ለዚህ ጽሑፍ መነሻ ከሆኑ ነገሮች ዋነኛው የዳግማዊ አፄ ምኒልክ የአደራ ቃል ነው፡፡ መጀመርያ ቃል ነበር እንዲል ታላቁ መጽሐፍ ቅዱስ፣ ዳግማዊ ምኒልክ ግንቦት 10 ቀን 1901 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ጃንሜዳ የኢትዮጵያን ሕዝብ አስመልክቶ ያስተላለፉት ቃልኪዳን ነበር፡፡ የቃል ኪዳኑ መልዕክት የንጉሡን ብልኃት፣ ጥበብና የመሪነት ሚናቸውን የሚያሳይ ነው፡፡
ይህ ቃል በልባቸው አገርን ሲመሩበት የነበረውን ጥበብ፣ በፍቅር ለማዋሀድ ያበረታቸውና ከግለሰቦች ፀብ በላይ መሆኑን ያመላከቱበት ነበር፡፡ የሥልጣናቸው ዘመን ማብቂያ አካባቢ ለኢትዮጵያ ሕዝብ በአደራ፣ በቃል ኪዳን፣ በማስጠንቀቂያና የወደፊቷን ኢትዮጵያ ምሥል ለማሳያ እንደ ጠቋሚ ካርታ አመላካች ነው፡፡ የዚህ የቃል ኪዳን መልዕክት እንዲህ የሚል ነው፡፡
‹‹እኔ እስካሁን በፍቅር እንዳኖርኳችሁ እናንተም ተስማምታችሁ በፍቅር እንድትኖሩ እለምናችኋለሁ፡፡ እናንተ አንድ ልብ ከሆናችሁ በምቀኝነት እርስ በርሳችሁ ተዋግታችሁ ካላለቃችሁ በቀር አገራችንን ኢትዮጵያን ለሌላ ባዕድ አትሰጧትም፡፡ ክፉም ነገር አገራችንንም አያገኛትም፡፡ ንፋስ እንዳይገባባችሁ አገራችሁን በያላችሁበት በርትታችሁ ጠብቁ፡፡ ወንድሜ፣ ወንድሜ እየተባባላችሁ ተደጋገፉ የኢትዮጵያን ጠላት ተጋግዛችሁ ተድንበር መልሱ፡፡ የኢትዮጵያ ጠላት በአንዱ ወገን ትቶ በአንዱ ወገን ቢሄድና ድንበር ቢጋፋ፣ በእኔ ወገን ታልመጣ በመጣበት በኩል ሁላችሁም ሂዳችሁ በአንድነት ተጋግዛችሁ ጠላታችሁን መልሱ፡፡ እስከቤታችሁ እስኪ መጣ ዝም ብላችሁ አትቆዩ፡፡››
ይህ መልዕክት በመጀመርያ የዳግማዊ ምኒልክን አስተዋይነት ብቻ አይደለም የሚያሳየው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ያለችበትንም ሁኔታ ጭምር የሚገልጽ ነው፡፡ ንጉሡ ያስተላለፉት መልዕክት ይኼ ብቻም አይደለም፡፡ በርካታ ቁምነገር ያላቸውና የእሳቸውን የታላቅ መሪነት፣ አባታዊ መካሪነት፣ የሕዝብ ወገንተኛ መሆናቸውን፣ አስተዋይነታቸውን፣ የወደፊቱን ችግር አስቀድመው በመተንበይ መፍትሔ አመላካችነታቸውን የሚያሳይ በመሆኑ እንዲህ ይነበባል፡፡
‹‹እኔ እናተን አምኜ ልጄን አደራ ብዬ እሰጣችኋለሁና አሳድጉት፣ በብልኃት ምከሩት፣ በጉልበት አግዙት፣ በምክር ደግፉት፡፡ ልጄን አደራ መስጠቴ ከልጄ ጋር ኢትዮጵያን አደራ ጠብቁ ማለቴ ነው፡፡ እኔም ይኸው በገዥዎቹ አለማወቅ በሕዝቡ አለመስማት የተነሳ ተብዙ ዘመን ጀምራ ተከፋፍላ የነበረችውን አገራችንን ኢትዮጵያን ማሰኛ፣ ተጣጥሬ ይኸው አስፋፍቻለሁ፡፡ እናንተም ከልጄ ጋር ሆናችሁ ተስማምታችሁ የኢትዮጵያ ድንበር እንዲሰፋ እንጂ አንድም ጋት መሬት እንዳይጠብ አድርጉ ጠብቁ አልሙ፡፡ የደጊቱ አገራችን የኢትዮጵያ አምላክ ያግዛችሁ፣ ይጠብቃችሁ፤›› ይላል መልዕክቱ፡፡ እነዚህ ቃላት ከመቼውም ጊዜ በላይ አሁን ለአገራችን ኢትዮጵያ ያስፈልጋታል፡፡
ስለዚህ ወንድሞች፣ እህቶች፣ አባቶችና እናቶች ይህችን ለምና ውብ አገር፣ አያቶቻችን በነፃነት ያስረከቡን አገር፣ ነፃነት ብቻ ሳይሆን ለወደፊትም አንድ ሆና በፍቅርና በኅብረት የምትኖርበት የቃል ኪዳን ካርታ ጭምር ነው፡፡. . . ይቀጥላል
(ዓቢይ ዓለሙ፣ ከአዲስ አበባ)