ዶዶ እስከ 19ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ በምድር ይኖር የነበረ ከማይበሩት የሚመደብ አዕዋፍ ነው፡፡ ሞሪሽየስ በሚባለው የህንድ ውቅያኖስ ደሴትም ላይ ብቻ ይገኝ እንደነበር ይነገራል፡፡ ከርግቦች ጋር ሲነፃፀር በአንድ ሜትር ዘለግ ያለ ቁመት ሲኖረው 20 ኪሎ ግራም ያህል ክብደትም ይመዝን ነበር፡፡ የሰው ልጅ ስለ አካባቢው በጽሑፍ ማስፈር በጀመረበት ጊዜ ይኖሩ ስለነበር ትክክለኛው የጠፉ ዝርያዎች መገለጫ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ለነገሩ የሰው ልጅም ለመጥፋታቸው ቀጥተኛ ተሳትፎ አድርጓል ይባላል፡፡ የሰው ዘር ለነዚህ ዝርያዎች መጥፋት መንስዔ ናቸው የሚባለው በሚኖሩበት ደሴት ውስጥ እነሱን ሊያጠቁ የሚችሉና ከዛ በፊት ያልነበሩ እንስሶችን ይዘው በመግባታቸው እንደሆነ ይታመናል፡፡ ውሻ፣ አሳማ፣ ድመትና አይጥ የዶዶዎችን ጎጆ ሲያራቁቱና ሲያጠቋቸው ሰው ደግሞ ጫካቸውን በመመንጠሩ እንዳጠፋቸው ይታመናል፡፡ በዚህም ምክንያት ከታወቁበት ጊዜ 200 ዓመት ባነሰ ለጥፋት ተዳረጉ፡፡ የእንግሊዝ ጦር ሞርሺየስ ላይ ሰፍሮ በነበረበት ጊዜ የመጨረሻዋ ዶዶ በአሳማ እንደተበላች ይነገራል፡፡ ይህም የሆነው በ1868 ዓ.ም. ነው፡፡
የማይበሩት
የማይበሩት ወፎች የሚባሉት ከአፍሪካ ሰጎን፣ ከአውስትራሊያ ኢሙና ካሶዋሪ፣ ከደቡብ አሜሪካ ሪያ፣ ከኒውዝላንድ ኪዊና ከአንታርክቲካ ፔንጉዊንስ ናቸው፡፡ በመላው ዓለም ተሰራጭተው የሚገኙት የቤት ውስጥ ዶሮዎችም ከነዚሁ ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡ ከኪዊ በስተቀር ሌሎቹ ክንፍ አላቸው፡፡ የአንዳንዶቹ የማይበሩ ወፎች የሩጫ ፍጥነት ያለመብረር ችሎታቸውን ያካካሰላቸው ይመስላል፡፡ ሁለት ፈጣን ተወዳዳሪ ሯጭ ወፎች ሰጎንና ኢሙ ናቸው፡፡ ሰጎኖች ከ45 እስከ 60 ኪሎ ሜትር በሰዓት ይሮጣሉ፡፡ ኢሙ 65 ኪሎ ሜትር በሰዓት ይሮጣል፡፡ የኢሙ ወንዱ ከሴቷ በመጠን ያንሳል፡፡ ዕንቁላሉን የሚያስፈለፍለውና ጫጩቶቹን የሚንከባከበውም ወንዱ ነው፡፡
- ማንይንገረው ሸንቁጥ ‹‹ባለአከርካሪዎች›› (2004 ዓ.ም.)