ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ በልደታ፣ በጉለሌና በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተሞች በሚገኙ 11 ወረዳዎች ውስጥ የሚኖሩ ሴቶችና ሕፃናትን ለመርዳት የ111,567,744.70 ብር ፕሮግራም ተግባራዊ ሊያደርግ ነው፡፡
ድርጅቱ ግንቦት 6 ቀን 2007 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጋር የአራት ዓመት የፕሮጀክት ስምምነት በሰሜን ሆቴል በተፈራረመበት ወቅት የተገኙት የድርጅቱ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ማርገሬት ሽለር እንደተናገሩት፣ ፕሮግራሙ ለችግር የተጋለጡ ሕፃናትን ለመርዳት፣ መንግሥት አካቶ ትምህርትን ጨምሮ በምትህርትና በጤናው ዘርፍ ያቀዳቸውን ሥራዎች ለማገዝና የወጣቶችን አቅም ለመገንባት የተቀረፀ ነው፡፡
በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ግምገማ የሥራ ሒደት መሪ አቶ አታክልቲ ገብረክርስቶስ፣ ወርልድ ቪዥን ከ111 ሚሊዮን ብር በላይ የሚፈጀውን ፕሮግራም በአግባቡ እንደሚተገብረው ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡
ድርጅቱ ከዚህ ቀደም ከአማራ፣ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች እንዲሁም ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልላዊ መንግሥታት ጋር በተከታታይ የ1.3 ቢሊዮን፣ የ862 ሚሊዮን እንዲሁም የ120,436,459 ብር ፕሮጀክቶች ለመተግበር ስምምነት ማድረጉ ይታወቃል፡፡