– የከፍተኛ አመራር ተተኪን ለመፍጠር ቁልፍ ሥራ መጀመሩ ተገለጸ
የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሳ የኢትዮ ኤርትራ ግንባር ፍፁም የማይደፈር ሆኖ መደራጀቱን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታወቁ፡፡
ሚኒስትሩ የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት፣ የኢትዮ ኤርትራ ግንባር በሁሉም ደረጃዎች ለሥልታዊ ኦፕሬሽን ሁለገብ የኃይል ዝግጁነትን ለማረጋገጥ መቻሉን ገልጸዋል፡፡
በግንባሩ የተሠለፈው ሠራዊት ዕለት ተዕለት የሚፈጽማቸው ወቅታዊና ሕገ መንግሥታዊ ግዳጆች ዓላማና ሊገኝ የሚፈለገውን ውጤት የሚገነዘብ፣ በወቅታዊ ግዳጁ ላይ የተሟላ ግንዛቤና አረዳድ እንዲይዝ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ተዋጊ አሀዶችም ከደረጃ አንፃር መያዝ ያለባቸውን የጦር መሣሪያዎችና ተተኳሾችን እንዲታጠቁ ተደርጓል ብለዋል፡፡
የአየር መከላከያ ኃይል መሣሪያዎች በቁጥርና በጥራት የተሟሉ እንዲሆኑ፣ እንዲሁም ተጨማሪ የሰው ኃይል በመመደብ ነባሮችንና አዳዲስ ‘ሳይቶችን’ የማጠናከር ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በጠንካራ ይዞታና በዋና መቺነት የተሠለፈው ኃይል ቁመናው ሁሌ የተጠበቀና ዝግጁ እንዲሆን መደረጉን የገለጹት ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ፣ ይህ በመሆኑም በማንኛውም ጊዜ ለሚከሰቱ ትንኮሳዎች አስተማማኝ የሆነ ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል የሥነ ልቦናና ጠቅላላ ዝግጁነት መፍጠር መቻሉን አስረድተዋል፡፡
በአጠቃላይ የመላ ሠራዊቱን ጥንካሬ ለማስቀጠል የማያቋርጥ የማጐልበት ሥራ እየተሠራ መሆኑን፣ በሁለተኛ ደረጃ አሁን ያለው ሠራዊት መልካም እሴት ተጠብቆ መተካካትን መፍጠር የሚቻልበት ስትራቴጂ መገንባት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
‹‹አሁን ያሉት ከፍተኛ አመራሮች በትግል ጊዜ ይዘዋቸው ያመጡዋቸው ጥሩ የሚባሉ እሴቶች አሏቸው፡፡ ሕገ መንግሥቱን በፅናት የመያዝ፣ ሕዝባዊነትና ተልኮ ፈጻሚነት በከፍተኛ ደረጃ የተጐናፀፉ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡
ይህ ሳይበረዝ ተኪ አመራር መፍጠር ላይ ቁልፍ ሥራ መጀመሩን የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ ለዚህም ራሱን የቻለ የትምህርት ተቋም መገንባቱን ገልጸዋል፡፡