አፍሪካ ኅብረት የተካው የቀድሞውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ለመመሥረት በአፋጣኝ ተጣድፎ የተገነባውና ለአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና አዳራሽ ሆኖ ሲያገለግል የቆየው አፍሪካ አዳራሽ በቅርስነት እንዲጠበቅ የሚያስችለው መሠረታዊ ጥገና እንዲደረግለት 56.9 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ገንዘብ እንደሚያስፈልግ ተገለጸ፡፡
አፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ለሪፖርተር በሰጠው መግለጫ መሠረት ከሁለት ዓመት በኋላ መሠረታዊ የጥገና ሥራው እንደሚጀመር የሚጠበቀውና አፍሪካ አዳራሽ በመባል የሚታወቀው ሕንፃ፣ በቀዳሚ ንጉሠ ነግሥት ኃይለ ሥላሴ ዘመን፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን መሥራች ጉባዔ እንዲያስተናግድ ታስቦ የተገነባ ነው፡፡
የግንባታ ሒደቱ 18 ወራት ብቻ የፈጀው አፍሪካ አዳራሽ እ.ኤ.አ. በ1961 ግንባታው በአንድ ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ ሊጠናቀቅ የቻለው አፍሪካ አዳራሽ፣ በ75 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ያካተተ ግዙፍና ዘመናዊ ሕንፃ ነው፡፡ ከዚህ ቦታ ውስጥ 3,600 ካሬ ሜትር የስብሰባ አዳራሾች ያረፉበት፣ 5,500 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነቡ ጽሕፈት ቤቶች እንዲሁም 4,700 ካሬ ሜትር ቦታ የሚሸፍኑ ጠቅላላ አገልግሎት የሚሰጡ ልዩ ልዩ ሕንፃዎችን ያካተተ ትልቅ ተቋም ነው፡፡
የአፍሪካ አዳራሽ ዕድሳት እ.ኤ.አ. በ2018 ተጀምሮ በ2021 እንዲጠናቀቅና ለአገልግሎት ክፍት እንዲደረግ መታቀዱን የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አስታውቋል፡፡ በቅርቡ ከፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ጋር በሕንፃው ዕድሳት ጉዳይ ላይ የተወያዩት፣ የኮሚሽኑ ዋና ጸሐፊ ዶ/ር ካርሎስ ሎፔዝ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ፣ ለሕንፃው ዕድሳት የሚያስፈልገውን ወጪና የጊዜ ሰሌዳ ማጽደቁን ለፕሬዚዳንቱ አስረድተዋል፡፡ የዕድሳት ወጪውንም ተመድ ከአባል መንግሥታት በሚዋጣ ገንዘብ ሊገነባ እንደሚችል ዋና ጸሐፊው አስታውቀዋል፡፡
የመጀመሪያውን መሥራች የአፍሪካ አንድነት ጉባዔ አሳክቶ፣ አጀብ አሰኝቶ የቆየው አፍሪካ አዳራሽ፣ ከጥቂት ዓመታት በኋላ 800 ያህል ተጨማሪ ጽሕፈት ቤቶችን ያካተተ ባለ ስድስት ፎቅ ሕንፃ እ.ኤ.አ. በ1975 ታክሎለታል፡፡ በቅርቡም አዲስ አበባን ከብራስልስና ከኒውዮርክ በመቀጠል በተመድ የሥራ ስምሪት ረገድ በርካታ ኤጀንሲዎች የሚንቀሳቀሱባት ለመሆኗ ማሳያ የሆነ ተጨማሪ ሕንፃ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ግቢ ውስጥ ተገንብቶ ለአገልግሎት በቅቷል፡፡
በቀድሞው የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ገናና ሥራ በሆነውና 150 ካሬ ሜትር ስፋት ባለው የመስታወት ላይ ሥዕል ያጌጠ ሕንፃ ነው፡፡ ‹‹ቶታል ሊበሬሽን ኦፍ አፍሪካ›› የሚል ስያሜ ከተሰጠው ከዚህ ሥዕል ባሻገር በርካታ የጠቢቡ ሰው ሥራዎችም በአፍሪካ አዳራሽ ይገኛሉ፡፡