጵያዊው አብርሃም ሃኒባል ካፈራው ሀብት ከሴት አያቱ ለፑሽኪን ደርሶታል፡፡ አሌክሳንደር ፑሽኪን ሥነ ጽሑፍ በተለይ ግጥምን መጻፍ ከጀመረ በኋላ ብዙ ጊዜ አፍሪካዊነቱን ኢትዮጵያዊነቱን ያስታውስ ነበር፡፡ እርሱም በአንድ ወቅት በነበረበት ከባለሥልጣኖች ጋር ችግር ለምን ወደ ሁለተኛ አገሬ አፍሪካ ሄጄ ባርፍ ብሎ ይናገርና ይጽፍ ነበር፡፡
ዓለም አቀፍ የፑሽኪን ፋውንዴሽን ሲመሠረት አንድ በሩሲያ ሕዝብ ውስጥ የሚታይ ነገር ተገነዘበ፡፡ ይኸውም የአሌክሳንደር ሰርጌይቪች ወዳጆች የሩሲያ ፍቅረኞች ተማሪዎች ወታደሮችና የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች ሕዝብ እርሱን ጠግቦ መናገር አያባሩም ነበር፡፡ ስለ ሥራዎቹ በቃላቸው ሲገጥሙና ሲያነቡ ልዩ ነው፡፡ የአሌክሳንደር ሰርጌይቪች ሥራዎችን በማንሳት ሩሲያውያን ሲያደንቁትም ሆነ ሲናደዱ ተወው ይኼ ኢትዮጵያዊ አፍሪካዊ ‹‹ቮት ኢታ ኤፍዎኘ›› ይሉታል፡፡ ይህን የኢትዮጵያና የሩሲያ ቅርስ ብሎም የአፍሪካ ቅርስ ለዘላለም ይኖራል፡፡ አሌክሳንደር ፑሽኪንም በሕዝባችን አኅጉሮችን አንድ ሲያደርግ ይገኛል፡፡
ዛሬ አዲስ አበባ በሩሲያ በሳይንስና የባህል ማዕከል ወይም በሕዝባችን አጠራር የፑሽኪን ማዕከል የኢትዮጵያ ገጣሚያንና የታሪክ ሰዎች በተለይ ወጣቶች ግጥማቸውንና ጽሑፋቸውን ከፑሽኪን ጋር ለማመሳሰል ይጥራሉ፡፡ በዚህም የውልደቱ ቀናት በፑሽኪን አዳራሽ የፑሽኪን ገጣሚያን ማኅበር ዝግጅታቸውን ያቀርባሉ፡፡ በመሆኑም የሥነ ጽሑፍ ጥማታቸውን በሩሲያ የሳይንስና ባህል ማዕከል ይወጣሉ፡፡ በመሆኑም ዛሬ በኢትዮጵያ የሥነ ጽሑፍንና ግጥምን በሚሠራ ሰው በፑሽኪን ባህል አዳራሽ ተገኝቶ ሥራውን ሲያቀርብ ለዛ ሩሲያዊ ኢትዮጵያዊ ለሆነው አሌክሳንደር ፑሽኪን ክብራቸውን ስለገለጹ ታሪካቸው ዓለም አቀፍ እንደሆነላቸው ይቆጥሩታል፡፡ ይህም ለሩሲያና ኢትዮጵያ ግንኙነት ታሪካዊና ወቅታዊ መስለው ሆኖ ይገኛል፡፡
አዎ አሌክሳንደር ፑሽኪንን እናስታውስ አሁን በልደቱ ዕለት ማለትም ሰኔ 6 ቀን እ.ኤ.አ. እናከብራለን፡፡ አዲስ አበባ በሚገኘው ብሔራዊ ሙዚየም የሚገኘውን በግንባታ ምክንያት የተነሳው በሞስኮ መንግሥት የተሰጠ ሐውልት አጠገብ ጉንጉን አበባ እናደርጋለን፡፡ ግጥምም ይነበባል፡፡ ሕፃናትም፣ ወጣቶችም፣ ገጣሚያንም ይገኛሉ፡፡ አዎ በአዲስ አበባ የፑሽኪን አደባባይ አሁን ትልቅ ሆኖ ተሠርቷልና ከተማችንንና አደባባዩን የሚመጥን አዲስ ሐውልት ከሞስኮ እንጠብቃለን፡፡ ይህ ሐውልት ሲመጣና አደባባዩ ቅርጹን ሲይዝ ወደፊት ኢትዮጵያውያንና ብሎም አፍሪካውያን ብቻ ሳይሆኑ የዓለም ኅብረተሰብ በተከታታይ እንደሚጐበኙት ይታመናል፡፡ ሞስኮ አሌክሳንደር ፑሽኪን ሐውልት ሥር እንደሚደረገው ፍቅረኞች ተጋቢዎችና ተወያዮች ለሐሳብ ዕረፍት መዝናኛ ቦታ ይመርጡታል ተብሎ ይታመናል፡፡ ለዚህም እንደሚመቻች ይጠብቃል፡፡
