Tuesday, November 28, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየግል ድርጅቶች የጡረታ አዋጅ ረቂቅ ማሻሻያ ተቃውሞ አስነሳ

የግል ድርጅቶች የጡረታ አዋጅ ረቂቅ ማሻሻያ ተቃውሞ አስነሳ

ቀን:

በፕሮቪደንት ፈንድ የታቀፉ የግል ድርጅት ሠራተኞችን በመንግሥት በሚተዳደረው የግል ድርጅቶች ጡረታ እንዲዘዋወሩ የሚያስገድድ ማሻሻያ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቅረቡ፣ በግል ድርጅቶች ሠራተኞች ዘንድ ተቃውሞ ቀሰቀሰ፡፡

የግል ድርጅቶች ሠራተኞች ጡረታ አዋጅ 7/5/2003 በሐምሌ ወር 2003 ዓ.ም. ተግባራዊ መሆን ከመጀመሩ በፊት፣ የፕሮቪደንት ፈንድ ሽፋን ያላቸው የግል ድርጅት ሠራተኞች በነበራቸው የፕሮቪደንት ፈንድ ተጠቃሚነት ለመቀጠል እንዲወስኑ፣ ወይም በግል ድርጅት ሠራተኞች ጡረታ ስለሚሸፈኑበት ሁኔታ ሊስማሙ እንደሚችሉ ይደነግጋል፡፡

በዚህ የተነሳም በአገሪቱ የሚገኙ በርካታ የግል ድርጅቶች ሠራተኞች በተሰጣቸው አማራጭ ላይ ውይይት በማድረግ በፕሮቪደንት ፈንድ መታቀፍን መምረጣቸው ይታወሳል፡፡ ነገር ግን ከአራት ዓመት በኋላ ባለፈው ሐሙስ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው ማሻሻያ አዋጅ የቀድሞውን አማራጭ በማስቀረት፣ ሁሉም የግል ድርጅቶች ሠራተኞች በጡረታ ዕቅድ እንዲሸፈኑ ማሻሻያ አቅርቧል፡፡

ማሻሻያው በዚህ ላይ ብቻ ሳይሆን የግል ኩባንያ ባለቤቶች በግል ድርጅቶች ሠራተኞች የጡረታ ዐቅድ ሥር እንዲታቀፉ፣ እንዲሁም ከአሥር ዓመት በታች ያገለገሉ የግል ድርጅት ሠራተኞች በሚለቁበት ወቅት ቀደም ሲል ይፈቀድ የነበረውን ክፍያ ያስቀራል፡፡

በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አንድ የግል ባንክ ኃላፊ፣ አሁን በሥራ ላይ በሚገኘው የግል ድርጅቶች ሠራተኞች የጡረታ አዋጅ በሚፈቅደው መሠረት፣ በሁሉም ቅርንጫፎች የሚገኙ ሠራተኞች በፕሮቪደንት ፈንድ እንዲታቀፉ በፍላጎታቸው መምረጣቸውን ገልጸዋል፡፡ ረቂቅ አዋጁ ለፓርላማ በመቅረቡ ግን ከሠራተኞች ጋር በጉዳዩ ላይ ውይይት እያደረጉ መሆኑንና ውሳኔ ለመወሰን መቸገራቸውን አስረድተዋል፡፡

ለዚህ የሚሰጡት ምክንያት ደግሞ በፕሮቪደንት ፈንድ ወይም ቀድሞ በነበራቸው ጡረታ ለመቀጠል ተስማምተው ሲቆጥቡ የነበሩ ሠራተኞች፣ የፕሮቪደንት ፈንድ ወደ ግል ድርጅቶች ሠራተኞች ጡረታ ፈንድ እንደሚዘዋወር በረቂቅ አዋጁ የተካተተ በመሆኑ ቢፀድቅ የሕግ ተጠያቂነትን ያስከትል እንደሆነ ከሕግ ባለሙያዎች ጋር በመነጋገር ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

