በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል በቅርቡ የኩላሊት ንቅለ ተከላ እንደሚጀመር፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱ ለፓርላማ ገለጹ፡፡
ሚኒስትሩ የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን ግንቦት 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት፣ የኩላሊት ንቅለ ተከላ በኢትዮጵያ ይጀመራል የተባለበት ጊዜ ለምን እንደዘገየ በምክር ቤቱ ተጠይቀዋል፡፡
‹‹በዚህ ዓመት እንጀምራለን ብለን የነበረ ቢሆንም የግብዓት ግዥው ከታሰበው ጊዜ በላይ መውሰዱ፣ እንዲሁም ማዕከሉን ለሕክምናው በሚመች ሁኔታ የማደስ ሥራው ጊዜ በመውሰዱ ዘግይቷል፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
የኩላሊት ንቅለ ተከላ ለማድረግ የሚያስፈልጉ መሣሪያዎች፣ ግብዓቶች፣ መድኃኒቶች እንዲሁም የሕክምና ማዕከሉ ዝግጅት መጠናቀቁን ጠቁመዋል፡፡
በአሁኑ ወቅትም በባለሙያዎች የታካሚዎች መረጣ እየተካሄደ መሆኑን፣ ኩላሊት የሚለግሱ ሰዎች ወይም ቤተሰቦችም እየተለዩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የታካሚዎች መረጣ የሚደረገው ለሕክምናው ብቁ መሆናቸውን ለማረጋገጥ እንደሆነ፣ መረጣው ሲጠናቀቅም በቀጥታ የንቅለ ተከላ ሕክምናው መሰጠት እንደሚጀመር አስታውቀዋል፡፡
የኩላሊት ንቅለ ተከላ ሕክምና አገልግሎት ለመስጠት ጫፍ ላይ በመደረሱ፣ አሁን በሰፊው ትኩረት የተሰጠው ለኩላሊት እጥበት አገልግሎት መሆኑንና ወደ ክልል የጤና ተቋማት የማስፋፋት ሥራ ላይ መሆናቸውንም አብራርተዋል፡፡
የኩላሊት እጥበት (ዲያሌሲስ) በተለያዩ የክልል ከተሞች መጀመሩን አስታውቀው፣ ለአብነትም በመቐለ ሐይደር ሆስፒታልና በባህር ዳር ከተማ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡
ዝግጅት እየተደረገባቸው ነው ካሏቸው ከተሞች መካከል ጐንደር፣ ሐዋሳና ጅማ ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታሎችና ወራቤ ሆስፒታል ይገኙበታል፡፡
በአዲስ አበባም የዲያሌሲስ ሕክምናውን በዘውዲቱ፣ በየካቲት 12 እና በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታሎች ለማስፋፋት መታቀዱን አስረድተዋል፡፡