አሌክሳንደር ፑሽኪን ብዙ የግጥም ሥራዎችን ሠርቶ አልፏል ለምሳሌ ‹‹ለእኔዋ አፍሪካ ሰማይ›› ‹‹ለአያቴ ኢትዮጵያዊ ዘርነቱ ከሚገኝበት ‹‹ኑዛዜ›› ‹‹ቁንጅና›› በእኔ ፊት ‹‹ለሩሲያ ስም አጥፊዎች›› ‹‹ሐውልት›› ስለ ዘለዓለማዊነቱ ሥራው ‹‹የታላቁ ጴጥሮስ ጥቁር ባለሟል›› ስለ ቅድመ አያቱ ያነሳበት ጽሑፎች ይገኛሉ፡፡
አዎ ሰሞኑን የሩሲያዊ ኢትዮጵያዊው አሌክሳንደር ፑሽኪንን ልደት ስናከብር ወደፊት አዲስ ሐውልት ሲመጣ መንግሥታችንና ሕዝባችን በዓለም ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ ኢትዮጵያዊውን አሌክሳንደር ፑሽኪን ለመቀበል የወቅቱ ትውልድ ዕድገትና ዲሞክራሲ ለሚመጥን መሠረት አዲስ አበባ ተቀብላ እንደምታስተናግድ ይታመናል፡፡ የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የሆነችው አገራችን በየባህል በአለባበሷ አጊጣ ሐውልቱን እንደምታሳርፈውና የአፍሪካ መዲና የሆነችበትንና የሁሉ አፍሪካውያን የሆነውን አሌክሳንደር ፑሽኪን በክብር የምታኖርበት ጊዜን በጉጉት ሲጠበቅ የዋና ከተማችንም ነዋሪዎች በተለይ ተማሪዎች የሥነ ጽሑፍ፣ ሙዚቀኞችን ሌሎችም እንደሚተባበሩ ከፍተኛ እምነት አለ፡፡ በመሆኑም ሩሲያውያን ዳያስፖራዎች አሌክሳንደር ፑሽኪንን በኢትዮጵያ የተጠበቀ ቅርስ ልዩ የሩሲያውያንና የኢትዮጵያውያን ሀብት ነው በማለት ልደቱን በታላቅ ደስታ ያከብሩታል፡፡ ይጠብቁታል፡፡
በአሁኑ ወቅት ኢንተርናሽናል ፑሽኪን ፋውንዴሽን ከኢትዮጵያ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና ከሩሲያ የሳይንስና ባህል ማዕከልና ከኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር ጋር በመተባበር የአሌክሳንደር ፑሽኪን 220 ዓመት ልደት ለማክበር የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የአሌክሳንደር ፑሽኪን ሥራዎች ኮንግረስ ለማካሄድ ሥራ ላይ ይገኛል፡፡ ይህም ዝግጅት ከአፍሪካ ኅብረት ጋር ይደረጋል፡፡
በመጨረሻ እንኳን ለ217ኛው የታላቁ ሩሲያዊና ኢትዮጵያዊ ገጣሚ አሌክሳንደር ፑሽኪን በጁን 6 በሰላም አደረሳችሁ፡፡
የኢንተርናሽናል ፑሽኪን ፋውንዴሽን