አንድ ስማቸውንም ሆነ የሚሠሩበትን መሥሪያ ቤት መጥቀስ ያልፈለጉ ሥራ አስኪያጅ ‹‹እንዴት በሕግ የተሰጠን መብት ተጠቅመው ፕሮቪደንት ፈንድን የመረጡ ሠራተኞችን ገንዘብ ለመውሰድ መንግሥት ሕግ ያወጣል?›› ሲሉ ድርጊቱን ተችተውታል፡፡

በማከልም ጉዳዩ የሠራተኞችን መብት መደፍጠጥ እንደሆነና መንግሥት ማድረግ የነበረበት ለፕሮቪደንት ፈንድ የማኅበራዊ ዋስትና የሕግ ከለላ በመስጠት፣ በቀጣሪዎች እንዳይመዘበር መቆጣጠር ነበረበት በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የግልግልና ዳኝነት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተርና የሕግ ባለሙያው አቶ ዮሐንስ ወልደ ገብርኤል፣ በረቂቅ አዋጁ ላይ የግል አስተያየታቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ አቶ ዮሐንስ አስተያየታቸውን መስጠት የጀመሩት፣ የግል ጡረታ ቦርድ ውስጥ የግል ባለሀብቶች እንዲወከሉ በሕጉ የተቀመጠ መሆኑን አስታውሰው፣ በዚህ ቦርድ ውስጥ የግሉ ዘርፍን በመወከል የተቀመጠ ሰው በዚህ ረቂቅ ማሻሻያ ላይ በስምምነት ፈርሞ ከሆነ፣ የግሉን ዘርፍ የሚወክል ግለሰብ ነው ብለው እንደማያምኑ በመግለጽ ነው፡፡ ‹‹እነዚህ ተወካዮች የግሉን ዘርፍ የሚወክሉ ናቸው ብዬ አላምንም፡፡ ምክንያቱም የግሉ ዘርፍ የመንግሥት ተጧሪ የመሆን ፍላጐት አለው ብዬ አላምንም፤›› ብለዋል፡፡

በ2003 ዓ.ም. ፀድቆ ወደ ሥራ የገባው የግል ድርጅቶች ጡረታ አዋጅ ቀደም ሲል በፕሮቪደንት ፈንድ ወይም በጡረታ ዐቅድ ተሸፍነው የነበሩ ሠራተኞች፣ ከፕሮቪደንት ፈንድና ከጡረታ ዐቅድ እንዲመርጡ በተሰጣቸው ዕድል ነፃ ውይይት አድርገው ፕሮቪደንት ፈንድን ይጠቅመናል ብለው መወሰናቸውን አቶ ዮሐንስ ይገልጻሉ፡፡ ‹‹የግሉ ዘርፍ ሠራተኞች ውሳኔ እንዳልወሰኑ አድርጐ በመውሰድ እንደገና ወደኋላ ሄዶ ሠራተኛው የወሰነውን ውሳኔ መሻር የሕግ መርሆዎችን የሚጥስ ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹በንጉሡ ጊዜ ፀረ አብዮት ወንጀል ፈጽመሃል፤›› ተብለው በደርግ ጊዜ ሰዎች እንደሚከሰሱ ገልጸው፣ ይህንንም ረቂቅ አዋጅ ከዚህ ሥርዓት ጋር አነፃፅረውታል፡፡ ሌላው አቶ ዮሐንስ  ያነሱት በዚህ ረቂቅ አዋጅ ላይ የግል ኩባንያ ባለሀብቶች በጡረታ ዐቅድ እንዲታቀፉ ማሻሻያ ማቅረቡ ትክክለኛነት ላይ ነው፡፡

