‹‹እናመሰግናለን›› የሚለው ለኃያሉ ኃይሌ ገብረሥላሴ የተሰነዘረ የምስጋና ቃል የተሰማው በለንደን ማንችስተር ከተማ ባለፈው እሑድ ነበር፡፡ የሩጫ ስፖርት ተንታኞች ስለ ኃይሌ አውርተው በማይሰለቹበት አንደበታቸው የታላቁን አትሌት ስንብት በማስመልከት እናመሰግናለን ብለዋል፡፡ አስተያየቱም ለኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ስፖርት ቤተሰብ የቤት ሥራ የሰጠ ይመስላል፡፡ ‹‹እንዴት በክብር ይሸኝ ይሆን?›› ለሚለው ጥያቄ ምላሹ ይቆይና ለአሁኑ ግን የታላላቅ ሩጫ ክብረወሰኖች አለቃ፣ የዓለም የሩጫ ስፖርት ድምቀት፣ ከ20 ዓመታት በላይ ዝናውን የናኘበት ስፖርት፣ ከእንግዲህ ላይመለስበት ከውድድር ዓለም መሰናበቱን ይፋ ያደረገው በለንደን የስፖርት መናገሻ በሆነችው በማንችስተር ሲሆን፣ ኃይሌ በከተማዋ እስካለፈው እሑድ 16ኛ ደረጃ አግኝቶ እስካጠናቀቀበት ድረስ ለአምስት ጊዜ የድል አክሊል የተቀዳጀበትን ዓመታት አሳልፎበታል፡፡
ኃይሌ የዛሬ አምስት ዓመት ገደማ ከሩጫ ውድድር ራሱን ማግለሉን የሚገልጹ ዘገባዎች ወጥተው መነጋገሪያ ሆኖ ነበር፡፡ ‹‹አቁሜያለሁ›› ካለ በኋላ መልሶ ወደ ውድድር መመለሱም እንዲሁ መነጋገሪያ ሆኖ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ አትሌቱ ሁኔታውን አስመልክቶ በጊዜው የተናገረው በስሜት ሆኖ እንደነበር ገልፆ ውሳኔውን ካጤነ በኋላ ወደ ውድድር መመለሱም ይታወሳል፡፡
ከ24 በላይ የዓለም ታላላቅ ክብረወሰኖችን ያንኮታኮተው ኃይሌ በዓለም ስሙ የናኘባቸው ከተሞች፣ በአፍሪካ ምሳሌ የሆናቸው ስፖርተኞች፣ ለኢትዮጵያ ደግሞ እንደ ዓርማ መታወቂያም የሆናት ታላቁ ሰው እጅ መስጠት ግድ ሆኖበታል፡፡ ፊት የለመደ ከኋላ መከተል እንደማይስማማው ዕድሜውና ጉልበቱ ተባብረው የለመደውን የክብር ቦታ ስለነፈጉት ማቆሙ ተገቢ እንደሆነ አምኗል፡፡
‹‹ሩጫ ማቆም አልችልም ሩጫ ለእኔ ሕይወቴ ነው›› በማለት ከእንግዲህ ወደ ውድድር ፊቱን እንደማያዞር ያስረዳው ኃይሌ ሩጫን ግን በሕይወት እያለ ማቆም እንደማይሆንለት ተናግሯል፡፡
ኃይሌ በሩጫው ዓለም ከሁለት አሠርታት በላይ ባስቆጠረው ስኬታማ የውድድር ዓመታት ውስጥ ለአንድ አትሌት ትልቁ ሕልሙ እንደሆነ በሚነገርለት ኦሊምፒክ በ1988 ዓ.ም. እና በ1993 ዓ.ም. በ10,000 ሜትር በተከታታይ ሁለት ኦሊምፒክ ላይ የወርቅ ሜዳሊያ አሸናፊ ከመሆኑም ባሻገር፣ የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር (አይኤኤኤፍ) በወርቅ ደረጃ ዕውቅና በሚሰጣቸው ኦሊምክን ጨምሮ በዘጠኝ የተለያዩ ርቀቶች አዳዲስ ክብረ ወሰኖችን አስመዝግቧል፡፡ ከዚህ ውጪ አምስት የቤት ውስጥ ውድድሮችን ጨምሮ በአጠቃላይ ከ15 በላይ የጎዳና ሩጫዎችን ማሸነፍ የቻለው አዳዲስ ክብረ ወሰኖችን በማስመዝገብ እንደነበርም ይታወቃል፡፡
ኃይሌ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለምን ትኩረት ማግኘት የቻለው በ1985 ዓ.ም. የዓለም ወጣቶች ሻምፒዮና ላይ በአምስትና አሥር ሺሕ ሜትር የድርብ ድል ባለቤት ከሆነ በኋላ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ለኃይሌ ትልቅ ስኬት ተደርጎ የተወሰደው ደግሞ በ2001 ዓ.ም. በርሊን ማራቶን ርቀቱን ከ2፡04 በታች መግባቱ ሲሆን፣ ከአንድ ዓመት በኋላ በራሱ የተያዘውን ክብረወሰን 2 ሰዓት 03 ደቂቃ በማጠናቀቅ ያስመዘገበው ውጤት ከኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን የዓለም ክስተት እስከመባል ደርሶም ነበር፡፡
በወቅቱ ያስመዘገባቸው አንዳንዶቹ ክብረወሰኖች ከጊዜ በኋላ የተሰበሩ ቢሆንም፣ ሆኖም ተከታታይነት ያላቸውን ውድድሮች በማሸነፍ ኃይሌን ልዩ እንደሚያደርገው የብዙዎች እምነት ሆኖ ቆይቷል፡፡