የኩባንያ ባለቤቶች ወይም ባለሀብቶች በርካታ የማኅበራዊ ዋስትና አማራጮች እንዳሏቸው፣ ከእነዚህም መካከል የጡረታ ኢንሹራንስ ሊገዙ እንደሚችሉና ሌሎች የመሳሰሉትን ማድረግ እንደሚችሉ እየታወቀ፣ መንግሥት የራሱ ተጧሪ ሊያደርጋቸው መፈለጉ አስገራሚ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ የግል ድርጅት ማለት በኢትዮጵያውያን ብቻ የተያዘ አለመሆኑንና ትውልደ ኢትዮጵያዊ የሆኑ የውጭ ዜጎች ያቋቋማቸው ኩባንያዎችም እንዳሉ የሚገልጹት የሕግ ባለሙያው፣ እነዚህ የውጭ ዜጎች በአገራችው የተሻለ የማኅበራዊ ዋስትና ሽፋን የሚያገኙ ሆነው ሳለ መንግሥት እነዚህንም ተጧሪ ለማድረግ ማሰቡ አስደናቂ ነው ብለዋል፡፡

መንግሥት ይህንን ማሻሻያ እያደረገ የሚገኘው ካለው ከፍተኛ የገንዘብ ፍላጎት አንፃር እንደሆነ እንደሚገምቱ የሚገልጹት ባለሙያው፣ ‹‹መንግሥት ያልተረዳው ከመንግሥት የተሻለ አገር የሚያለማው የግል ባለሀብቱ መሆኑን ነው፤›› ሲሉ ተከራክረዋል፡፡

ይህ ረቂቅ ማሻሻያ ሙሉ አይደለም ብለው የሚከራከሩበት ሌላው ነጥብ የጡረታ ሽፋን ያላቸው የቤተሰብ መሪዎች፣ ‹‹የተሽከርካሪ አደጋ ሊሆን ይችላል ወይም በፍትሕ እጦት በሚደርስ የሕግ ተጠያቂነት ለእስር በሚዳረጉበት ወቅት፣ የእሱን ወይም የእሷን እጅ ጠበቀው የሚኖሩ ቤተሰቦቹን የማይሸፍን ጎደሎ ነው፤›› ብለውታል፡፡

እንደ ደቡብ አፍሪካ፣ ግብፅና ሞሪታንያ የመሳሰሉ አገሮች በተገለጸው ዓይነት ችግር ለሚፈጠር የቤተሰብ ቀውስ ‹‹የቤተሰብ አበል›› የሚል ዋስትና እንዳላቸው፣ ይህ ማሻሻያ የሚፀድቅ ከሆነ ይህንን ነጥብ ሕግ አውጪው ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል፡፡

ፓርላማው ባለፈው ሐሙስ በአዋጁ ላይ አጭር ውይይት ካደረገ በኋላ ጉዳዩን ለሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በዋናነትና፣ በተደራቢነት ደግሞ ለሕግ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር ዕይታ መርቶታል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለሲኒመር ትሬዲንግ አ/ማ አባላት በሙሉ የጠቅላላ ጉባኤ የስብሰባ ጥሪ

ለሲኒመር ትሬዲንግ አ/ማ አባላት በሙሉ የጠቅላላ ጉባኤ የስብሰባ ጥሪ ሲኒመር ትሬዲንግ...

የባህር በር በቀጣናዊ ተዛምዶ ውስጥ

በበቀለ ሹሜ መግቢያ በ2010 ዓ.ም. መጋቢት ማለቂያን ይዞ ዓብይ አህመድ በጠቅላይ...

ሥጋት ያስቀራል ተብሎ የሚታሰበው የጫኝና አውራጅ መመርያ

በአዲስ አበባ ከተማ በሕገወጥ መልኩ በመደራጀት ማኅበረሰቡ ላይ እንግልትና...

ማወቅ ወይስ አለማወቅ – ድፍረት ወይስ ፍርኃት?

በአሰፋ አደፍርስ ወገኖቼ ፈርተንም ደፍረንም የትም አንደርስምና ለአገራችን ሰላምና ክብር...